የቅዱሳን ልብ የሚያርፍበት አገልግሎት
በአንድ
ወቅት በአሜሪካን አገር ግራንድ ራፒዲስ
በሚባለው ከተማ ጥቂት ኢትዮጵያውያን
የእግዚአብሔርን ፊት በጾምና በጸሎት እየፈለግን
ባለበት ሰዓት የእግዚአብሔርን ቃል እንዲያካፍል
የተመረጠው ሰው ለመልእክቱ መግቢያ ያደረገውን
የማይረሳ ምሳሌ ሁል ጊዜ አስታውሳለሁ፡፡
እንዲሀ ነው ነገሩ!
እንደ
አውሮጳውያን አቆጣጠር በ2009
የተባበሩት
መንግታት የኢኮኖሚ ፎረም ባደረገው ዓመታዊ
ስብሰባ የተለያዩ የመንግሥታቱ አባል አገሮች
ተወካዮች የየአገራቸውን የሥራ ሪፖርት ይዘው
ቀረቡ፡፡ ከየአገሩ የመጡ ተወካዮች
ምን ለመሥራት
ታሰቦ ምን አንደተከናወነና እንዴት ያለ ለውጥ
እየታየበት እንደሆነ እያካፈሉ አንዳቸው
ከሌላው ልምድም እየቀሰሙ ባለበት ወቀት የአንድ
አገር ሪፖርት ግን የብዙዎችን ልብ የነካና
የተደነቀ ሆነ፡፡ ያቺ አገር በሩቅ ምሥራቅ
የምትገኝ ባርማ በመባል የምትተወቅ አገር ናት ፡፡ ባርማ በ2009
ዓ.ም
ልትሠራ ያቀደችውና ያከናወነችው ሌሎች አገሮች
ካቀረቡት ጋር በፍፁም የማይገናኝ
ነገር ግን ሁሉንም ያስደነቀ አቀራረብ ነበር፡፡
ሌሎች ስለ ልማት፣ ስለ አኮኖሚያዊ
እድገት፣ ስለ ውጭ ግንኙነትና ስለ ወታደራዊ
ዝግጅቶቻቸው ሆኖ ካቀዱት ምን ያህል እንደተሳካላቸው
ነበር ያቀረቡት፡፡ ባርማ ግን በ2009
መግቢያ
ላይ የያዘቺው እቅድ በአገሪቱ ውስጥ ያለ
እያንዳንዱን ዜጋ በነፍሰ ወከፍ ደስተኛ
እንዲሆን ስለማድረግ ነበር፡፡ ከልማት ሥራዎች
ሁሉ የሚቀድመው የዜጋው ረክቶና ተደስቶ የመኖር
ጉዳይ ስለሆነ ከዚህ አንፃር አቅዳ 90
በመቶ
እንደተሳካለት
ያቀረበቺው ሪፖርት ሁሉንም የጉባኤ ተሳታፊዎችን
ሊያስደንቅ ችሏል፡፡
ይህ ለእኛ የእግዚአብሔርን
ሕዝብ ለምናገለግል
ሰዎች እጅግ በጣም አስገራሚ ትምህርት ያለበት
ምሳሌያዊ መልእክት ነው፡፡ እኛ ከባርማ
መንግሥት ይልቅ የምናገለግላቸውን ቅዱሳን
ልባቸው እንዲያርፍ ማድረግ ይኖርብናል፡፡
እግዚአብሔርም
እኛን በዚህ ምድር ላይ
ያስቀመጠን የእርሱን አሳብ እያገለገልን በስሙ
የተጠሩትን ሁሉ እንድናንፃቸው ነው፡፡
የአገልጋዮች አገልግሎት
የምዕመናንን
ልብ የሚያሳፈርፍ
እንዲሆን
ደግሞ የእግዚዘአብሔር
ቃል ይመክረናል፡፡ በአገልግሎታችን
የቅዱሳንን ልብ እንዴት
ማሳረፍ እንደሚቻል
ሐዋሪያው ቅዱስ
ጳውሎስ ለፊልሞና በጻፈውን
መልእክት ከቁጥር 1-7
መመልከት
እንችላለን፡፡ ወደ
ዋናው አሳባችን ከመግባታችን በፊት ስለ ፊልሞና
መጽሐፍ ሁለት ወይም ሦስት መሰረታዊ በሕሪያቶችን
እንመልከት፡፡ የፊልሞና መጽሐፍ
ሐዋሪያው
ጳውሎስ በእሥር
ቤት ሆኖ ከጸፋቸው የአዲስ ኪዳን መጻሕፍት
አንዱ ነው፡፡ ጳውሎስ ይህንን መፅሐፍ በሚጽፍበት
ወቅት በሮም እሥር ቤት ሊሆን ይችላል፣ ወይም
በሌላ ቦታ ሊሆን ይችላል ብቻ መልእክቱን
ያስተላፈው ከእሥር ቤት ነው፡፡ የፊልሞናን
መጽሐፍ በጣም ተናፋቂ ከሚያደርጉት ነገሮችም አንዱ ይህ ነው፡፡ ከየትና እንዴት በማንስ
ተጻፈ የሚለው አሳብ የሚተላለፈው መልእክት
ተሰሚነት እንዲኖረውና አቅምም አንዲያገኝ
ያደርገዋል( ቁ.9)፡፡
ሁለተኛው
የፊልሞና በጣም አጠር ካሉ
ወይም ምዕራፍ ከሌላቸው መጻሕፍት ይመደባል፡፡
በጠቅላላው በመጽሐፍ ቅዱ ውስጥ ወደ አራት
ያህል መጻሕፍት በምዕራፍ ያልተከፈሉ
ሲሆን እነርሱም አብዲዩ፣2ኛ
ዮሐንስ፣ 3ኛ
ዮሐንስ ና ፊልሞና ናቸው፡፡ እነዚህ መጻሕፍት
በምዕራፍ አይከፋፈሉ እንጂ ትልቅ ቁም ነገር
ያዘሉ ናቸው፡፡ በምዕራፍ ያልተከፈሉበት
ምክንያት አጠር ባለ መልክ ስለቀረቡ ብቻ እንጂ
መልእክቱ ከእግዚአብሔር ስላልሆነ አይደለም፡፡
ሦስተኛ የፊልሞናን
መጽሐፍ ልዩ የሚያደርገው የመልእክታቴ ምጋቤ
አካል ከሆኑት መጸሕፍት የሚመደብ መሆኑ ነው፡፡
ይህ መጽሐፍ ለቡድን ወይም ከቤተ ክርስቲያን
ወይም ለአንድ አገልግሎት ክፍል የተላከ ሳይሆን
የሕዝብ እረኛና አገልጋይ ለሆነ ሰው በግሉ
የተላከ የመጋቢያዊ መልእክት ያዘለ ነው፡፡
ለአንድ ግለሰብ የተላኩ ሌሎችም መጻሕፍት
በአዲስ ኪዳን ውስጥ
ያሉ ሲሆን ሁላቸውም የየራሳቸው ባሕሪያት
ያሉአቸው ናቸው፡፡
በዚህ
አጭር ትምህርት ውስጥ ሐዋሪያው ጳውሎስ
ለፊልሞና
የሚያቀረበውን
መልእክት ሁሉንም ማየት እችልም ፣ ነገር ግን
ከቁ 1-7 ያለውን
ብቻ እንመለከታን፡፡ ይህንን
መልእክት የሚያስተላልፈው የእግዚአብሔር
ሰው ጳውሎስ የጌታ አገልጋይ ከሆነው ከፊልሞና
ጋር ትልቅ የአገልግሎት
መተሣሠር ነበራቸው፡፡ ጳውሎስ በእሥር ቤት
ሆኖ ስለ ፊልሞና አገልግሎት የሰማው ነገር
በእርሱ ላይ የፈጠረው አዎንታዊ ተጽእኖ በዚህ
የንባብ ክፍል ውሰጥ ይገኛል፣ ምክንያቱም
ጳውሎስ በፊልሞና አገልግሎት ምክንያት
መጽናናቱንና መደሰቱን ይናራል(
ቁ.
7)፡፡
በፊልሞና አገልግሎት በቤተ ክርሰቲያን
ያሉ ቅዱሳንን
ልብ በማረፉ ምክንያት
ጳውሎስ ተደስቷል፣ በብዙ
መጽናናትም
ተጽናንቷል፡፡ እንዲህ ያለ
አገልግሎት ማገልገል እንዴት ዓይነት መታደል
ነው!
ፊልሞና
የሚያገለግለው አገልግሎትና በቤተ ክርስቲያን
ውስጥ የሚያደርገው ሥራና ተግባር ሁሉ የሕዝቡን
ልብ ከመረበሽና መንፈሳቸውን ከማናወጥ ይልቅ
ልባቸውን የሚያሳርፍ ነበር፡፡ ስለዚህ እኛ
ዛሬ በዚህ ዘመን የምንገኝ አማኞች የቅዱሳንን
ልብ ከማሳረፍ አንፃር እንዴት አይነት አገልግሎት
እየሰጠን እንደሆነ ራሳችንን መመልከት
ይኖርብናል፡፡ እስቲ የቅዱሳንን ልብ የሚያሳርፍ
ሕይወትና አገልግሎት ምን እንደሚመስል ሐዋሪያው
ጳውሎስ ለፊልሞና ከጻፈው መልእክት እንመልከት፡፡
1.
አገልገሎቱ
የቅዱሳንን ልብ የሚያሳርፈው
አገልጋይ
የይቅርታ ልብ ያለው ነው፡፡
ጳውሎስ
ይህንን መልእክት ለፊልሞና የሚልክበት ተቀዳሚ
ምክንያት በፊልሞናና በአናሲሞስ መካከል
ክርስትያናዊ ይቅርታን ለማስፈን ነው፡፡ ይህ
መጽሐፍ ሙሉውን የሚናገረው
ስለ ይቅርታ ነው፡፡ ፊልሞና በፍቅርና ሌሎች
መልካም ሥራዎች የቅዱሳንን ልብ ያሳረፈ ምርጥ
አገልጋይ ቢሆንም ጳውሎስ በድጋሚ ስለ አናሲሞስ
ይጠይቀዋል፡፡ አናሲሞስ የፈልሞና አገልጋይ
(በጥንት
አባባል ባሪያው) ሆኖ
ከፊልሞናም ጋር አብሮ ይኖር
ነበር፡፡ ነገር ግን በአንድ
ወቅት ፊልሞናን ዘርፎ በመኮብለሉ
የፊልሞና ልብ በአናሲሞስ
አዘነ፡፡
ይሁን እንጂ አናሲሞስ ኮብልሎ በሄደበት ጳውሎስ
አገኘውና ወንጌል ሰበከለት፣ አናሲሞስም በጌታ በኢየሱስ አመነ፡፡ ጳውሎስ በእሥር
ቤት በነበረበት ወቅት በወንጌል እንዲያምን
ምክንያት ስለሆነው አናሲሞስ ይረዳና ያግዘው
ነበር፡፡ በዚህን ጊዜ የአናሲሞስ ለጳውሎስ
አስፈላጊ ሰው ቢሆንም ያለ ፊልሞና ፈቃድ ለራሱ
ሊያስቀረው ስላልፈለገና በሁለቱ መካከል
የይቅርታ
መንፈስ እንዲሰፍን ስለፈለገ ወደ ፊልሞና
ይልከዋል፡፡ እንዲያውም ፊልሞና አናሲሞስን
እንደ ወንድሙ እንዲቀበለው ይማጸነዋል፡፡
ያ ብቻ ሳይሆን የተደበለውንም ሁሉ በእርሱ
ላይ እንዲቆጥርበት ይጠይቀዋል፡፡ እንግዲህ
ከዚህ የምናየው እርቅና ሰላም በሌለበት ሥፍራ
ሁሉ ጭንቀትና መረበሽ እንዲሁም አለመረጋጋት
መኖሩን ነው፡፡ ስለዚህ ነው ሐዋሪያው እባክህ
ልቤን አሳርፍልኝ የሚለው!
ይህ
የጌታ አገልጋይ ባደረጋቸው ሥራዎች ሁሉ
የቅዱሳንን ልብ በማሳረፍ የሚታወቅ ቢሆንም
አሁን ደግሞ ለአናሲሞስ ይቅርታ በማድረግ
የበለጠ የጳውሎስንና የሌሎችን ልብ እንዲያሳርፍ ተጠይቋል፡፡ ይቅርታ ሲደረግ የቅዱሳን ልብ
ያርፋል ማለት ነው፡፡ ሁለት የቤተ ክርስቲያን
መሪዎች ሲጫቃጨቁና ሲቃረኑ እንቅልፉን የሚያጣው
ምዕመኑ ነው፡፡ ሁለት መጋቢዎች ባለመግባባት
እርስ በእርሳቸው ሲገፋፉ የሚያዝነውና
የሚረበሸው ጉባኤው ነው፡፡ መሪዎች እርስ
በእርሳቸው የሰላምና የፍቅርን አገልግሎት
በሚሰጡበት ወቅት በምዕመናን መካከል ያለው
ደስታና ፍንደቃ ትልቅ ይሆናል፡፡
የብሉይ
ኪዳን መጸሕፍትን በምንመለከትበት ወቅት
የእሥራኤል ሕዝብ ለጦርነት ከተጋለጠባቸው
ምክንያች አንዱ የመሪዎች ሁኔታ ነው፡፡
በአናጸሩ ደግሞ አገርን ከሚመሩ ነገሥታት
የተነሳ ምድርት አርፋ እንደምትቀመጥ የእግዚአብሔር
ቃል በእርሱ ጊዜ ምድሪቱ በሰላም አርፋ ተቀመጠች
እያለ ይናገራል፡፡ እንደዚሁም ሁሉ በቤተ
ክርስቲያንም የሚያገልግሉ መሪዎች እርስ
በርሳቸው በፍቅር ሲቀባበሉና ሲዋደዱ በመላ
ቤተ ክርስቲያን የሚታየው ደስታ እጅግ የላቀ
ይሆናል፡፡ ጳውሎስም ፊልሞናን ልቤን
አሳርፍልኝ ማለትም ይቅርታ በማድረግ ልብ
የሚያሳርፍ ሥራህን ቀጥል የሚለው ለዚህ ነው፡፡
ዛሬም
እኛ የሚያስፈልገን የአገልግሎት ብዛት
አይደለም፡፡ ብዙ መስበክም አይደለም፡፡ ነገር
ግን የቅዱሳንን ሁሉ ልብ የሚያሳርፍ አገልጋይ
ሆነን መገኘት ነው፡፡ እኛ ይቅርታን የማይቀበል
በቀለኛ በሆነ ሁኔታ ውስጥ ያደግን ሰዎች
ነን፡፡ አብዛኛው ባህላችን ቁጣና በቀል የተሞላ
ነው፡፡ ብድር በምድር የሚለው አስተሳሰብ
አብሮት ከማደጉ የተነሳ ትውልዳችን ይቅርታን
መጠየቅን እንደ ሽንፈት፣ ይቅርታን ማድረግን
እንደ ሞኝነት የሚቆጥር ነው፡፡ ጌታን
ተቀብለን አገልጋዮችና የቤተ ክርስቲያን መሪዎች
ከሆንንም በኃላ እንኳ ያ አብሮን ያደገው
ልማዳችን ከውስጣችን አልወጣ ብሎ ጊዜ
ይወስድብናል፡፡ ስለዚህ ብዙዎቻችን በእግዚአብሔር
ቤት እንበቃቀላለን፣ አንዳችን ሌሎችን
እናሳድዳለን፡፡ በተለያየ
የአገልግሎት ዘርፎች ብናገለግልም
በእግዚአብሔር መድረክ ላይ
እያለንም በቀለኝነት ያጠቃናል፡፡ ይህ ከመሆኑ
የተነሳ የእግዚአብሄርም ልብ አልተደሰተም
የቅዱሳንም ልብ አላረፈም፡፡ እኛ የእግዚአብሔርን
ሕዝብ እያሳረፍን ነው ወይስ እያሳዘንን;
እያራወጥነው
ወይስ እያረጋጋነው፣ እያጽናናነው ወይስ
እያስጨነቅነው ነው የሚለውን ጠይቀን መልስ
ማግኘት ይኖርብናል፡፡ የእግዚብሄርን ቃል
በማስተማርና የተለያዩ
ቅዱሳት መጻሕፍትን መበጻፍ በዘመናችን ቤተ
ክርስቲያን ዘንድ ትልቅ አክብሮት ያላቸው
ዶር ጆን ማካርተር ይቅርታ አለማድረግ እንዴት
ያለ ክፉ ነገር እንደሆነ እንደሚከተለው
ገልተዋል፡፡
ይቅርታን
አለማድረግ ባለፈው የመራርነት ሕይወት እሥረኞች
አንድንሆን የሚያደርገን ነው፡፡
ይቅርታን አለማድረግ ለሰይጣን አሠራር የተከፈተ በር የሚሰጥ ሲሆን እኛም
አጋንንትን በዚያው እንኳን ደህና መጣህ
እያልነው ነው፡፡ ይቅርታ አለማድረግ በእኛና
በእግዚአብሔር መካካል ላለን ሕብረት እንቅፋት
ነው፡፡ ምከንያቱም ጌታ ኢየሱስ ሲያስተምር
ለሰዎች
ኃጢአታቸውን ይቅር ባትሉ የሰማዩ አባታችሁ
ኃጢአታችሁን ይቅር አይላችሁም፡፡ ለሰዎች
ኃጢአታቸውን ይቅር ካላልን ደስታችንና ሰላማችን
ይወሰድብናል፡፡ ጳውሎስ በፊልሞናና በአናሲሞስ
መካካል ሆኖ ሁለቱን የሚሸ መግላቸው ይመስላል፡፡
አናሲሞስ ፊልሞናን በጣም አድርጎ በድሎታል፡፡
ጳውሎስና ፊልሞና በነበሩበት ዘመን አናሲሞስ
ያደረገውን ዓይነት በደል የፈጸመ በባህላቸው
መሠረት ይወገዛል ፣ ይወገራል፣ ይሰደዳል
እንዲያውም ገደላልም፡፡ እርሱ የፈጸመው
ወንጀል በማንኛውም ማኅበራዊና ሕዝባዊ ጉዳዮች
ሥፍራ እንዳይኖረው የሚያደርግ ነው፡፡ምክንያቱም
አናሲሞስ ለፊልሞና ባሪያው ሆኖ እያለ ያንን
በአሠሪዎች ዘንድ ከባድ ወንጀል ሆኖ የሚታወቀውን ጥፋት ሠራ፡፡ ምናልባት አናሲሞስ ከአካባቢው
የሸሸው የሚደርስበትን ቅጣት ፈርቶም ሊሆን
ይችላል፡፡ የእግዚአብሔር ሕግ ግን ይህንን
በደለኛውን ሰው አንደ ወንድምህ ቁጠረው ይላል፡፡
ይህ ቀላል ሊሆን የማይችልበት ምክንያት አለ፡፡
አንደኛ ባሪያና ጌታ ሁለቱ እኩል በማዕድ
መቀመጥ የሚችሉበት ባህላዊ አግባብ በጊዜው
አልነበረም፡፡ ዘራፊና ቀመኛ ምንም ቢሆን
ከተቀማው ሰው ጋረ ሕብረት እንዲያደርግና
ከዚያም አልፎ እንደ ወንድም ሊቀበል የሚችል
ሥርዓትም ሆነ ልማድ አልነበረም፡፡ የእግዚአብሔር
ህግ ግን ከዚህ ሁሉ ይለያል፡፡ እንደ ወንድምህ
ቁጠረው ፣ ባሪያ ከነበረበት እንደ ወንድምህ
አድርገው የሚል ነው፡፡ ጥፋት አድርሶ የኮበለለውን
የጠገበ ሠራተኛ ወደ ሥራው አንዲመለስ
አሠሪውን እንማፀነው ይሆናል ፣ ወንድም
አድርገው ለማለት ምንም የማይታሰብ ነው፣
ማለት የሚፈልግም ካለ ደግሞ ሆን ብሎ ሽምግልናውን
ለማደፍረስ እንደሚፈልግ ሰው ለፈረጅበት ሁል
ይችላል፡፡ ጳውሎስ ለፍልሞና የሚናረው መልእክት
ግን ወደ ሥራው እንዲመለስ ከሚለው የዘለለና
እንደ ወንድም ቁጠረው የሚለው ነው፡፡ ይህ
ሊሆን የሚችለው ክርስትና ሲገባን ብቻ ነው፡፡
ስለ ይቅርታ ሰብከው ሲመለሱ ወንድማቸውን
ይቅር አልልም ብለው ሳምንት ሙሉ ሽማግሌ
የሚያመላልሱ አገልጋዮች ብዙ ናቸው፡፡ እነዚህ
ስብከት ችለዋል እንጂ ክርሰትናው ገና
አልገባቸውም አሊያም
ክርስትና የሚያሰከፍለውን ዋጋ ገና አላወቁትም፡፡
ምክንያቱም ክርስትና የዘረፈህን
ጥጋበኛና ጎረምሳ አገልጋይን ወደ አንተ ሲመጣ
እንደ ወንድምህ አድርገው እንጂ እንደ ሠራተኛህ
አትየው የሚል ነው፡፡
ጳውሎስ
ስለ ፊልሞና የተረዳው ሁሉ አዎንታዊ ነው፡፡
የሚያርምበት አንድም ነገር እስከማይኖርበት
ድረስ ሕይወቱ የተመሰከረለት ሰው ነው፡፡ ምን
አይነት ባሕሪያ ነው!
አሁን
ግን ለአናሲሞስ ይቅርታ በማድረግ የበለጠ
ይምሰገናል ክርሰቲያናዊ ጀግና ይባላል ወይም
ብዙ የሆነው መልካም ነገሩ በአንድ ነገር
ምክንያት
ብቻ ዋጋው ሊረክሲበት ይችላል፣ ያውም ይቅርታ
በማድረግ ወይም ባለማድረግ፡፡ ብዙ የመድረክ
ጀግኖች ተፈትነው በቀላሉ ክብደታቸው ታወቀ፡፡
እኔ እኮ ጌታን ካገኘውና በመንፈስ ቅዱስ
ከተሞላው ይህን ያህል ሰዓት ሆኖኛል፣ እነ
እገሌም በመንፈስ ቅዱስ የተሞሉት እኔ እጅ
ጭኜ ስጸልይ ነው ብለው የሰውን ሁሉ እትኩሮት
ሲስቡ የኖሩ ቱባዎቻችን ክርስትናቸው ከወጣበት
በአንዴ ሲወርድ ያየነው ለባልንጀራቸው ይቅርታ
እንዲያደርጉ ሲጠየቁ ያዙኝ ልቀቁኝ ሲሉ ያየን
ቀን ነው፡፡
2.
የቅዱሳንን
ልብ የሚያሳርፍ አገልጋይ ስለ ሰዎች
ሕይወት የሚጨነቅ ነው(
ቁ.4)፡፡
ፊልሞና
ለሰዎች ግድ የሚለው፣
ለእነርሱ
የሚጨነቅና በቅዱሳን
ሁሉ ዘንድ ፍቅር ያለው ሰው ነበር፡፡ እርሱ
ከተወሰኑ ሰዎች ጋር በፍቅር የተሳሰረ ፣
ከተቀሩት ጋር ደግሞ አኩራፊ ዓይነት ሰው
ሳይሆን ከቅዱሳን
ሁሉ ጋር በፍቅር የሚኖር ሰው ነው፡፡ ይህ
ፍቅር ደግሞ ለሰዎች ሁሉ ሸክም እንዲኖረው
አድርጎታል፡፡ ጳውሎስም
ለፍልሞና ፍቅር እንደነበረው
ከቁ.11-14
ያሳየናል፡፡
አናሲሞስ በእሥር ቤት ላለው ለጳውሎስ
በጣም ስለሚያስፈልገው ከራሱ
ጋር ቢያቆየው የማይወቀስበት
ብዙ ምክንያቶች አሉ፡፡ አንደኛው፣ አናሲሞስ
ገና ጌታን ሳያገኝ ከፊልሞና ኮብልሎ ሄዷል፡፡
ሁለተኛ ወንጌል መስክሮ እንዲለወጥ ምክንያት
ስለሆነው አሁን የወንጌል ልጁ ሆኖታል፡፡
ስለዚህ ቢያስቀረው
ፊልሞናም ቢሆን ቅር ሊሰኝበት አይችልም፡፡
ይሁን እንጂ
ጳውሎስ ከራሱ ጥቅም ይልቅ የፍልሞናን
በመስቀደም አናሲሞስን ወደ ፊልሞና ላከው፡፡
ለእኔ ይልቅ የአንተ ይሻላል የሚል አቅም ያለው
ክርስትና ያለው ሰው ነው፡፡ እንግዲህ
እግዚአብሔርም
ደስ የሚሰኝበትና የቅዱሳን
ልብ የሚያርፍበት ሕይወት
እንዲህ ዓይነቱ ነው፡፡
3. የቅዱሳንን
ልብ የሚያሳርፍ አገልጋይ ስለ እግዚአብሔር
የሚያስብ ነው(ቁ
4-5)፡፡
የእግዚአብሔር
ክብርና ከእርሱ ጋር ያለን ሕብረት ግድ የሚለን
ስንሆን የቅዱሳን ልብ ያርፋል፡፡ ጳውሎስ
በዚህ ክፍል ስለ ፍልሞና እምነት ሰምቶ
እግዚእብሔርን ያመሰግናል፡፡እምነት ሙሉ
በሙሉ ለእግዚአብሔር ያለንን
መሰጠትና
መተማመን እንዲሁም በጌታችን በፍጹም ማረፋችንን
የሚያመለክት ሲሆን
እኛን ከእግዚአብሔር ጋር ያገናኘናል፡፡
ፍቅር ደግሞ
ከሰዎች ጋር ያገናኘናል፡፡ ፡ ፈልምና እውነተኛ
የሆነ እምነት የነበርውነና
በእውነትም የተመሰከረለትም
አማኝ ነው፡፡ ሰዎች ከወንድሞቻቸው ጋር
ያላቸውን ነገር የሚያበላሹት
ከእግዚአብሔር ጋራ ያላቸው ነገር መበላሸት
ሲጀምር ነው፡፡ ብዙዎች ከእግዚአብሔርና
ከወንድሞቻቸው ጋር ካላቸው ህብረት ይልቅ
ለመድረካቸውና ለአገልጋይነት ስማቸው ትኩረት
ይሰጣሉ፡፡
ከአሥር ዓመት በፊት
ከአዲስ አባባ 400 ኪሎ
ሜትር አካባቢ የምትገኝ አንዲት
ቤተ ክርስቲያን ባዘጋጀቺው ኮንፍራንስ
የእግዚአብሔርን ቃል ለመስበክ ሄድኩ፡፡
ጉባኤው በጣም ትልቅ በመሆኑ ጸሎት ቤቱ ስላልቻለ
ፕሮግርሙ የተካሄደው በሜዳ ላይ ነበር፡፡
በዚያ ኮንፍራንስ መልእክት ካቀረብኩ በኋላ
የንሰሐ ጥሪ ሳቀርብ አንድ ወጣት ሚስቱን
እንደበደላትና ይቅርታ ሊጠይቃት እንደሚፈልግ
ተናገረ፡፡ ስለዚህ ከቤተ ክርስቲያን መጋቢ
ጋር በመሆን ሚስቱን አስጠራናትና ይቅርታ
እንድታደርግለት ስንጠይቃት አባቴ ይህንን
መስማት አለበት አለች፡፡ አባቷ የቤተ ክርስቲያን
ሽማግሌ ስለሆነ ከሰዎች ጋር የነገውን ፕሮግራም
በሚመለከት አንዳንድ ሥራዎችን እየሠራ ካለበት
አስጠራነውና ጉዳዩን ሁሉ አጫወትነው፡፡
ልጅቷ ይቅርታ አድርጋ ወደ ትዳሯ የመመለስ
ልብ ቢኖራትም
የአባቷ አቋም ግን ከጠበቅነው በላይ አስቸጋሪ
ሆኖ ተገኘ፡፡ ልጅቱ ከባሏ ጋር በተፈጠረው
ጊዜየያዊ
አለመግባባት ምክንያት
ካለችበት ትዳር ወጥታ ወደ አባቷ ቤት መጥታ
እዛው ናት፡፡ ጉዳዩን ለማስተካካል በጣም
ሰፊ ጊዜ ወሰደብን፡፡ ልጁን የበደለውን ሰው
ይቅር እንዲል ደጋመን ብንለምነውና ብንማጸነው
አባትዬው በጭራሽ እምቢ አለ፡፡ በመጨረሻም
ላይ እንዲህ ኣይነት ክርስቲና ይዘህ የቤተ
ክርስቲያን ሽማግሌ ልትሆን
ስለማትችል አግደንሃል ሲሉት እንደዚህ ከሆነ
እሺ እንዳላችሁት ይሁን አለ፡፡ ወጣቱ ባለትዳር
ሚስቱን የዞ ቤቱ ቢገባም ይህ ሽማግሌ ስለ
ክርስቲናውና እግዚአብሔር ስለሚጠብቅበት
ኑሮ ሳይሆን የተጨነቀው ስለ ሽምግልናው መሆኑ
የሁላቸንንም ልብ እንዳሳዘነ አስታውሳሁ፡፡
ዛሬም
በእኛ ዘመን ስለ ስማቸውና ስለ መድረካቸው
እንዲሁም በሰው ፊት ስለሚታየው አገልግሎታቸው
እንጂ ስለማይታየው መንፈሳዊ ሕይወታቸውና
የጌታ መንፈስ ከእነርሱ ስለሚፈልግባቸው
ሕይወታቸው ግድ የማይላቸው ብዙ አገልጋዮችና
መሪዎች ሊኖሩ ይችላሉ፡፡ ፊልሞና ግን እንዲህ
ዓይነት ሰው አይደለም፡፡ የሰሙትን ሁሉ
የሚያስመሰግን እምነት ያለው ሰው ነው፡፡
አንዲህ ዓይነቱ ሕይወት እግዚአብሔርን
ያስደስዋል ፣ የቅዱሳንንም ልብ ያሳርፋል፡፡
4. የቅዱሳንን
ልብ የሚያሳርፈው ስለ እውነተኛ ሕብረት
የሚያሳስበው ነው፡(
6)፡፡
በጌታ
ያለን አማኞች ማወቅ ያለብን ነገር ቢኖር
እውነተኛ እምነትን የቅዱሳን ሕብረት እንደሚከተለው
ነው፡፡ አንድነት፣የወንድማዊ ፍቅርና ሰላም
የክርስትያንነታችን ምልክትና የሕይወታችን
ክፍል ነው፡፡ ከሌሎች ጋር በምናሳልፍበት
ወቅት ከሌሎች እንማራለን፣ እንታነጽባቸዋለንም፡፡
ወደ ቤተ ክርስቲያን የምንሄደው ስብከት
ሰምተንና ተነቃቅትን ለመመለስ ብቻ ከሆነ ያ
ሁኔታ እኛን ራስ ወዳዶች ያደርገናል፡፡
ይልቁንም ለሌሎች በረከት ለመሆን፣ ከእነርሱም
ጋር ለመተያየትና እርስ በእርሳችንም ለመልካም
ሥራ እንድነነቃቃ ነው፡፡ ወደ እግዚአብሔር
ቤት የምንሄደው ለጋራ በረከት ነው፡፡
የወንድማችንን ሐዘን ሀዘናችን ደስታውንም
ደስታችን ልናደርግ ነው ፡፡ የእኛንም ሸክም
እነርሱ እንዲጋሩ ለማድረግ ጭምር እንጂ
ተሰብከን፣ ወይም ሰብከን ወይም ዘምረን ወይም
ለራሳችን በረከቱን አፍሰን ልንመጣ ብቻ
አይደለም፡፡ የቅዱሳን
ልብ የሚያርፈው ግን አንዳችን
ከሌላው ጋር በሕብረት ስንተሳሰር ነው፡፡
በርካታ አገልጋዮች ሰዎች
ሲጣሉ ደስ ይላቸዋል፡፡ እንዲያው ሰው ምን
ይለናል ብለው እንጂ ዱላ ቢያቀብሉ የማይጠሉ
አናካሾች አይጠፉም፡፡አንዲት ቤተ ክርስቲያን
ምዕመናን እርስ በርሳቸው ሲጨቃጨቁ አሁን
ወደ እኛ ይመጣሉ ብለው የሚደሰቱ ቤተ ክርስቲያን
አገልጋዮች ጥቂት አይደሉም፡፡ እነ ፊልሞና
ግን ይህ አይነከካቸውም፡፡ ስለ ሕብረትና
አንድነት የሚያስቡና የሚጨነቁ፣ የሚጠበቡም
ናቸው፡፡ ስለዚህ እንደዚህ ባሉት አገልጋዮች
ሕይወትና አገልግሎት የቅዱሳን
ልብ ያርፋል፡፡
5. የቅዱሳን
ልብ የሚያርፍበት አገልጋይ ስለ መንፈሳዊ
እውቀት የሚያሳስበው ነው(
ቁ6)፡፡
እውቀት ስንል ተራ መረጃ ሳይሆን ስለ እግዚአብሔር
ያለን ጥልቅ
መረዳት ማለታችን ነው፡፡ የእግዚአብሐሔርን
ነገር በጽንሰ አሳብ ደረጃ ማወቅናTheoretical knowledge በሕይወት
ልምምድ ውስጥ ገብተን ማወቅ /experiential knowledge/ ሁለት
የተለያዩ ነገሮች ናቸው፡፡ ፅንሰ አሳብ በሆነው
እውቀት ወደ ንስሐ አምልኮ፣ እንዲሁም ወደ
ይቅርታ ሕይወት መድረስ አይቻልም፡፡ በአገራችን
ሳለሁ በአውሮጳና በአሜሪካ እንዲሁም በሌሎች
የምዕራብ አገሮች በየክረምቱ ስለሚወርደው
በረዶ ከሚሰማው ነገር ተነስቼ ለሌሎችም ሰዎች
አስረዳቸው ነበር፡፡ በኢትዮጵያ የተቆረቆሩ
የፕሮቴስታንት አማኞች ቤተ ክርስቲያን
ሕንጸዎች ጣሪያቸው ከመሀል ከፍ ያለና ዳርና
ዳሩ ዝቅ ያለ ሲሆን ይህ አሠራር ምዕራባውያን
በረዶው ሲወርድ ጣሪያው ላይ ተከምሮ
እንዳይጎዳው እየተንሸራተተ እንዲወርድ
አድርገው ስለሚሠሩት ሚሲዮናውያኑ ወደ አገራችን
ሲመጡ ያንን የለመዱትን ዓይነት ቤት ስለሚሠሩ
ነው የጸሎት ቤቶቸችን ሕንጻዎች ከሌላው የተለዩ
የሚሆኑት ሲባል ስለ ሰማሁ እኔም ለብዙዎች
የሰማሁትን ያንኑን አስረዳ ነበር፡፡ ነገር
ግን ያንን ሁሉ የማስረዳው በረዶውን በዓይኔ
እንኳን ሳላየው ነበር፡፡ ከብዙ ጊዜያት በኋላ
ወደ ሚቺጋን መጥቼ በረዶ ሲወርድ፣ ከተማውን
ሁሉ ሲሸፍን፣ መንገዱን ሁሉ ሲዘጋ በቤቶች
ሁሉ ጣሪያ ላይ ተከምሮ ከዚያ እየተንሸራተተ
ሲወድቅ፣ መንገዱን ሁሉ ሸፍኖ ለመንዳት
ሲያስቸግርና እያንዳንዱ የሚቺጋን ነዋሪ
በወፋፈፍራም
ልብሶች ተጀቡኖ ሲሄድ ሳይ ለበረዶ ያለኝ
እውቀት የተለየ ሆነ፡፡ እንዲያውም እኔ በበረዶ
ላይ ሲነዳና መኪናዬ መንገድ ስታ የወጣችበትን
አጋጣሚ ሁሉ ሳስበው ሰው በመረጃ ብቻ የሚያውቀው
እውቀት በሕይወት ልምድ ከሚያውቀው ምን ያህል
የተለየ እንደሆነ በበለጠ
ተገነዘብኩ፡፡ ጳውሎስም ይህ የሕይወት ልምድ
እውቀት እንዲበዛለት ለፍልሞና
እንደሚጸልይለት ቃል ይገባለታል፡፡ ይህ
ጥልቅ እውቀትና መረዳት አፓጎኒሲስ ተብሎ
የሚጠራ ሲሆን ስለ እግዚአብሔርና
በእኛ ውስጥ ስላለው መንፈሳዊ ነገር ጥልቅ
የሆነ መረዳት a deep
understanding about God and about what in us/ ማለታችን
ነው፡፡ በእኛ ዘንድ እግዚአብሐየር ያቀመጠው
በጣም ብዙ የሆነ መልካም
ነገር አለ፡፡ ጌታ ኢየሱስን ካመንንበት ጊዜ
ጀምሮ ከእርሱ በጣም ብዙ መንፈሳዊ ስጦታዎችን
ተቀብለናል፡፡ ይህንን እግዚአብሔርን አውቆ
መከተልና አውቆም ማገልገል ሕይወታችንን
ያሳድገዋል፤ በእግዚአብሔርም ላይ ያለን
መተማመን ይጨምራል፡፡ በእኛ ዘንድ ያለው
ሁሉ በማወቅ የሚለው
አሳብ ልዩ
ትኩረት የሚሰጠው ነው፡፡ እግዚአብሔር በእኛ
ብዙ መልካም ነገሮችን አስቀምጧል፡፡ ከጌታ
ያገናቸው መንፈሳዊ ስጦታዎች
ክርስቶስን ወደ ማወቅ
እንድንደርስ የሚያደርጉን ናቸው፡፡ ስለዚህ
የቅዱሳንን ልብ የሚያሳርፍ አገልጋይ በክርስቶስ
ስላለው እውቀት
ግድ የሚለው ነው፡፡
6.
የቅዱሳንን
ልብ የሚያሳርፍ አገልጋይ ለክርስቶስ ክብር
ግድ የሚለው ነው፡፡
ፍልሞና
ሁሉንም ነገር ያደረገው ለክርስቶስ ነው፡፡
መንፈሳዊ ፍሬንም የሚያፈራው ለክርስቶስ
ነው፡፡ ጳውሎስ በአንተ ያለው ነገር ለክርስቶስ
ፍሬን እንዲያፈራ እለምናለሁ በማለት ለፍልሞና
የሚጸልየውን የጸሎት ይዘት ይገጻል፡፡
በአገልግሎታችን ፍሬን ብናፈራ ያ ፍሬ ክርስቶስን
ለማክበር መሆን አለበት፡፡ ሰዎችንም
በአገልግሎታችን የምናዘጋጀው ለክርስቶስ
ነው፡፡ ክርስቶስ በእኛ ሕይወትና ኑሮ በሚከብርብት
ወቅት የምናገልግላቸውና አብረውን ጌታን
የሚያመልኩ ሰዎች ልባቸው ያረፈ ይሆናሉ፡፡
ስለዚህ
ጳውሎስ ይህንን
አንቀጽ ሲደመድም ልቤን አሳርፍልኝ ይላል፡፡
ዛሬም ሰዎች ተጨንቀዋል፣
ፈርተዋ፣ተረብሸዋል፣ ግራም ተጋብቷል፣ምእናንም
በአገልጋችና በመሪዎች መካከል ካለው አላስፈላጊ
ሽኩቻ የተነሳ ተንገላትተዋል፣ ከቦታ ወደ
ቦታ ተንከራተዋል፣ ከአንዱ አበባ ተነስታ
በሌላው ላይ እንደምትቀመጥ ከዚያም ተነስታ
ወደሌላው አበባ እንደምትበር ንብ ተጉላልተዋል
፡፡ በመንፈሳዊ
ሕይወታቸው መጠንከር አልቻሉም፡፡ አማኞች
ሥር መስደድ ሲጀምሩ መሪዎችና መድረክ ናፋቂ
ሰባኪዎች ካሉበት ሥፍራ ያፈናቅሉአቸዋል፡፡
ከዚህም የተነሳ በመንፈሳዊ ሕይወት መጭብርብር
ውስጥ ገብተዋል ፣አያሌዎችም ለአውሬ ተጋልጠዋል፡፡
ይህ ሁሉ ሲሆን እኛ አገልጋዮች ስለ እነርሱ
ግድ አላለንም፡፡ ስለዚህ ቆም ብለን በማሰብ
የምዕመናኖቻችን ልብ ልናሳርፍ ይገባናል፡፡
ጳውሎስ ለፍልሞና የሚልከው ይህ መልእክት
ለአገልጋች ሁል ማነቂያ ደወል ነው ብዬ
አምናለሁ፡፡ የቅዱሳንን ልብ የሚያሳርፈውን
ማንነት እግዚአብሔር ይስጠን፡፡ አሜን፡፡