Thursday, January 28, 2016

እግዚአብሔር የተቀበለውን ልትፈርድበት አንተ ማን ነህ? ክፍል ሁለት


                     እግዚአብሔር የተቀበለውን ልትፈርድበት አንተ ማን ነህ?

ባለፈው ሳምንት የግብረሰዶማውያንና የሌስቢያንን ጋብቻ አስመልክቶ ሰዎች እግዚአብሔር በተቀበለው ላይ ልንፈርድ እኛ ማን ነን በማለት እንደሚከራከሩና ወደፊትም ክርክራቸውን አጠናክረው እንደሚገፉበት ተነጋግረን ነበር ያቆምነው፡፡ መነሻውን ከአሜሪካ ያደረገው የግብረሰዶማዊትና የውርጃ ሕጋዊነት ቀስ በቀስ ወደ አዳጊ አገሮችም እየተዛመተ በመሆኑ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን የሚገጥማትን ተግዳሮት ለመመከትምን ልታደርግ ይገባታል በሚል አሳባችንን በእንልጥልጥል እንደተውነው ይታወሳል፡፡ ወደ ተነሳንበት አሳብ እንመለስና ውይይታችንን እንቀጥል፡፡ እግዚአብሔር ግብረሰዶማውያንን ከተቀበለ እኛ ለምን እንፈርድባቸዋለን የሚለው አባባል አንድ ነገር አስታወሰኝ፡፡ አንድ ክርስቲያን በሠርጉ ላይ ሰዎች መንፈሳዊ መዝሙር ሲዘምሩ አብሮአቸው ሲዘምር ቆየና ከዘመዶቹ መካከል የክርስቲና ተቃዋሚ የሆኑት ስለሚበዙ መዝሙሩ ጋብ ባለበት ሰዓት ብድግ ይሉና ሠርግ ቤቱን በዘፈን ያናውጡታል፡፡ ያን ጊዜ ክርስቲያን የሆነው ሙሽራም ከእነርሱ ጋር ጭፈራውን ያነስካዋል፡፡ ያነ እነዚያ ዘፋኞች ኃይላቸውን ጨምረው በአንዴ ድንኳኑንና አካባቢውን በመቆጣጠር ሳያቋርጡ በመዝፈን የሚዘምሩ ክርስትያን ወገኖችን ጸጥ አሰኙአቸው፡፡ በሁኔታው የተደናገረ አንድ ወንድም በሠርጉ ማግሥት ሙሽራውን አንተ ክርስቲያን ስትሆን በሠርግህ ላይ እንዴት ዘፈን እየዘፈንክ ዓለማዊ ጭፈራ ትጨፍራለህ ብሎ ጠየቀው፡፡ ሙሽራውም ሲመልስ እግዚአብሔር ይክበርበት እንጂ አይደለም ዘፈን ሌላም በተገኘና ባደረግኩት ፡፡ እንዲያው አንተ እንዴት እግዚአብሔር እንደከበረና ክብርንም እንደገለጠ አላየህም እንዲዬ አለው፡፡
እግዚአብሔር ግብረሰዶማውያንን ከተቀበለ እኛ ለምን እንፈርድባቸዋለን የሚለው ጥያቄ ከዚሁ ጋር ተመሳሳይ ነው፡፡ ይህ በጣም መሰረታዊ ጥያቄ ነው፡፡ እግዚአብሔር የተቀበለውን ማን ሊፈርድበት ይችላል? ቃሉስ የሚለው ይህ አይደል? እግዚአብሔር ያጸደቃቸውን ማን ይከሳቸዋል? ይህንን ጥያቄ ይዤ ስለ ግብረሰዶማዊነት የቅዱሳት መጻሕፍትና የሥልታዊ ነገረ መለኮት ጥናት ምን ይላሉ የሚለውን ማሰብ ጀመርኩ፡፡ የክርስቲያን ፈላስፋዎች ከሆኑት ዊሊያም ኤል ግሬይግ እና ሌሎች የሚሉት አሳብ ግን መሠረታዊ ነው፡፡ እንደ ክሬይግ አባባል እግዚአብሔር የተቀበለውን ልንፈርድበት እኛ ማን ነን የሚለውን ጥያቄ ከመመለሳችን በፊት ሌላ ወሳኝ ጥያቄ መመለስ ይኖርብናል፡፡ ልክ የሆነና የተሳሳተ (right and wrong) የምንላቸው ነገሮች ስለ መኖር አለመኖራቸው አስቀድመን እንጠይቅና መልስ ልናገኝላቸው ይገባል፡፡ ይህ ልክ ነው ፣ ያ ደግሞ የተሳሳተ ነው ብለን ከመወሰናችን በፊት ልክ( right) የሆነውና ስህተት (wrong) የሆነው የትኛው እንደሆነ ለይተን ማወቅ ይኖርብናል፡፡ አንድን ነገር ልክ ነው ወይም ስህተት ነው የምንለው ምንን መሠረት በማድረግ ነው? ልክ በሆነውና በተሳሳተው መካካል ያለው ልዩነትስ ምንድነው? በተለምዶም ቢሆን እንደሚነገረው የግብረገባዊ እሴት ( moral values) መሠረቱ እግዚአብሔር ነው፡፡ እግዚአብሔር በባሕሪዩ ቅዱስ ነው፣ መልካም ነው፡፡ እርሱ ጻድቅ፣ አፍቃሪ ፣ታጋሽ፣መኃሪና ቸር ሲሆን መልካም ነገር ሁሉ ከእርሱ የሚገኝ በመሆኑ የእርሱ ባሕሪያት ነጸብራቅ ነው፡፡ ፍጹም መልካም የሆነው የእግዚአብሔር ባሕሪይ እኛም መልካምን እንድናደርግ ያዘናል፡፡ ለምሳሌ ቅዱስ ቃሉ ጌታ አምላክህን በፍጹም ልብህ በፍጹም ነፍስህ በፍጹም አሳብህ ውደድ፣ ባልንጀራህንም እንደራስህ ውደድ፣ አትግደል ፣ አትስረቅ አታመንዝር የሚሉና ሌሎች ትዕዛዞችን ይሰጠናል፡፡ እነዚህ ትዕዛዞች እንዲያው ዝም ብለው ግምድል አሳቦች ሳይሆኑ ፍጹም ከእግዚአብሔር ከራሱ ባሕሪይ የሚመነጩ ትእዛዞች በመሆናቸው አንድ ነገር ልክነው ወይም የተሳሳተ ነው የምንለው እግዚአብሔር በሰጠው ትዕዛዛት ላይ በመመሥረት መሆን አለበት፡፡ ክርስቲያኖች ልክ የሆነውንና የተሳሳተውን ነገር የምንረዳው በዚህ መንገድ ነው፡፡ ዓለማትን ሁሉ የፈጠረና ራሱን ለእኛ የገለጠ ታላቅ አምላክ አለ፡፡ ይህ አምላክ እኛ አንዳንድ ነገሮችን እንድናደርጋቸውና ሌሎችን ደግሞ እንዳናደርጋቸው አዝዞናል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ የሰጠንን ትዕዛዝ ሁሉ እንድናከብረው ግረገባዊ ግዴታ moral obligation አለብን፡፡ ትዕዛዙን የተላለፍን እንደሆነ ደግሞ ጥፋተኞች ስለምንሆን በፊቱ ይቅርታ መጠየቅና ምህረት እንድናገኝ ያስፈልጋል፡፡
እኛ ጥፋተኞች የምንሆነው የጥፋተኝነት ስሜት ሲሰማን ሳይሆን የእግዚአብሔርን ህግ ተላልፈን ስንገኝ ነው፡፡ ሕጉን ከጣስን በኋላ የጥፋተኝነት ስሜት ባይሰማንም እንኳ ጥፋተኞች ነን፡፡ ምክንያቱም ጥፋተኝነት ወይም ጥፋተኛ አለመሆን የሚወሰነው እግዚአብሔር በሰጠን ሕግ መሠረት እንጂ በሚሰማን ስሜት አይደለም፡፡ ለምሳሌ ዊልያም ኤል ክሬግ ይህንን አሳብ በምሳሌ ሲገልጸው እንዲህ አለ፡፡ በሁለተኛው ዓለም ጦርነት ጊዜ ድል የቀናቸው ናዚዎች ከአሳባቸው ጋር የማይሰማሙትን አስተሳሰብ የማሰለወጥ ካልሆነ እንደዚያ ያለውን ጨርሶ በማጥፋት ሁሉም ሰው በአይሁዶች ላይ የተረደገው ጭፍጨፋ ( Holocaust) መልካም እንደሆነ እንዲያስብ የሚደርጉት ተግባር ተሳካላቸው፡፡ ይሁን እንጂ ድርጊቱ አሁንም ቢሆን ስህተት ነው ምክንያቱም ሰው እንዴትም ቢያስብ እግዚአብሔር ግን ስህተት ብሎታልና”፡፡ ግብረገባዊነት የሚደላደለው በእግዚአብሔር ስለሆነ አንድ ልክ የሆነ ነገር ልክ መሆኑና ስህተትም ስህተት መሆኑ በሰዎች አስተሳሰብ ምክንያት ሊቀየር አይችልም፡፡
ኪሬይግ በጉዳዩ ላይ ይህንን ዓይነት አጽንኦት የሚሰጥበት ምክንያት በማህበረሰባችን መካከል አብዛኛዎች ሰዎች ትክክል( right) ወይም ስህተት ( wrong ) ስለሆነው ነገር የሚያስቡትና የሚበይኑት ከእውነት አንጻር ሳይሆን ከልምዳቸው ወይም ከሚሰማቸው ስሜት አንጸር ስለሆነ ነው፡፡ ለምሳሌ በዘፈን እግዚአብሔር እንደሚከብርና ክብሩንም እንደሚገልጥ ሙሽራው የተረዳው እንዴት ነው? በአብዛኛው አንድ ነገር ሞቅ ደመቅ ሲል የእግዚአብሔር ክብር ወረደ እንላለን፡፡ ይህ የራሳችን ልምምድ አንጂ በሞቀና በደመቀ ነገር ሁሉ ውስጥ የእዚአብሔር ክብር ስለመገለጡ እርግጠኖች ሆነን አይደለም፡፡ ሙሽራውም እግዚአብሔር ደስ መሰኘቱንና ክብሩን መግለጡ የሚታወቀው መዝሙሩ፣ ጭብጨባው እና እልልታው ሽብሽባውም ምድሩን ሲያናውጥ እንደሆነ የለመደው ነገር ነበረው፡፡ አሁን ግን ሲያየው ከመዝሙሩ ይልቅ በጣም ያየለው ዘፈኑ ሲሆንበት እዚያ ውስጥ ነው እንግዲህ እግዚአብሔር የሚከብርበት ብሎ ደመደመ ማለት ነው፡፡ ግብረሰዶማውያንንስ እግዚአብሔር እንደተቀበላቸው በምን እርግጠኞች እንሆናለን? ፍርድ ቤቱ ስለፈቀደና እነርሱም በጣም ሞቅ ብሎአቸውና ነካ አድርጎአቸው መንገድ ላይ ወጥተው ስለጨፈሩ እንዲሁም በጣም ሀብታሞች ስለሆኑ እግዚአብሔር ተቀብሎአቸዋል ማለት ነው? ይህም ቢሆን የሰዎች ስሜት ወይም ልምምድ የወለደው መሳሳት እንጂ እውነቱ ይህ ሆኖ አይደለም፡፡
ስለዚህ የአንድ ነገር ትክክለኛነት ወይም ትክክለኛ አለመሆንን ለመበየን መለኪያ ያስፈልጋል ፡፡ ያለዚያ ብያኔው አንጻራዊ ይሆናል ማለት ነው፡፡ ጎመን ለሁሉም ሰው ሊጣፍጥ አይችልም፡፡ ለአንዳንድ ሰው በጣም ይጣፍጠዋል ለሌላው ደግሞ አይጠፍጠውም፡፡ አንዲት ሴት የሠራችው ጎመን ለእኔ በጣም ሲጣፍጠኝ ጓደኛዬ ደግሞ ጭራሽ እንደሚያስጠላው ሁሉ ሰዎች የግብረገባዊ ሕጉን እንደዚሀው ያዩታል፡፡ አንድ ነገር ለአንዱ ልክ ሆኖ ያው አንዱ ነገር ደግሞ ለሌላው ሰው የተሳሳተ ከሆነ እውን የሆነ ልክ የሚባል ወይም እውን የሆነ ስህተት የሚባለ ነገር የለም ማለት ነው ምክንያንቱ ብያኔው አንጻራዊ ስለሆነ ነው፡፡ ለምሳሌ ግብረሰዶምነት ምንም ችግር የለበትም፣ ውርጃም ኃጢአት አይደለም የሚሉ በጣም ብዙ ሲሆኑ የውርጃን ወይም የግብረሰዶምነት ትክክለኛነት የሚመዝነበት መለኪያ ( standard) ኖሮአቸው ሳይሆን ከሚሰማቸው ስሜት በመነሳት ብቻ ነው፡፡ ለሌሎቻችን ደግሞ ያ ነገር ፍጹም ኃጢአት ነው አልፎም ርኩሰትም ሰይጣናዊነትም ነው፡፡ በዚህ መካከል የሚዳኘን ኃይልና እርሱ የሚሰጠን መለኪያ ያስፈልጋል፣ ያውም የእግዚአብሔር መኖርና ዘመን ተሻጋሪ የሆነው የእርሱ ሕግ ናቸው፡፡
እንግዲህ ለሰው ልጆች ሕግን የሰጠው እግዚአብሔር ባይኖር ሁሉም ነገር አንጻራዊ ነው ማለት ነው፡፡ በተለያየ ባህልና ህብረተሰብ መካከል የአንድ ነገር ትክክለኛነቱ ወይም ስህተት የመሆኑ ጉዳይ አንጻራዊ ነው፡፡ እግዚአብሔር ከሌለ ፍጹም የሆነ ሕግ የለም ማለትነው፣ ስህተት ወይም ትክክል የምንለው አንድም ነገር አይኖርም ማለት ነው፡፡ እያንዳንዱ የሚያደርገው ነገር እንደየራሱ አንጸራዊ ነው ማለት ነው፡፡ ያለ እግዚአብሔር ሕግ የአንድ ነገር ፈይዳው ልክ ነው ወይም የተሳሳተ ነው የሚል የለም፡፡ ልክ ወይም ስህተት የምንላቸው ነገሮች ራሳቸው የመጡት ከየት ነው? ልክን ልክ ወይ ስህተትን ስህተት የሚደርገው እግዚአብሔር የሰጠን መለኪያ (standard) ነው፡፡ ያው የእግዚአብሔር ቃል ነው፡፡ የእግዚአብሔርን ቃል ማመን አለማመን፣ ለእርሱ መገዛት አለመገዛት ሌላ ጉዳይ ነው፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔር ቃል ኃጢአት ያለው ምን ጊዜም ኃጢአት ነው፡፡ ጽድቅ ነው ያለውም እንደዛው ጽድቅ ነው፡፡
ታዲያ ከዚህ አንጻር ይህ መለኪያ ( ስታንዳርድ) ስለ ግብረሰዶማዊነት ምን ይላል? ስለውርጃስ? እንመለስበታለን፡፡

እግዚአብሔር በተቀበለው ላይ ልትፈርድ አንተ ማን ነህ?



እግዚአብሔር በተቀበለው ላይ ልትፈርድ አንተ ማን ነህ?


ሰሞኑን በአሜሪካን አገር የሁለተኛ ደረጃ ትምህርቱን በመከታታል ላይ ያለ ወጣት ተማሪ አስቸጋሪ በሆነ አንድ ጉዳይ ጓደኞቹን ሲሞግታቸው ሰማሁ፡፡ ጉዳዩ ስለ ተመሳሳይ ጾታ መሳሳብ ሲሆን ወጣቱ ደግሞ እግዚአብሔር ግብረሰዶማውያንን ከተቀበላቸው እኛ ለምን እንኮንናቸዋለን እያለ ነበር ጓደኞቹን የሚሞግታቸው፡፡ ይህ ልጅ ብቻ ሳይሆን የአሜሪካን ጠቅላይ ፍርድ ቤት የተመሳሳይ ጾታ ጋብቻን ከፈቀደበት ወርሃ ነሐሴ 2015 ወዲህ የጉዳዩ አነጋጋሪነትና አወዛጋቢነት በሁሉም ዘንድ እየጨመረ መጥቷል፡፡ ሕጉ በፍርድ ቤት እንደ ጸደቀ ፕሬዝዳንት ባራክ ኦባማ ወዲያውኑ ለመላው አሜሪካን ሕዝብ ባሰሙት ንግግራቸው “የዛሬው ቀን ወደ እኩልነት ለምናደርገው ጉዞ ወሳኝ ነው፡፡ ግብረሰዶማውያንና ሌስቢያውያን እንደ ማንኛውም ሰው የመጋባት መብት ያገኙበት እለት ነው፡፡ ፍቅር ያሸንፋል” በማለት በተለይም የግብረሰዶማውያንን አንጀት አርሰዋል፣ የብዙዎቻችንንም ቆሽት ደግሞ አሳርረዋል ፡፡ የፍርድ ቤቱን ውሳኔና የፕሬዝዳንቱን ንግግር ተከትለው ግብረሰዶማውያን የደስታ ድምጸቸውን ማሰማት ጀመሩ፣ወዲያውኑ ቀስተ ደመና መሰል ባንድራ በአንዳንድ ቤቶች ላይ መስቀል ተጀመረ( እዚህ ቤት የምንኖረው ግብረሰዶማውን እንደሆንን ይታወቅልን እንደማለት)፡፡ በመንገድ ሲሄዱም ይህ ባንድራ ያለበትን ወይም መሰል ልብሶችን እና፣ ወይን ጠጅ ቀለም ( ፔርፕል) የበዛበትን አልባሳትን በማድረግ የራሳቸውን ልዩ መለያ ለሕዝብ ሁሉ ማሳየት ጀመሩ፡፡ ለመጋባት የተጫጩ ጌዬዎች(ግብረሰዶማውያን) በአደባባይ መሳሳሙን ተያያዙት፡፡ ተደብቀው ሲያደርጉት የነበረውን የአገሪቱ ሕጉ ከፈቀደላቸው ዕለት ጀምሮ ይፋና አዋጅ አደረጉት፡፡ እንዲያውም “የእኛ ይሻላል ከሌላ” የሚሉ መሰሉ፡፡
በአንጻሩ ደግሞ የጠቅላይ ፍርድ ቤቱ ውሳኔ እጅግ ያስደነገጣቸውና ያሰቆጣቸው ቁጥር ሥፍር የሌላቸው ናቸው፡፡ አንዳንዶች የተቃውሞ ድምጻቸውን አሰምተዋል፣ በውሳኔው ላይ ምንም ለውጥ ማምጣት ባይችሉም እንኳ፡፡ የቢሊግሪሃም ወንጌል አገልግሎት ማህበር ፕሬዝዳንት ታዋቂው አሜሪካዊ ወንጌላዊ ፍራክሊን ግሪሃም ፣ ዶር ጆን ማካርተር ፣ ዶር ጆኤል አር ቢኪ እና ሌሎችም በርካታ ታላላቅ የእግዚአብሔር ሰዎችም ግብረሰዶማዊው ጋብቻ ኃጢአት መሆኑንና የጠቅላይ ፍርድ ቤት ውሳኔ ለምድሪቱ የእግዚአብሔርን ቅጣት የሚያስቸኩል መሆኑን በጉባኤያቸውም አስተምረዋል በአገሪቱ መገናኛ ብዙሐንና በማህበራዊ ገጾችም አውጀዋል፡፡ አሳዛኙ ነገር ግን በግብረሰዶማዊው ጋብቻ ላይ ለዘብተኛ አቋም የያዙ ብቻ ሳይሆን ሌሎች በመጽሐፍ ቅዱስ እውነት ያምናሉ ከምንላቸው አብያክርስቲያናትም ይህን ጋብቻ የሚፈቅዱ መበራከታቸው ነው፡፡ ይህ ሁኔታ ለወንጌላውያን አማኞች የባሰ አስደንጋጭ ሆኗል፡፡ እንዲያውም አንዳንዶቹ ይህ እንደማንኛውም ጋብቻ ስለሆነ ተጋቢዎቹን የምትኮንኑት እናንተ እነማናችሁ፣ እኛስ ምን መብት አለን፣ መፍረድ የሚችለው እግዚአብሔር ነው፡፡ እግዚአብሔር ደግሞ ፍቅር ነው እያሉ የሚሰብኩ እየተበራከቱ ናቸው፡፡ ወጣቱ ተማሪም ጓደኞቹን የተገዳደራቸው ይህንን ስብከት ስለማ እንደሆነ መጠራጠር አያስፈልግም፡፡ የግብረሰዶማውያንን ጋብቻ አልቀበልም፣ ለሠርጋቸውም ኬክ አልጋግርም፣አዳራሽም አላከራይም ያሉቱ ለእሥር መጋለጣቸው ታይቷል፡፡ የግብረሰዶማውያንን ጋብቻ በቤተክርስቲያኔ አላስፈጸምም፣ በጋብቻቸው ምስክር ወረቀትም ላይ ፈርሜ አልሰጣቸውም የሚሉ የቤተክርስቲያናት መጋቢዎች የኬንታኪው የሩዋን ክፍለ ከተማ ጸሐፊ ኪም ዴቪስ እጣ ሊደርስባቸው እንደሚችል ከወዲሁ ሁኔታው ያመላክት ነበር፡፡ የወጣቱን አቀራረብ ካየሁና ከሰማሁ በኋላ ወንድም ዘላለም መንግሥቱ ሊገጥመን ያለውን ፈታኝ ሁኔታ ሲገልጸው “ድጣማ ዳገት” ማለቱ ( ስንቶቻችን በልባችን እንዳኖርነው ባላውቅም) የበለጠ ገባኝ፡፡
ያ ወጣት ተማሪ እንዳደረገው የዛሬዋ እውነተኛ ቤተክርስቲያን ከምትጋፈጣቸው ከፍተኛ ጥያቄዎች አንዱ ግብረሰዶማውያንን እናጋባቸው ወይስ አናጋባቸው የሚለው ሲሆን ለዚህ ጥያቄ የሚሰጠውም መልስ ከወዲሁ ብዙ እያጋገረ ነው ፡፡ በግልጽ እንደምናየው የግብሰዶማዊነትን አኗኗር ዘይቤ ህጋዊ ነው ብሎ የማይቀበል ክርስቲያን እንደአጥፊ፣ ግልፍተኛ ወይም እንደ ጠላት ሊቆጠር ነው፡፡ ለዘብተኛ በሆኑ ቤተ እምነቶች ብቻ ሳይሆን ቫንጄሊካልና ፔንቴኮስታል በሆኑትም ዳግመኛ የተወለዱ ከሚባሉት መካከል በተመሳሳይ ጾታ የሚሳሳቡ እንዲያውም መጋባት የሚፈልጉ መኖራቸው የቤተ ክርስቲያንን ጭንቀት በጣም ያገዝፈዋል፡፡ መጽሐፍ ቅዱስ ሙሉ በሙሉ የእግዚአብሔር ቃል እንደሆነ በሚያምንና በሚያስተምር ቤተ ክርስቲያን ግብረሰዶምነት ፈቃድ አግኝቶ ማየት ለብዙዎች የልብ ስብራት ነው፡፡ ዶር ጆኤል አር ቢኪ የጠቅላይ ፍርድ ቤት ውሳኔ በሰሙበት ሳምንት ለጉባኤያቸው ሲያስተምሩ “የጠቅላይ ፍርድ ቤትን ውሳኔ የሰማሁባትን ቀን እንደ ቀብር ቀን እቆጥራታለሁ፣ በህይወቴ አሳዛኝ ከምላቸው ቀናት አንዷ ናትና” ብለዋል፡፡ ዶር ቢኪ ለጉባኤታቸው ባዘነና በተሰበረ ልብ ሲናገሩ፡ “አሜሪካ ያደረገችው ነገር ምንም ጊዜ ሳይፈጅ በአዳጊ አገሮች ይተገበራል፣ የብልግና ፍልም፣ የአደንዛዥ እንክብልና ሌሎችን ለዓለም ሕዝብ አስተዋውቀናል፣ አሁን ደግሞ የግብረሰዶማውያንን ጋብቻ ፈቅደናል ስለዚህ ሌሎች የዓለም ሕዝቦች እኛን እየተከተሉ ያንን ሊያደርጉት ነው፡፡ ለልጆቻችን የምናስወርሰው መልካም ቁም ነገር እያጣን ነን” ብለዋል፡፡
ይህ እውነተኛ አባባል ነው፡፡ በኢትዮጵያ ባለች አንዲት ቤተ ክርስቲያን ዳግመኛ ተወልደዋል ተብለው ከሚታሰቡ፣ የደህንነት ትምህርት ተምረው የውሃ ጥምቀት ከወሰዱ በኋላ በአገልግሎት ከተሰለፉት መካከል ሁለት ወንዶች የወደፊት ሕይወታችንን አብረን በጋራ ለመምራት እንድንችል በጋብቻ ለመጣመር ተስማምተን በእግዚአብሔር ፊት እየጸለይን ቆይተናልና ቤተ ክርስቲያናችን ለጋብቻችን እውቅና ትስጥ የሚል ጥያቄ ይዘው ቢመጡ የቤተ ክርሰቲያን መጋቢ ምላሽ ምን ይሆናል? መቼም ብስል ከጥሬ ከሆነው የአሜሪካን ቤተ ክርስቲያን ዘመናዊ ልምምድና ከቴሌብዥን ስብከታቸው የማይቀዳ ጉድ የለምና ጠያቂዎቹ ይህ ሰብዓዊ መብታችን ነው፣ ደግሞም እግዚአብሔር የእኛን ጋብቻ አልከለከለም ብለው ቢሞግቱ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ምን ልታደርግ ትላለች? ሰዎችን ከቤተ ክርስቲያን ታባርር ወይስ ትቀበላቸው? አንዳንዶች እግዚአብሔር ፍቅር ነው፣ ስለዚህ በፍቅር እንቀበላቸው የሚለውን ስብከት በመስበክ በመጽሐፍ ቅዱስ ተመሳሳይ ጾታ ግንኙነት ተወግዞም እንኳ ቢሆን መጽሐፉ በተጻፈበት ዘመን የነበረውን ባሕል ታሳቢ በማድረግ ሰለሆነ አሁን እኛን ከመጋባት አይከለክለንም እያሉ ቢፋለሙን ምን እናደርጋቸዋለን? እግዚአብሔር የተቀበላቸውን ልትኮንኑ እናንተ ማን ናችሁ የሚሉ ከዉጭ ሳይሆን ከውስጥ ያውም ከአገልጋዮች መካከል መነሳት ጉዳዩ ለቤተ ክርስቲያን እጅግ በጣም አደገኛ እንደሆነ ያሳያል፡፡ ወንድም ዘለለም “ድጣማ ዳገት” ያለውን ይህንን ችግር እንዴት ትወጣዋለች?
የአሜሪካን ጠቅላይ ፍርድ ቤት የተመሳሳይ ጾታ ሕጋዊነት ካጸደቀ በኋላ የኢትዮጵያ መንግሥት ደግም የውርጃን ሕጋዊነት ይፋ አድርጓል፡፡ ዜናውን ጃኑዋሪ 26 2016 ላይ ያወጀው የአሜሪካ ድምጽ ራዲዮ የአማሪኛው ፕሮገራም በይፋ ሲያሰማን የድጣማው ዳገት ጉዳይ እንደገና መታሰብ እንዳለበት ሁሉም ያሰላሰለ ይመስለኛል፡፡ አሜሪካንም እኮ የለስቢያንና የጌዬዎችን ጋብቻ ሕጋዊ ወደምታደርግበት አሳዛኝ ሁኔታ የደረሰችው ውርጃና መሰል ነገሮችን ስትፈቅድ ቤተ ክርስቲያናትም ከሥሯ እየተከተሉ ስቀበሉአት ቆይታ ነው፡፡ የኃጢአት ትንሽና ትልቅ ባይኖርም እንደ ሰው አበባል ከትንሹ ወደ ትልቁ ወይም ከዲጡ ወደ ማጡ እያለች እዚህ ደርሳለች፡፡ አገራችን ኢትዮጵያ ደግሞ ውርጃን በመፍቀድ የአሜረካንን የክህደትንና የሕገ እግዚአብሔር ጥሰት ተግባር በምድሪቱ ለመገንባት አጥልቃ እየቆረች መሆኗን እያሳየች ነው፡፡ ለግብረሰዶማዊው ጋብቻ እደርስበታለሁ አሁን ከውርጃው ልጀምር የምትል ትመስላለች፡፡ ይህ ለቤተ ክርስቲያናት ድንጋጤ የፈጠረ ይመስለኛል፡፡ በአሁኑ ዘመን ፖለቲከኞችና አንዳንድ እያዋዙ የሚወስዱ አጥቢ የቤተ ክርስቲያን ፓስተሮች በል ልበልህ፣ እከከኝ ልከክልህ የሚባባሉበት ሁኔታ ቤተ ክርስቲያንን እያደከማት ነው፡፡ አብዛኛዎቹ ነቢያትና በገንዘባቸው ቤተ ክርስቲያንን ለመምራት የሚሹ ሀብታም ነጋዴዎች አንዱ በአፍ ሌላው በእጅ ሲባባሉ እውነት ሰሚ እያጣች ነው፡፡ ያውም በቤተ ክርስቲያን ! ይህንን በዓይኑ ያየ ለእውነት የሚቀና ማንም መንፈሳዊ መሪ ማረሩና መድበኑ አይቀርም፡፡ ውርጃ እኮ የትውልድ ማጥፊያ ነው፡፡ የቤተ ክርስቲያንም ቀንደኛ ተግዳሮች ነው፡፡ የውርጃና የግብረሰደማውያን ጉዳይ ያን ያህል ወሽመጥ የሚቆርጥ የሆነበት ምክንያት በፖለቲካው አካባቢ ካሉ አማኞች መካከል አንዳንዶች ለጉዳዩ(ለውርጃና ለግብረሰዶማዊነት) ዘብ ስለሚቆሙላቸው ጭምር ነው፡፡ የትኛውም ይሁን የቱ ታዲያ የኢትዩጵያ ቤተ ክርስቲያናት መንፈሳዊ እሴታቸውንና ዘመን ተሻጋሪ የሆነውን የእግዚአብሔርን ቃል ከመጠበቅ አንጻር ምን እየሠሩ ነው? ምንስ ማድረግ ይገባቸው ነበር የሚለውን ለማንሳት ነው፡፡ እንመለስበታለን፡፡