Thursday, April 6, 2017
እንጀራው
በዚህ ሳምንት እኔና ውድ ባለቤቴ የወር አስቤዛችንን ( ቀለባችንን ማለቴ ነው) ለመሸማመት ከመኖሪያ ቦታችን ትንሽ ራቅ ብሎ ወደሚገኘው ገበያ አዳራሽ ሄድን፡፡ የገበያ ቦታው ሜድቴራኒያን ፉድ ማርኬት Mediterranean food market ተብሎ የሚጠራ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ከሌሎች ገበያ አዳራሾች ሁሉ ይልቅ ይኸኛውን አዘውትረው የሚጎብኙበት ትልቁ ምክንያት የአበሻ ምግብ ለመሥራት የሚያስችሉ ቅመማቅመሞች በየዓይነቱ ስለሚገኙበት ነው፡፡ ለምሳሌ ፡ በርበሬ፣ ኮረርማ፣ እርድ፣ ቀረፋ ፣ ጥቁር አዝሙድ፣ ምጥምጣ፣ ቡና፣ ወዘተ ሁሉም በየዓይነቱ ይሸጥበታል፡፡ ቅመሞቹ በትናንሽ ብልቃጦች እየታሸጉ በላያቸው ላይ ምንነታቸውን የሚያሳይ ጽሑፍና መለያ ቁጥር ከታተመባቸው በኋላ በተመደበላቸው መደርደሪያ ላይ በተርታ ተደርድረው ይገኛሉ፡፡ እንዲያው ባንገዛቸውም እንኳን እነዚያን ማየት ለዓይን ምግብ ነው፡፡ ታዲያ በአገር ቤት ሳለን እንደነበረው በትንሽ ብር ፌስታል ሞልቶ መመለስ ያለ እንዳይመስለን አደራ፡፡ በአንዲት ትንሽ ብልቃጥ የታሸገችው በርበሬ ዋጋ አይቶ በአገራችን ገንዘብ ካሰሉት ዋጋው ያስደነግጣል፡፡ ስለዚህ አንድ ነገር ለመግዛት ሲታሰብ በአገር ቤቱ ገንዘብ ማስላት አይታሰብም፣ ማስላቱም ተገቢ አይደለም፡፡
የአሜሪካኖች ምግብ በአጭር ጊዜ ውስጥ ያልታሰበ ቦርጭ እያሸከመ ስለሚያስቸግር ከዚህ ሁሉ እዳ ውድም ቢሆን የአገራችንን ምግብ ለምን አልበላውም በሚል እዚህ አገር ከገባንበት ጊዜ ጀምሮ ሽሮና እንጀራ ተለይቶን አያውቅም፡፡ ለታናሽ ልጃችን ፌቬን ደግሞ የአሜሪካኖች ምግብ ተመራጭ ብቻ ሳይሆን ከተመራጭ በላይ ነው፡፡ አልፈ አልፎ እንገዛላታለን እኛም የምንቀማምሰው በእርሷ ምክንያት ነው፡፡ ከፈቀድንላትማ ያለ እርሱ ባትበላ ደስታውን አትችለውም፡፡ እውነት መናገር ይሻላል የአሜሪካኖች ምግብ ሲጣፍጥ አይጣል ነው፡፡ ቢሆንም የሽሮን ውለታ መርሳት ጥሩ አይደለም ብለን ስለመከርናት እግዘር ይስጣትና እሺ ብላ ከእኛ ጋር የአበሻውን ምግብ በሥነሥርዓት እየበላችው ነው፡፡ ከምግብ ሁሉ ታማኝና ባለውለታችን ሽሮ ነው፡፡ መሸለም ቢያስፈልግ በመጀመሪያው የክብር መዳሊያ መጥለቅ ያለበት በሽሮ አንገት ነው፡፡ አንድም ቀን ሰልችቶን አያውቅን ፣ እኛም አንሰለቸውም፡፡ ይኸውና ሽሮአችን ባሕር ተሸግሮ በመምጣት የተለመደ አገልግሎቱን እየሰጠን ነው፡፡ ባለቤቴ ተዋበች ሌላ ማንኛውንም ምግብ ብትበላ እንጀራ ካልቀመሰች የሆነ ነገር የሚጎድልባት ይመስላታል፡፡ በፌቬንና በእርሷ መካከል ያለው ልዩነት በጣም ሰፊ ነው፡፡ እኔ ባለቤቴን አልፌ አልፎ እመክራታለሁ፡፡ ታበዥዋለሽ እላታለሁ፡፡ እምቢ ስትለኝ “ቃሉ ሁሉንም በልክ አድርጉ ይላል” ብዬ ልሰብካት ብሞክር የቱጋ ነው የጻፈው ትለኛለች፡፡ የተጻፈ ነገር ካለ ንገረኝ እንጂ ያልተጻፈውን አታንብብ ትለኛለች፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ አጠናን ዘዴ ውስጥ “አውድ” የሚባል ነገር መኖሩን በሰበብ በአስባቡ የነገርኩአትን ይዛ “አውድ ጠብቅ” እያለች ወደ እኔ ታነጣጥርብኛለች፡፡ በገዛ እጄ ስለ አውድ ነግሬአት ራሴው አፍ አጣሁ፡፡ እንዲያውም የእንጀራና የቡና ፍቅር እየባሰባት መሄዱን ሳይ “ይህ የእንጀራ ፍቅር በዝቷል፣ ወደ ሰማይም ሄደሽ እንጀራ እበላለሁ እንዳትይ እዚያ እንጀራ የሚባል ምግብ አይኖርም ይልቁንስ የተሻለና ከሁሉም የላቀ ሕይወት ነው የሚጠብቀን እንጂ” እያልኩ ሊሰብካት ቢሞክር አሁንም “ይህ ትምህርት ከእውነተኛው አስተምህሮ ጋር ስለጣጣሙ እርግጠኛ ሁን እንጂ እኔ መንግሥተ ሰማይ ሄጄ እንጀራ አልጋግርም የሚጋግርልኝም ይኖራል ብዬ አላስብም” ትለኛለች፡፡፡ ባለቤቴንና ልጀቼን ይህንን አታድርጉ ብዬ በቃል ጥቅስ ከመገሰጼ በፊት አውዱን በጥንቃቄ የመመልከት ግዴታ ውስጥ ገብቻለሁ፡፡ ያውም እኔው ራሴ አውድ context ስለሚባል ነገር ነግሬአቸው ያመጣሁት መዘዝ ነው፡፡ እኔ የሚቀለኝና ነጻነት የሚሰማኝ በመነቃቂያ ኮንፍራንስ ስሰብክ ነው፡፡ እዚያ ከየት አመጣኸው የሚል የለም፡፡ የተሳሳተም ቢሆን ተናግረው አሜን በሉ ሲባል አሜን የሚባልበት ቦታ ነው፡፡ እኔ እዚያም ቢሆን አውድ እጠብቃለሁ እንጂ ምክንያቱም ወደ ቤት ስመለስ ባለቤቴ “እሺ የዛሬው አገልግሎት እንዴት ነበር ታዲያ?" ብላ ሳትጠይቀኝ አልፋ አታውቅም፡፡ እኔም ‘ጌታ ይመስገን በጣም ጥሩ ነበር” እላታለሁ፡፡ እዚያጋ ቢያበቃ መልካም ነበር ግን አያበቃም፡፡ “ስለ ምን ሰበክ?” የሚለው ጥያቄ ይከተለኛል፡፡ ይህን ጊዜ ከስብከቴ መካከል ደግ ደጉን መርጬ በጥንቃቄ እነግራታለሁ፡፡ ባለቤቴ አገልግዬ ስመለስ በጥያቄ ማጣደፍ ብቻ ሳይሆን በጌታ የተሳካ የስብከት አገልግሎት እንዳቀርብ አጥብቃ ትጸልይልኛለችና ስለ እርሷ ጌታን አመሰግናለሁ፡፡ ታዲያ በእኔ ቤት መንፈሳዊ ነጻነት ፣ በነጻነት መስበክ፣ ጥቅስ እየጠቀስኩ አንዱን ከአንዱ ጋር አገናኝቼ ማሳመን በቀላሉ እልሆን እያለ መጥቷል፡፡ በመሆኑም ደስተኛ ነኝ፡፡ ባለቤቴንና ልጆቼን እግዚአብሔር ስለሰጠኝ ምስጋናዬም የላቀ ነው፡፡
ባለቤቴ ቡናንም ስትወድ አይጣል ነው፡፡ እኔ ደግሞ ቡና አልጠጣም፡፡ ጧትና ማታ ቡና ካላፈላሽ እያልኩ የማስቸግር ባል ባለመሆኔ ራሱ ልታመሰግነኝ ሲገባት “ባትጠጣ ሙሉ መብት አለህ፣ ማንም በግድ ጠጣ አይልህም፣ ደግሞ ብትጠጣም ችግር የለውም ለራሴ ሳፈላ እግሬ መንገዱን ትጠጣለህ” ትለናለች፡፡ይህ እኮ በእኛ ቤት የሴቶች እኩልነት ብቻ ሳይሆን የሴቶች የበላይነትም መኖሩንም ያሳያል፡፡ አሁን አሁን በተለይም ወተት በቡና የሚባለውን በትንሽ በትንሹ ስትሰጠኝ ቀየችና ለእኔ በማይገባኝ ሁኔታ የቡናውን መጠኝ ከቀን ወደ ቀን በዛ እያደረገች ምን አለፋችው በቡና ሱስ አስያዘቺኝ፡፡ አሁን በቁጥጥሯ ሥር ገብቻለሁ፡፡ በአገሬ ሳለሁ ለቡና ሱስ ያልተንበረኩ ሰው አሁን ከምሳ በኋላ ያቺን ወተት በቡና የምትለዋን ካልጠጣሁ ይደክመኝ ጀመረ፡፡
ለማንኛም እኔና ባለቤቴ ወደ ሜዲትራኒያን ገበያ አዳራሽ የሄድነው ጤፍ፣ ገብስና ቡና ለመግዛት ነው፡፡ እዚያ የኢትዮጵያ ቡናም አለ፡፡ባለቤቴ የምትፈልገውን ዕቃ እየመረጠች በጋሪው ላይ ስታስቀምጥ የእኔ ሥራ ጋሪውን እየገፋሁ ከኋላዋ መከተል ነው፡፡ እርሷ የመረጠችውን ብቻ ነው እንጂ የእኔ ምርጫ ውሃ አያነሳም፡፡ ከኋላዋ ሆኜ ያንን ጋሪ እየገፋው እያለ ዓይኔ በአንድ ነገር ላይ አረፈ፡፡ ከፊት ለፊታችን ባለው ጠሬጴዛ ላይ በሚያምር ንጹሕ ላስትክ ታሽጎ የተደረደረ ደስ የሚል ነገር፡፡ ምግብ ነው ታዲያ! ገበያተኞች አንዱ ከሌላው እየተከተሉ የሚያነሱት፡፡ ገበያ አዳራሹ የዐረቦች በመሆኑ ምክንያት ብዙ ዐረቦች ይገበዩበታልና እነርሱም ያንን ሲያነሱ አየሁ፣ ሶማሊያውያንም ፣ ሱዳናውያንም በየተራ እየመጡ ሲወስዱ አየሁ፡፡ እኔም ተጠጋሁና አይቼ ልቤን ደስ አለው፡፡ ለባለቤቴ አሳየሁአት፣ አየሽው ይህንን ነገር አልኩአት፡፡ ለካ እርሷ ከእኔ በፊት አይታዋለች ግን እንደ እኔው አልገረማትም፡፡ ነገሩ እንጀራ ነው፡፡ እንጀራ በዚህ ገበያ ሲሸጥ ከዚያም አልፎ ደግሞ ኢትዮጵያውያን ያልሆኑትም ጭምር ተሻምተው ሲወስዱ አታይም እንዴዬ አልኳት፡፡ ያውም እኮ ነጭ ወረቀት የመሰለ እንጀራ እኮ ነው፡፡ የእንጀራ ፍቅር የባለቤቴን ያህል ባይሆንም እንጀራን እወደዋለሁ ፡፡ የአገሬ ምግብ እንደዚያ ሲሸጥ በማየቴ ኩራት ኩራት አለኝ፡፡ በአገራችን የነጭ ጤፍ እንጀራ የሚበላው ሀብታም ሰው ቤት ነው ፡፡ ይህ ደግሞ ከንጣቱ ጋር ልስላሴው ራሱ ብላው ብላው የሚያሰኝ ነው፡፡ ነገር ግን እንጀራ ወዳድ ባለቤቴ ያሳየችው ቸልተኝነት አንድ ጥየቄ እንድጠይቃት አደረገኝ፡፡ ይህንን እንጀራ አልወደድሺውም አልኳት፡፡ እርሷም መልሳ እንዲህ አለችኝ “እንጀራ ይመስልሃል? ይህ እኮ እውነተኛ እጀራ ሳይሆን ዱቄቱን ሳልፍራይዜር ከሚባል ኬምካል ካር ቀላለቅለው ስለሚጋግሩ የነጣው በዚያ ምክንያት ነው የለሰለሰውም ለዚያ ነው፡፡ እውነተኛ እንጀራ ግን እንደዚህ አይለሰልስም አይነጣምም፡፡ ይህኛው ሁለትና ሦስት ቀን እዚህ ቢውል አይደርቅም አይሰባበርም፡፡ እውነተኛው እንጀራ ግን ጠሬጴዛ ላይ እንደዚህ አይቀመጥም ፣ በልዩ ጥንቃቄ በኮባና በሌሎች ቅጠሎች ተሸፋፍኖ በእቃ ውስጥ ነፋስ በማይነካው መልኩ ይቀመጣል፣ ይህኛው እንጀራ ከኬሚካሉ የተነሳ ለጤና ጎጂ ሲሆን እውነተኛው ግን በጣም ጤናማ ነው፣ ጤፋችን ብረት በተባለ ንጥረ ነገር የበለጸገ ስለሆነ ለጤና ጠቃሚ ነው፣ አሁን እኔ የጤፉን ዱቀት ወስጄ ስጋግረው የሚወጣው እንጀራና ይህኛው እንጀራ በምንም ሊገናኙ አይችሉም” አለችና አስዳችኝ፡፡
ከዛ በኋላ ራሴን ጠየቅኩኝ እነዚያ ሰዎች ታዲያ እንጀራ እንጀራ እያሉ የሚሻሙት ለምንድነው አልኩ፡፡ መልሱ እውነተኛውን እንጀራ ስለማያውቁ ነው፡፡መለስለሱንና መንጣቱን እንጂ በማስመሰል የተሠራ የሀሰት እንጀራ መሆኑን አላውቁትም ማለት ነው፡፡ ሐሰት መሆኑን የምታውቀው ኢትዮጵያዊቷ ባለቤቴ የእውነተኛው እንጀራ ጋጋሪ ኢትዮጵያዊት ስለሆነች ነው፡፡ በመሠረቱ እንጀራ ከመነሻው የኢትዮጵያውያን ባህላዊ ምግብ እንጂ የዓረቦችም የሶማሊያውያንም አይደለም፡፡ የሱዳኖችም ምግብ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያውያን ምግብ ነው፡፡ ስለዚህ ኢትየጵያውያን ሐሰተኛውን እንጀራ ከእውነተኛው የመለየት ብቃት አላቸው፡፡ ሌሎች ግን ይህ ብቃት ስሌለላቸው በብረት የበለጸገውን የጤፍ እንጀራ ሳይሆን ኬምካል የተሞጀረበትን ነጭ እንጀራ ይበሉታል፡፡
ከዚህ የተማርኩት አንድ መንፈሳዊ ቁም ነገር አለ፡፡ ዛሬ በቤተ ክርስቲያን የሐሰት አስተማሪዎችንና የሐሰት ትንቢቶችን፣ ተአምራቶችን እንዲሁ በቀላሉ ልንለያቸው አንችልም፡፡ እውነተኛውን ትምህርት ካላወቅን በቀላሉ እንወሰድባቸዋለን፡፡ የሐሰት ትምህርቶች ይመርካሉ፣ ብዙዎች ይከተሉአቸዋል፣ ያደንቁአቸዋልም፡፡ ነገር ግን ከእውነተኛው ትምህርት ጋር ሲያስተያዩት ውስጣቸው በገዳይ መርዝ የተመላ ነው፡፡ እውነተኛው እንጀራ ዋጋው ውድ ሲሆን ሐሰተኛው ደግሞ ቀለል ባለ ዋጋ እንደሚገኝ ሁሉ የስህተት ትምህርትቶችና ትንቢቶች እንደ ልብ ይገኛሉ፡፡ ሐሰተኛውን ከእውነተኛው ለመለየት ቀላሉ መንገድ እውነተኛውን ትምህርት በሚገባ ማወቅ ነው፡፡ባለቤቴ ኢትዮጵያዊ በመሆኗ እውነተኛውን እንጀራ ስለምትጋግር ሱዳናውያንና ሶማሊውያን የሚገዙት ሳልፍራይዜር ያለበት እንጀራ እንደምግብም አልታይ አላት፡፡ እኔም ምስጥሩም ስለማላውቅ ልቤ በዚያ እንጀራ ተማርኮ ነበር፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ቤተ ክርስቲያን በሐሰት ትምህርትና በጤናማ ትምህርት፣ በሐሰት ትንቢትና በእውነተኛ ትንቢት ፣በሀሰት ተአምራትና በእውነተኛው ተአምራት መካከል ያለውን ልዩነት ምዕመናን ተረድተው በሐሰተኛው መርዝ እንዳይጠቁ እውነተኛውን ትምህርት በማስጨበጥ ልትተጋ ይገባታል፡፡ ፈጣሪ በቸርነቱ ይጠብቀን ይርዳንም ፡፡ አሜን
ረጅም ነኝ ግን ሰሞኑን ቁመቴ የማጠሩ ነገር ኣሳሰበኝ፡፡
ረጅም ነኝ ግን ሰሞኑን ቁመቴ የማጠሩ ነገር ኣሳሰበኝ፡፡
እኔ ስለራሴ የተረዳሁትና ሰዎችም የሚመሰክሩልኝ በጣም ረጅም እንደሆንኩ ነው፡፡ እንዲያውም በቤተሰባችን ብቻ ሳይሆን በተወለድኩበት አካባቢ እንደ እኔ ያለ ረጅም ሰው የለም ማለት እችላለሁ፡፡ ለቀበሌያችንና ለወረዳችን የመረብ ኳስ ስጫወት በጣም ነበር የማስደስተው፡፡ በቤተክርስቲያን ስናገለግልም መዘምራን በደረጃ ላይ ሲቆሙ እኔ ከፊት ባለው ደረጃ ላይ ከቆምኩኝ በሶስተኛ ደረጃ ላይ ከቆሙት ጋር እኩል እሆናለሁ፡፡ በኳየር አገልግሎት ጊዜ ከኋላ መቆም የማልፈልገው ጭንቅላቴ ኮርኒሱን ስለሚነካብኝ ነው፡፡ ስለዚህ ፊቴን ወደ ሌሎች መዘምራን አዙሬ ጎኔን ለጉባኤው ሰጥቼ ከዳር በኩል እቆማለሁ፣ ከዚያ መዘምራኑ ከያዙት ከየትኛውም ደብተር ላይ እያየው መዘመር እችላለሁ፡፡
ወደ ስብከት አገልግሎት ስገባ ከመዘምራን ተለየሁ እንጂ መዘምራን ሲያገለግሉ ደስ ይለኛል፡፡ የዛሬውን አያርገውና ኳየሮች የሚዘምሩት መዝሙር ለረጅም ጊዜ ከልብ አይጠፋም ነበር፡፡ በመከራም ቀን እንደ ትንቢት ቃል የቅዱሳንን ልብ ደግፏል፡፡ ለምሳሌ “ድሉ የጌታችን ነው ፣ድሉ የአምላካችን ነው ድሉ” የሚለውን መዝሙር የሰማሁት በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በ1973ዓ.ም ማለትም ከ36 ዓመት በፊት ነው፡፡ ሌሎችም በጊዜው የተዘመሩ መዝሙሮች አይረሱኝም፡፡ በጊዜው የወላይታ ቤተ ክርስቲያን በመራራ ስደት ውስጥ ሳለች የመሠረተ ክርስቶስ ቤክ መዘምራን ወደ ቦታው ተንቀሳቅሰው በ”ኦቶና” ዓመታዊ ኮንፍራንስ ላይ ሲዘምሩና ሕዝቡ አብሮአቸው በእምባ ሲራጭ እኔና እኩያዎቼ ከመድረኩ ፊት ለፊት በመሬት በተጎዘጎዘው ሣር ላይ እንድንቀመጥ አስተናጋጀች ስላስገደዱን እዚያው ሆኜ ነው የሰማሁት፡፡ ይህ መዝሙር ዛሬም ለእግዚአብሔር ሕዝብ ትኩስ መልእክት ያለው ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በመዝሙር የማገልገል ጥማት ውስጤ ገብቶ ስለነበር እስከአሁን አራት በሚያህሉ ኳየሮች አገልግያለሁ፡፡ ታዲያ መዘምራኖቹ በቁመቴ ብቻ ሳይሆን ድምጼም ዝማሬውን ስለሚያተራምስባቸው ይቸገሩብኝ ነበር፡፡ እኔም ከመዘምራን ጋር ባገለገልኩባቸው ጊዜያቶች ቅር ያለኝ ነገር ቢኖር አብሬአቸው ፎቶ መነሳቴ ነው፡፡ ከእነርሱ ጋር የተነሳሁአቸው ፎቶዎቼ አብዛኛዎቹ ወይ ከአንጌቴ፣ ወይ ከፍንጫዬ በላይ የላቸውም፡፡ ጌታ ኃጢአቴን ሁሉ ይቅር እንዳለኝ መጽኸፉ ስለነገረኝ እኔም ይቅር ብዬአቸው ነው እንጂ ያኔ ፎቶ ባነሱን ሰዎች ላይ ቂም ቢጤ ሁሉ ቋጥሬባቸው ነበር ፡፡አጫጭሮቹ ከእግራቸውም ከጭንቅላቸውም በሌንሳቸው እንዲገቡ ብለው እኔን ከአጭሮቹ ትክክል ቆርጠውኛልና፡፡
በቤተ ክርስያቲናችን የበረውን ትልቁን ፑልፒት አጫጭሮቹ ሰባኪዎች አይወዱትም ነበር፡፡ ያንን ፑልፒት ያስቀየረን አንዱ የእነርሱ ብሶት ነው፡፡ ፑልፒቱ ስለሚከልላቸው ከሥሩ ለእነርሱ ተብሎ የተዘጋጀ ኩርሲ አይነት ነገር ስላለ ሲሰብኩ እዚያ ላይ ይወጣሉ፡፡ ከዚያ እንደምንም ብለው ከደረታቸው በላይ ይታያሉ፡፡ ሊሰብኩ እዚያ ላይ ወጥተው "እታያለሁ?"ብለው ጉባኤውን የጠየቁ ሁሉ ነበሩ ብል ታምኑኛላችሁ? አሁን ብዙ ሲዘመር አልሰማውም እንጂ አንድ "መሸሸጊያ ዋሻ 2x መከታ ጋሻችን" የሚል ተወዳጅ መዝሙር ነበርና ከምንወዳቸው ሽማግሌዎቻችን አንዱ ይህን ምዝሙር እያዘመረ ጉባኤውን ሲመራ በተለይ መሸሸጊያ ዋሻ የሚለው ቃልጋ ሲደርሱ በዚያ ፑልፒት ሥር እየተደበቀና ከዚያም ብቅ እያለ ሲመራ ጥሩ ምሳሌ ይሆንለት ነበር:: ታዲያ ከመድረኩ ጫፍ ወደ ሌላው ጫፍ የሚሯሯጥ ሰባኪ ያ ፑልፒት አይመቸውም፡፡ እኔ ስሰብክ ግን ያንን ኩርሲ ስለማልፈልግ ወደ ጎን አሽቀነጥረውና መሬቱ ላይ ቆሜ እንኳ ጉባኤው ከደረቴ ሳይሆን ከወገቤ በላይ ያየኝ ነበር፡፡ አስቡ እንግዲህ! የቤተክርሰትያናችን አባቶች ቅጽል ስም ሁላ አውጥተውልኛል፡፡ በጣም የምናከብራቸው የነበረ ጋሼ ጥላሁን “ሰማይ ዛፉ” ፣ “ብቅል አውራጅ”፣ ይሉኝ ነበር፡፡ ጋሼ ወልደአምላክማ በስሜ ከሚጠሩኝ “ቀውሌ” ሲሉኝ ይቀላቸዋል፡፡ ጋሼ ማሞ ደግም ልክ እንደ ጋሽ ጥላሁን “ሰማይ ዛፉ” እንደሚሉኝ ልንገራችሁ፡፡ የማታውቁኝ ወገኖቼ ምን ያህል ረጅም እንደሆንኩ በዚህ ይግባችሁ ብዬ ነው፡፡
በረዶ ካልዘነበ በቀር አንዳድ ጊዜ ከባለቤቴ ጋር በእግር እንጓዛለን( ባለንበት አገር ዎክ ይባላል)፡፡ ታዲያ የምንጓዘው እያወራን ነው፡፡ ምን አለፋችሁ ባለቤቴ ቀስ ብላ የመናገር ባሕሪይ ስላላት እሷ የምትለው እኔጋ አይደርስም፡፡ እኔ ከላይ ሆኜ ስለምናገር እያንዳንዱን ነገር ትሰማለች፡፡ ስንቸገር ለምን እኔና አንቺ በስልክ አናወራም እላታለሁ፡፡ አብረን እየተጓዝን ወደ አንድ የገበያ አዳራሽ ስንደርስ እርሷ የሆነ ዕቃ እንግዛ ብላኝ ወደ ውስጥ ስንገባ ህንዳዊው የሱቁ ባለቤት አላየንም ነበር ግን ኮሜዲኖው አጠገብ ቆመን ስናናግረው በሆነ ወንበር ላይ የቆምኩ መስሎት አንገቱን አሰግጎ ወደ ጫማዬ አየኝና "በምን ላይ ቆመህ ነው ?" ያለኝ ቀን እንዴት እንደሳቅኩ ልነግራችሁ አልችልም፡፡ የሰውዬው አባባል በአዲስ አበባ ቦሌ ቃለ ሕይወት ቤክ አገልግዬ ስመለስ አንዲት የሀብታም ልጅ የምትመስል ከእናቷ ጋር ስትሄድ ነበርና በአጠገባቸው ሳልፍ አይታኝ እንደመሞላቀቅ አድርጎአት "ወይኔ ጂሴስዬ....ሰውዬው ምን ያክላ.....ል" ማለቷን አስታወሰኝ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ተቃራኒውም ይገጥመኝና አቤት የጌታ ሥራ እንዴት ግሩም ነው እላላሁ፡፡ ለአገልግሎት ሌላ ቦታ ካልሄድኩ በግራድ ራፒዲስ ከተማ ወደሚገኘው ካልቬሪ ቤተክርስቲያን ሄደን የጌታን ቃል እንሰማለን፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ ትልቅ ከመሆኑ የተነሳ ስድስት የሙጪያና የመግቢያ በሮች አሉት፡፡ አንድ ቀን ግን ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ስንገባ የመጀመሪያውን ፈረቃ ተካፍለው የሚወጣውና ሁለተኛውን ለመካፈል የምንገባው ሰዎች ዌስት ጌት (የምዕራቡ መግቢያ በር) በኩል ባለው በተላለፊያ ላይ ተገናኘን፡፡ ታዲያ በፈረንጆች አካባቢ ረጅም ሰውና ሽማግሌዎችን ማየት እንደ ልብ ስለሆነ እንደ እኛ አይገርማቸውም፡፡ ግን ያን ቀን የሚወጣው ሕዝብ ሲወጣ እኛ ደግሞ ስንገባ ከፊት ለፊቴ አንዲት ዕድሜዋ በግምት ከ25-30 ውስጥ የሚሆናት ወጣት ሴት በሕዝቡ መካከል ወደ እኛ አቅጣጫ ትመጣ ነበር፡፡ ከሰው ሁሉ ከፍ ብለን የምንታየው እኔና እርሷ ብቻ ነበርን፡፡ ግን ሆን ብላ ወደ እኔ መጣችና በአጠገበ አለፈች፡፡ ታዲያ ምን አለፋችሁ ወደ አናቴ ቁልቁል እያየችኝ ስታልፍ አንዱ ሽማግሌ ፈረንጅ ተክ ብሎ ሳቀ፡፡ አንተንም የሚበልጥ መኖሩን እወቅ የሚል ይመስላል፡፡
እኔም ይህንን ሁሉ የዘከዘኩት በቁመቴ ላዝናናችሁ ወይም ላስቀናችሁ አይደለም፡፡ ቁመቴ 6.5 ሃይት መሆኑ በህግ ተረጋግጦ በመንጃ ፈቃዴና በሌሎች ሕጋዊ ሰነዶች ላይ ሰፍሮ እያለ ሰሞኑን አጭር መሆኔ ሲነገረኝ ክው ብዬ ስለ ደነገጥኩኝ የሚያጽናና መልእክት ወይም ምክር ካላችሁ እንድትለግሱልኝ በማለት ነው እንጂ፡፡ አጭር መሆኔ የተነገረኝ ከሀኪም ወይም ከሌላ ባለሙያ አይደለም፡፡ ካለሁበት አገርም አይደለም፡፡ ከነቢያት አገር ከኢትዮጵያ ነው፡፡ አንድ ሰው በቫይበር ግሩፕ ፈጠረና እኔንም እዚያው ውስጥ አካቶኝ መልእክት ስለላከብኝ ማን አንደሆነና የእኔንም ስልክ ከየት እንዳገኘ እንዲነግረኝ መልእክት ላኩበት፡፡ ከዚያ በዚያው በቫይበር ደውሎልኝ ማእረጉን በማስቀደም ስሙን ነገረኝ፡፡ ስሙን ለጊዜው ላቆይና ወንድማችን በማዕረጉ ነቢይ ነው፡፡ ፕሮፌት …….. እባላለሁ ከኢትዮጵያ አለኝ፡፡ ማዕረግ ያልኩበት ምክንያት አሁን አሁን ወንጌላዊነት ፣ መጋቢነት ፣ ወይም ሓዋሪያነትና ነቢይነት ለአገልግሎት እንደተሰጠን የጸጋ ስጦታ ሳይሆን እንደ ማዕረግ ስለሚታይና ሰዎችም በዚያ ማዕረግ ካልተጠሩ ስለሚከፋቸው ነው፡፡ እንግዲህ አሳብ እየተለዋወጥን እያለ ጌታ ስላገናኘን አመሰገነና በሰዓቱ እግዚአብሔር ስለ እኔ የሚያሳየውን ነገር ስላለው ልነግረኝ ፈቃደናነቴን ጠየቀኝ፡፡ ፕሮፌት ነኝ ስላለ እና እኔም የነቢያትን አገልግሎት ስለማከብር ንገረኝ አልኩት፡፡ ብዙ ነገር ነገሮኝ ያንን ሁሉ በምልክት ሊያጸናልኝ ፈልጎ ማረጋገጫ በምልከት ይደረድርልኝ ጀመር፡፡ “አንደኛ፣ በ1996 ዓ. መጨረሻና በ1997 መግቢያ ላይ በሕይወትህ አንድ ነገር ሆኗል፡፡ ሁለተኛ፣ አንተ ጥቁር ሰማያዊ መኪና አለችህ፡፡ ሦስተኛ፣ በግራ እግርህ ከጉልበትህ በታኝ ቆስሎ የዳነ ምልክት አለብህ፡፡ አራተኛ አንተ ረጅም ሰው አይደለህም በቁመትህ ከአጭር ሰው ትንሽ ከፍ ትላለህ፡፡ ይህንን የምነግርህ እምነት እንዲሆንህ ነው አሜን በል፣ ” አለኝ፡፡ እኔም አሜን አልኩ፡፡ ለምን አሜን አልክ አትበሉኝ
ስለ ቁመቴ ማጠር ስሰማ በጣም ደነገጥኩ፡፡ መልሼ “እኔ እኮ በጣም ረጅም ሰው ነኝ፡፡ እንዲያውም ድሮ ከጋምቤላ አካባቢ መጥተው ለአየር ኃይል መረብና ቅርጫት ኳስ የሚጫወቱ ረጃጅም ሰዎች ነበሩ:፡ ወይም ከቦረና ነገሌ መጥተው በመረብ ኳስ ሜዳ ያገኘናቸው ሰዎች ካልሆኑ እሰከአሁን በቁመት የሚያክለኝ ሰው አልገጠመኝም፣ አንተ ደግሞ ከአጭር ሰው ትንሽ ከፍ እንደምል ትነግረኛለህ፡፡ ነገሩ እንዴት ነው?” ስለው፣ “እንግዲህ እኔ የማውቀው ነገር የለም ጌታ ያሳየኝ ይህ ነው” አለኘኝ፡፡ የቁጣ መልስ ስለመሰለኝ ጨዋታችንን እዚውጋ አበቃን፡፡ ደግሜም ያንን ሰው አላገኘሁትም፡፡
ታዲያ ምን አሳሰበህ የሚል ቢኖር ከላይ በተጠቀሱት ዓመታት በሕይወቴ የሆኑ ብዙ ነገሮች ነበሩና ትክክል ነው ብዬ ተቀበልኩ፡፡ በእግሬም ላይ ገጣባ መኖሩ እውነት ነው፡፡ በልጅነቴ የአጋም ፍሬ ለመብላት ብዬ ዛፍ ላይ ወጥቼ ከአንዱ ዛፍ ወደ ሌላ እየተሸገጋርኩ እያለ የቆምኩበት እንጨት በመሰበሩ ከከፍታ ላይ ተወርውሬ ስወድቅ ከታች የቆመው ሹልና ደረቅ እንጨት ተቀብሎኝ እግሬ ውስጥ በመሸንቀሩ ምክንያት በጣም ቆስዬ ነበርና ያ ስድን ገጣባው እዚያ አለ፡፡ መኪናዬም ጥቁር ሰማያዊ ነች፡፡ እነዚህ ምልክቶች ልክ መሆናቸውን ሳይ ነው የደነገጥኩት፡፡ ይህን ሰው ከማግኜቴ ከሁለት ሳምንታት በፊት ወደ መታጠቢያ ቤት ስገባ የበሩ የላይኘው ጉበን አናቴን ደርግሞት ስለነበር ያ አሳጥሮኝ ይሆን እንዴ ብዬም አሰብኩ፡፡ ደግሞ የተናገረው ጌታ ነው ሲለኝ እንዴት አልጨነቅም? ቁመቴን የሰጠኝ ጌታ እንደሆነ ሙሉ በሙሉ አምናለሁ፡፡ በቤተ ክርስቲያኔ ከእኔ ጋር አብሮ እንዲሠራ የተመደበ መጋቢ ነበርና ሰዎችን ለመገብኘት አብረን ስንሄድ እርሱ አጭር ብቻ ሳይሆን ሆዱም ላይ ቦርጭ ነገር ጣል ስላደረገችበት እንዲያው ድቡልቡል ነው፡፡ ታዲያ አንድ ቀን አብረን ስንሄድ የእርሱ አባት በርቀት ሆነው አይተውን ኖሯልና ለምን ከዚያ ከረጅሙ ጓደኛው ጋር ይሄዳል ቢቀርበትስ ምን አለበት ብለው እቤታቸው ያወሩትን ወንድሙ ሲነግረን አይዞህ ብዬ አጽናንቼዋለሁ፡፡ አንተንም እኔንም እግዚአብሔር ግሩምና ድንቅ አድርጎ ፈጥሮናለልና ከእኔ ጋር ለመሄድ አትፍራ እለው ነበር፡፡ እጥረቱን ባደንቅለትም በሆድ ላይ ስለሚከመረው ቦርጭ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ሁሉ እነግረዋለሁ፡፡ አጭር ሰው ቦርጭ ከበዛበት ደረቱ ላይ ይወጣበትና ወደኋላ ይለጥጠዋል፡፡እንዲያውም በእርሱ ቁመት ልክ ሆነው በጣም ቦርጫም የነበሩ አቢዬ ደመቀ የሚባሉ የእኛ አካባቢ ሰው ከቦርጫቸው መብዛት የተነሳ ሆዳቸውን ወደላይ የሚያዩ ይመስላሉ፡፡ ታዲያ አብዬ ደመቀ ጫማቸውን ማየት ስለማይችሉ ጫማቸውን ሲያስጠርጉ ሊስትሮዎቹን በጣም ሲያስጠነቅቁአቸው "ጫማዬን በደንብ ጥረጉልኝ ፣ እኔ ባላይ እግዜር ያያችኋል" ይሉ እንደነበር ሁሉ ነግሬው እንደ እርሳቸው እንዳይሆን አስጠነቅቀዋለሁ-- ከዚያ ውጭ አጫጭሮች በጣም ያስፈልጉናል እነርሱ ባይኖሩ ማን ረጅም ይለናል? እኛስ ባንኖር እነርሱንስ አጭር ማለት እንዴት ይቻላል? አንዳችን ለሌላችን እናስፈልጋለን ማለት ነው፡፡ እኔን እግዚአብሔር ግሩምና ድንቅ አድርጎ በመፍጠሩ እያመሰገንኩ ስኖር ሳለ ቁመቴ ማጠሩን ከነቢይ መስማቴ እንዴት አያስደንግጠኝ? ደግሞ ረጅም መሆኔን ነግሬው ማብራሪያ ሲጠይቀው “እኔ የማውቀው ነገር የለም እግዚአብሔር ያሳየኝን ነገርኩህ” ማለቱ በበለጠ እንዳስብ አደረገኝ፡፡ ከጌታ የተቀበልኩትን ቁመት ምንም ሳልጠቀምበት ስለቀረሁ ተወሰደብኝ ማለት ነው ብዬም አሰብኩ፡፡ ያንን ጋሽ ጥላሁንና ጋሼ ማሞ ያሉኝን ብቅል እንኳ ሳላወርድ ቀርቼ ይሆናል እያልኩ ሌሊቱን ሙሉ አሰብኩ፡፡ በአንድ በኩል ከብቅል ጋር ምንም ጉዳይ እንዳይይኖረኝ ዳግም ተወልጃለሁና ብቅል ባይወርድም ተጠያቂ አልሆንም ብዬ ልጽናና ሞከርኩ፡፡ነቢይ ኢዩ ጩፋ ቁመታቸው ያጠረ ሰዎችን አስረዝማለሁ በማለት ሲዳክር ያየሁት ስለነበረ እግዚአብሔር አጫጭሮችን እያስረዘመ እኔን ረጅሙን የሚያሳጥረኝ ምን አግኝተብኝ ይሁን ብዬ አሰብኩ፡፡ ቃሉ "ለሰው ሁሉ ከሚሆን በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም"( 1 ቆሮ 10፡13) ይለናል፡፡ ግን እኔ እኮ ለሰው ሁሉ ከሚሆን በቀር የተለየ ፈተና ገጥሞኛል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር አስከ አሁን ድረስ ከእኔ በቀር ቁመቱን ያሳጠረለት ሰው አልሰማሁም አላየሁም በማለት ከጌታ ጋር በቃሉ ተሟገትኩ፡፡
ጠዋት እንደምንም ነጋልኝና ቁመቴን ለማየት ወደ ማስታወትጋ ሄድኩ፡፡ እቤታችን ያለው ማስታወት ከደረት በላይ እንጂ ሙሉ ቁመት ስለማያሳይ አልተሳካልኝም፡፡ ነገር ግን ባለቤቴ ሶፋችን ላይ ቁጭ ብላ መጽሐፍ ቅዱስ እያነበበች ሳለ ጠጋ ብዬ በስሟ ጠራሁአትና “ቁመቴ ማጠሩ አያሳዝንሽም?” አልኳት፡፡ ያንን ቃል ስደግምላት አይኗን ከመጽሐፉ ነቀለችና ወደ እኔ አየት ካደረገች በኋላ ወደ ንባቧ ተመለሰች፡፡ አሁንም እንደገና ጠየቅኳት ፡፡ ከዚያ እንዲህ አለቺኝ፡፡ “ምን ሆነህ ነው ደግሞ ዛሬ? ብላ ወደ ንበቧ መለስ አለች ወዲያው ደግሞ ወደ እኔ አየት አደረገቺኝና “ትላንት የት ሄደህ ነበር? ሰሞኑን የሆነ ቦታ ሄደሃል ማለት ነው? አለችኝ፡፡ እግዚአብሔር ቁመቴ ማጠሩን በነቢይ በኩል ተናረኝ ስላት የሳቀቺው ሳቅ ራሱ አስደነገጠኝ፡፡ እኔ የቃሉ አስተማሪ ሆኜ በዚህ መታሌለን እንደ መንፈሳዊ ጅልነት አድርጋ ወሰደቺውና “እግዚአብሔር ሥራ ጨረሰና የአንተን ቁመት እየለካ መዝናናት ጀመረ ማለት ነው?” አለች፡፡ እንግዲህ ነቢያት እውነተኞች ናቸው.፣ ከእግዚአብሔር ናቸው የሚባለው በምልክት የሚነገረው ነገር ካለንበት አካላዊና ማህበራዊ ነገሮቻችን ጋር መግጠሙን ስናይ አይደል? ያ ነቢይ የነገረኝ ምልክት አብዛኛው ትክክል ነው፡፡ ግን ግልጥ የሆነውን ከኢትዮጵያ እስከ አሜሪካ ድረስ ያለው ሕዝብ በአደባባይ የሚያየውን ረጅሙን ቁመቴን አጭር ያለው እግዚአብሔር ነው ሲባል ማመኔ ባለቤቴን ምን ነካህ ቢያስብላት ምን ጥፋት አለባት?እኔም ሳስበው እግዚአብሔር ስለ እኔ የመኪና ቀለምና የቁመቴ ጉዳይ ዋና አጀንዳው አለመሆኑን የነቃሁት ብዙ ከለፋሁ በኋላ ነው፡፡ ባለቤቴ ያንን ጥያቄ ባትጠቀኝና ከእኔ ጋር ብትደነግጥ ምን ልንሆን እንደምንችል ገምቱ፡፡
ከዚህ የምንረዳው ሐሰተኞች ነቢያቶች የሚባሉት ውሸት ብቻ የሚናገሩ እንዳይደሉ ነው፡፡ ሐሰተኞች እውነት በሚመስሉ በርካታ ነገሮች ውስጥ ሐሰተኛ መርዛቸውን ሸፍነው ስለሚያቀርቡ ሐሰትነታቸውን መለየት ቀላል ሥራ አይደለም፡፡ በሰሙት ነገር ወዲያው የሚወሰዱ የእኔ ቢጤዎቹ በቀላሉ ይመረዛሉ፡፡ የሚገርመው ነገር ያ ነቢይ በቫይበር ግሩፕ ካካተታቸው ሰዎች ውስጥ የማውቀው አንድ ወዳጄ ስለነበረ መደወል አስፈከገኝ፡፡ ስለ ሁኔታው ሳጫውተውና ነቢይ ነኝ ስለተባለውም ሰው ያውቅ እንደሆነ ብዬ ስጠይቀው የነገረኝ ነገር በበለጠ አስደመመኝ፡፡ በአገር ቤት እያለ እንደሚያውቀውና ጥሩ የሆነ የአገልግሎት ሕይወት እንደነበረውም አጫወተኝ፡፡ ነገር ግን አሁን የሰዎችን ፌስ ቡክ እየወሰደ ከዚያ መረጃዎችን ከሰበሰበ በኋላ ጌታ ተናገረኝ እያለ ወደ ሰዎች እንደሚደውል አስረዳኝ፡፡ ይህ ማለት የእኔ መኪና ቀለም ጥቁር ሰማያዊ መሆኑ የተነገረው ከጌታ ሳይሆን ከፌስ ቡክ ነው ማለት ነው፡፡የቁመቴም ጉዳይ ቢሆን ከውድ ባለቤቴ ጋር ሆኜ የተነሳሁትና ለቫይበር ፕሮፋይል ያደረግኩት ፎቶ በእርግጥም የአጭር ሰው ይመስላል ፡፡ ከእርሷ ጋር እኩል ለመሆን በደረጃ ላይ ሰበር ብዬ የተነሳሁት ስለሆነ ነቢዩ ከዚያ ሊያይ እንደሚችል ገባኝ፡፡ አንዳንዶች መዘምራን ቅኔና ወይም ዜማ ከዓለማዊ ዘፈን በመቅዳታቸው እነርሱም በዘመሩበት አማኞች በየሰፈሩ በመሰደባቸው የመጣብን ቁስል እያመረቀዘና እየጠዘጠዘን ባለበት ጊዜ የትንቢትን መልእክት ከፌስ ቡክ የሚቀዱ ደፋር ነቢያት የሚያታልሉን አጋጣሚ መፈጠሩ አስተክዞኛል፡፡ በዚህ ዓይነት ሁኔታ የተታለሉ ስንቶች ይሆኑ? ምን ይበጃል ትላላችሁ?
ወደ ስብከት አገልግሎት ስገባ ከመዘምራን ተለየሁ እንጂ መዘምራን ሲያገለግሉ ደስ ይለኛል፡፡ የዛሬውን አያርገውና ኳየሮች የሚዘምሩት መዝሙር ለረጅም ጊዜ ከልብ አይጠፋም ነበር፡፡ በመከራም ቀን እንደ ትንቢት ቃል የቅዱሳንን ልብ ደግፏል፡፡ ለምሳሌ “ድሉ የጌታችን ነው ፣ድሉ የአምላካችን ነው ድሉ” የሚለውን መዝሙር የሰማሁት በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በ1973ዓ.ም ማለትም ከ36 ዓመት በፊት ነው፡፡ ሌሎችም በጊዜው የተዘመሩ መዝሙሮች አይረሱኝም፡፡ በጊዜው የወላይታ ቤተ ክርስቲያን በመራራ ስደት ውስጥ ሳለች የመሠረተ ክርስቶስ ቤክ መዘምራን ወደ ቦታው ተንቀሳቅሰው በ”ኦቶና” ዓመታዊ ኮንፍራንስ ላይ ሲዘምሩና ሕዝቡ አብሮአቸው በእምባ ሲራጭ እኔና እኩያዎቼ ከመድረኩ ፊት ለፊት በመሬት በተጎዘጎዘው ሣር ላይ እንድንቀመጥ አስተናጋጀች ስላስገደዱን እዚያው ሆኜ ነው የሰማሁት፡፡ ይህ መዝሙር ዛሬም ለእግዚአብሔር ሕዝብ ትኩስ መልእክት ያለው ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በመዝሙር የማገልገል ጥማት ውስጤ ገብቶ ስለነበር እስከአሁን አራት በሚያህሉ ኳየሮች አገልግያለሁ፡፡ ታዲያ መዘምራኖቹ በቁመቴ ብቻ ሳይሆን ድምጼም ዝማሬውን ስለሚያተራምስባቸው ይቸገሩብኝ ነበር፡፡ እኔም ከመዘምራን ጋር ባገለገልኩባቸው ጊዜያቶች ቅር ያለኝ ነገር ቢኖር አብሬአቸው ፎቶ መነሳቴ ነው፡፡ ከእነርሱ ጋር የተነሳሁአቸው ፎቶዎቼ አብዛኛዎቹ ወይ ከአንጌቴ፣ ወይ ከፍንጫዬ በላይ የላቸውም፡፡ ጌታ ኃጢአቴን ሁሉ ይቅር እንዳለኝ መጽኸፉ ስለነገረኝ እኔም ይቅር ብዬአቸው ነው እንጂ ያኔ ፎቶ ባነሱን ሰዎች ላይ ቂም ቢጤ ሁሉ ቋጥሬባቸው ነበር ፡፡አጫጭሮቹ ከእግራቸውም ከጭንቅላቸውም በሌንሳቸው እንዲገቡ ብለው እኔን ከአጭሮቹ ትክክል ቆርጠውኛልና፡፡
በቤተ ክርስያቲናችን የበረውን ትልቁን ፑልፒት አጫጭሮቹ ሰባኪዎች አይወዱትም ነበር፡፡ ያንን ፑልፒት ያስቀየረን አንዱ የእነርሱ ብሶት ነው፡፡ ፑልፒቱ ስለሚከልላቸው ከሥሩ ለእነርሱ ተብሎ የተዘጋጀ ኩርሲ አይነት ነገር ስላለ ሲሰብኩ እዚያ ላይ ይወጣሉ፡፡ ከዚያ እንደምንም ብለው ከደረታቸው በላይ ይታያሉ፡፡ ሊሰብኩ እዚያ ላይ ወጥተው "እታያለሁ?"ብለው ጉባኤውን የጠየቁ ሁሉ ነበሩ ብል ታምኑኛላችሁ? አሁን ብዙ ሲዘመር አልሰማውም እንጂ አንድ "መሸሸጊያ ዋሻ 2x መከታ ጋሻችን" የሚል ተወዳጅ መዝሙር ነበርና ከምንወዳቸው ሽማግሌዎቻችን አንዱ ይህን ምዝሙር እያዘመረ ጉባኤውን ሲመራ በተለይ መሸሸጊያ ዋሻ የሚለው ቃልጋ ሲደርሱ በዚያ ፑልፒት ሥር እየተደበቀና ከዚያም ብቅ እያለ ሲመራ ጥሩ ምሳሌ ይሆንለት ነበር:: ታዲያ ከመድረኩ ጫፍ ወደ ሌላው ጫፍ የሚሯሯጥ ሰባኪ ያ ፑልፒት አይመቸውም፡፡ እኔ ስሰብክ ግን ያንን ኩርሲ ስለማልፈልግ ወደ ጎን አሽቀነጥረውና መሬቱ ላይ ቆሜ እንኳ ጉባኤው ከደረቴ ሳይሆን ከወገቤ በላይ ያየኝ ነበር፡፡ አስቡ እንግዲህ! የቤተክርሰትያናችን አባቶች ቅጽል ስም ሁላ አውጥተውልኛል፡፡ በጣም የምናከብራቸው የነበረ ጋሼ ጥላሁን “ሰማይ ዛፉ” ፣ “ብቅል አውራጅ”፣ ይሉኝ ነበር፡፡ ጋሼ ወልደአምላክማ በስሜ ከሚጠሩኝ “ቀውሌ” ሲሉኝ ይቀላቸዋል፡፡ ጋሼ ማሞ ደግም ልክ እንደ ጋሽ ጥላሁን “ሰማይ ዛፉ” እንደሚሉኝ ልንገራችሁ፡፡ የማታውቁኝ ወገኖቼ ምን ያህል ረጅም እንደሆንኩ በዚህ ይግባችሁ ብዬ ነው፡፡
በረዶ ካልዘነበ በቀር አንዳድ ጊዜ ከባለቤቴ ጋር በእግር እንጓዛለን( ባለንበት አገር ዎክ ይባላል)፡፡ ታዲያ የምንጓዘው እያወራን ነው፡፡ ምን አለፋችሁ ባለቤቴ ቀስ ብላ የመናገር ባሕሪይ ስላላት እሷ የምትለው እኔጋ አይደርስም፡፡ እኔ ከላይ ሆኜ ስለምናገር እያንዳንዱን ነገር ትሰማለች፡፡ ስንቸገር ለምን እኔና አንቺ በስልክ አናወራም እላታለሁ፡፡ አብረን እየተጓዝን ወደ አንድ የገበያ አዳራሽ ስንደርስ እርሷ የሆነ ዕቃ እንግዛ ብላኝ ወደ ውስጥ ስንገባ ህንዳዊው የሱቁ ባለቤት አላየንም ነበር ግን ኮሜዲኖው አጠገብ ቆመን ስናናግረው በሆነ ወንበር ላይ የቆምኩ መስሎት አንገቱን አሰግጎ ወደ ጫማዬ አየኝና "በምን ላይ ቆመህ ነው ?" ያለኝ ቀን እንዴት እንደሳቅኩ ልነግራችሁ አልችልም፡፡ የሰውዬው አባባል በአዲስ አበባ ቦሌ ቃለ ሕይወት ቤክ አገልግዬ ስመለስ አንዲት የሀብታም ልጅ የምትመስል ከእናቷ ጋር ስትሄድ ነበርና በአጠገባቸው ሳልፍ አይታኝ እንደመሞላቀቅ አድርጎአት "ወይኔ ጂሴስዬ....ሰውዬው ምን ያክላ.....ል" ማለቷን አስታወሰኝ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ተቃራኒውም ይገጥመኝና አቤት የጌታ ሥራ እንዴት ግሩም ነው እላላሁ፡፡ ለአገልግሎት ሌላ ቦታ ካልሄድኩ በግራድ ራፒዲስ ከተማ ወደሚገኘው ካልቬሪ ቤተክርስቲያን ሄደን የጌታን ቃል እንሰማለን፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ ትልቅ ከመሆኑ የተነሳ ስድስት የሙጪያና የመግቢያ በሮች አሉት፡፡ አንድ ቀን ግን ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ስንገባ የመጀመሪያውን ፈረቃ ተካፍለው የሚወጣውና ሁለተኛውን ለመካፈል የምንገባው ሰዎች ዌስት ጌት (የምዕራቡ መግቢያ በር) በኩል ባለው በተላለፊያ ላይ ተገናኘን፡፡ ታዲያ በፈረንጆች አካባቢ ረጅም ሰውና ሽማግሌዎችን ማየት እንደ ልብ ስለሆነ እንደ እኛ አይገርማቸውም፡፡ ግን ያን ቀን የሚወጣው ሕዝብ ሲወጣ እኛ ደግሞ ስንገባ ከፊት ለፊቴ አንዲት ዕድሜዋ በግምት ከ25-30 ውስጥ የሚሆናት ወጣት ሴት በሕዝቡ መካከል ወደ እኛ አቅጣጫ ትመጣ ነበር፡፡ ከሰው ሁሉ ከፍ ብለን የምንታየው እኔና እርሷ ብቻ ነበርን፡፡ ግን ሆን ብላ ወደ እኔ መጣችና በአጠገበ አለፈች፡፡ ታዲያ ምን አለፋችሁ ወደ አናቴ ቁልቁል እያየችኝ ስታልፍ አንዱ ሽማግሌ ፈረንጅ ተክ ብሎ ሳቀ፡፡ አንተንም የሚበልጥ መኖሩን እወቅ የሚል ይመስላል፡፡
እኔም ይህንን ሁሉ የዘከዘኩት በቁመቴ ላዝናናችሁ ወይም ላስቀናችሁ አይደለም፡፡ ቁመቴ 6.5 ሃይት መሆኑ በህግ ተረጋግጦ በመንጃ ፈቃዴና በሌሎች ሕጋዊ ሰነዶች ላይ ሰፍሮ እያለ ሰሞኑን አጭር መሆኔ ሲነገረኝ ክው ብዬ ስለ ደነገጥኩኝ የሚያጽናና መልእክት ወይም ምክር ካላችሁ እንድትለግሱልኝ በማለት ነው እንጂ፡፡ አጭር መሆኔ የተነገረኝ ከሀኪም ወይም ከሌላ ባለሙያ አይደለም፡፡ ካለሁበት አገርም አይደለም፡፡ ከነቢያት አገር ከኢትዮጵያ ነው፡፡ አንድ ሰው በቫይበር ግሩፕ ፈጠረና እኔንም እዚያው ውስጥ አካቶኝ መልእክት ስለላከብኝ ማን አንደሆነና የእኔንም ስልክ ከየት እንዳገኘ እንዲነግረኝ መልእክት ላኩበት፡፡ ከዚያ በዚያው በቫይበር ደውሎልኝ ማእረጉን በማስቀደም ስሙን ነገረኝ፡፡ ስሙን ለጊዜው ላቆይና ወንድማችን በማዕረጉ ነቢይ ነው፡፡ ፕሮፌት …….. እባላለሁ ከኢትዮጵያ አለኝ፡፡ ማዕረግ ያልኩበት ምክንያት አሁን አሁን ወንጌላዊነት ፣ መጋቢነት ፣ ወይም ሓዋሪያነትና ነቢይነት ለአገልግሎት እንደተሰጠን የጸጋ ስጦታ ሳይሆን እንደ ማዕረግ ስለሚታይና ሰዎችም በዚያ ማዕረግ ካልተጠሩ ስለሚከፋቸው ነው፡፡ እንግዲህ አሳብ እየተለዋወጥን እያለ ጌታ ስላገናኘን አመሰገነና በሰዓቱ እግዚአብሔር ስለ እኔ የሚያሳየውን ነገር ስላለው ልነግረኝ ፈቃደናነቴን ጠየቀኝ፡፡ ፕሮፌት ነኝ ስላለ እና እኔም የነቢያትን አገልግሎት ስለማከብር ንገረኝ አልኩት፡፡ ብዙ ነገር ነገሮኝ ያንን ሁሉ በምልክት ሊያጸናልኝ ፈልጎ ማረጋገጫ በምልከት ይደረድርልኝ ጀመር፡፡ “አንደኛ፣ በ1996 ዓ. መጨረሻና በ1997 መግቢያ ላይ በሕይወትህ አንድ ነገር ሆኗል፡፡ ሁለተኛ፣ አንተ ጥቁር ሰማያዊ መኪና አለችህ፡፡ ሦስተኛ፣ በግራ እግርህ ከጉልበትህ በታኝ ቆስሎ የዳነ ምልክት አለብህ፡፡ አራተኛ አንተ ረጅም ሰው አይደለህም በቁመትህ ከአጭር ሰው ትንሽ ከፍ ትላለህ፡፡ ይህንን የምነግርህ እምነት እንዲሆንህ ነው አሜን በል፣ ” አለኝ፡፡ እኔም አሜን አልኩ፡፡ ለምን አሜን አልክ አትበሉኝ
ስለ ቁመቴ ማጠር ስሰማ በጣም ደነገጥኩ፡፡ መልሼ “እኔ እኮ በጣም ረጅም ሰው ነኝ፡፡ እንዲያውም ድሮ ከጋምቤላ አካባቢ መጥተው ለአየር ኃይል መረብና ቅርጫት ኳስ የሚጫወቱ ረጃጅም ሰዎች ነበሩ:፡ ወይም ከቦረና ነገሌ መጥተው በመረብ ኳስ ሜዳ ያገኘናቸው ሰዎች ካልሆኑ እሰከአሁን በቁመት የሚያክለኝ ሰው አልገጠመኝም፣ አንተ ደግሞ ከአጭር ሰው ትንሽ ከፍ እንደምል ትነግረኛለህ፡፡ ነገሩ እንዴት ነው?” ስለው፣ “እንግዲህ እኔ የማውቀው ነገር የለም ጌታ ያሳየኝ ይህ ነው” አለኘኝ፡፡ የቁጣ መልስ ስለመሰለኝ ጨዋታችንን እዚውጋ አበቃን፡፡ ደግሜም ያንን ሰው አላገኘሁትም፡፡
ታዲያ ምን አሳሰበህ የሚል ቢኖር ከላይ በተጠቀሱት ዓመታት በሕይወቴ የሆኑ ብዙ ነገሮች ነበሩና ትክክል ነው ብዬ ተቀበልኩ፡፡ በእግሬም ላይ ገጣባ መኖሩ እውነት ነው፡፡ በልጅነቴ የአጋም ፍሬ ለመብላት ብዬ ዛፍ ላይ ወጥቼ ከአንዱ ዛፍ ወደ ሌላ እየተሸገጋርኩ እያለ የቆምኩበት እንጨት በመሰበሩ ከከፍታ ላይ ተወርውሬ ስወድቅ ከታች የቆመው ሹልና ደረቅ እንጨት ተቀብሎኝ እግሬ ውስጥ በመሸንቀሩ ምክንያት በጣም ቆስዬ ነበርና ያ ስድን ገጣባው እዚያ አለ፡፡ መኪናዬም ጥቁር ሰማያዊ ነች፡፡ እነዚህ ምልክቶች ልክ መሆናቸውን ሳይ ነው የደነገጥኩት፡፡ ይህን ሰው ከማግኜቴ ከሁለት ሳምንታት በፊት ወደ መታጠቢያ ቤት ስገባ የበሩ የላይኘው ጉበን አናቴን ደርግሞት ስለነበር ያ አሳጥሮኝ ይሆን እንዴ ብዬም አሰብኩ፡፡ ደግሞ የተናገረው ጌታ ነው ሲለኝ እንዴት አልጨነቅም? ቁመቴን የሰጠኝ ጌታ እንደሆነ ሙሉ በሙሉ አምናለሁ፡፡ በቤተ ክርስቲያኔ ከእኔ ጋር አብሮ እንዲሠራ የተመደበ መጋቢ ነበርና ሰዎችን ለመገብኘት አብረን ስንሄድ እርሱ አጭር ብቻ ሳይሆን ሆዱም ላይ ቦርጭ ነገር ጣል ስላደረገችበት እንዲያው ድቡልቡል ነው፡፡ ታዲያ አንድ ቀን አብረን ስንሄድ የእርሱ አባት በርቀት ሆነው አይተውን ኖሯልና ለምን ከዚያ ከረጅሙ ጓደኛው ጋር ይሄዳል ቢቀርበትስ ምን አለበት ብለው እቤታቸው ያወሩትን ወንድሙ ሲነግረን አይዞህ ብዬ አጽናንቼዋለሁ፡፡ አንተንም እኔንም እግዚአብሔር ግሩምና ድንቅ አድርጎ ፈጥሮናለልና ከእኔ ጋር ለመሄድ አትፍራ እለው ነበር፡፡ እጥረቱን ባደንቅለትም በሆድ ላይ ስለሚከመረው ቦርጭ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ሁሉ እነግረዋለሁ፡፡ አጭር ሰው ቦርጭ ከበዛበት ደረቱ ላይ ይወጣበትና ወደኋላ ይለጥጠዋል፡፡እንዲያውም በእርሱ ቁመት ልክ ሆነው በጣም ቦርጫም የነበሩ አቢዬ ደመቀ የሚባሉ የእኛ አካባቢ ሰው ከቦርጫቸው መብዛት የተነሳ ሆዳቸውን ወደላይ የሚያዩ ይመስላሉ፡፡ ታዲያ አብዬ ደመቀ ጫማቸውን ማየት ስለማይችሉ ጫማቸውን ሲያስጠርጉ ሊስትሮዎቹን በጣም ሲያስጠነቅቁአቸው "ጫማዬን በደንብ ጥረጉልኝ ፣ እኔ ባላይ እግዜር ያያችኋል" ይሉ እንደነበር ሁሉ ነግሬው እንደ እርሳቸው እንዳይሆን አስጠነቅቀዋለሁ-- ከዚያ ውጭ አጫጭሮች በጣም ያስፈልጉናል እነርሱ ባይኖሩ ማን ረጅም ይለናል? እኛስ ባንኖር እነርሱንስ አጭር ማለት እንዴት ይቻላል? አንዳችን ለሌላችን እናስፈልጋለን ማለት ነው፡፡ እኔን እግዚአብሔር ግሩምና ድንቅ አድርጎ በመፍጠሩ እያመሰገንኩ ስኖር ሳለ ቁመቴ ማጠሩን ከነቢይ መስማቴ እንዴት አያስደንግጠኝ? ደግሞ ረጅም መሆኔን ነግሬው ማብራሪያ ሲጠይቀው “እኔ የማውቀው ነገር የለም እግዚአብሔር ያሳየኝን ነገርኩህ” ማለቱ በበለጠ እንዳስብ አደረገኝ፡፡ ከጌታ የተቀበልኩትን ቁመት ምንም ሳልጠቀምበት ስለቀረሁ ተወሰደብኝ ማለት ነው ብዬም አሰብኩ፡፡ ያንን ጋሽ ጥላሁንና ጋሼ ማሞ ያሉኝን ብቅል እንኳ ሳላወርድ ቀርቼ ይሆናል እያልኩ ሌሊቱን ሙሉ አሰብኩ፡፡ በአንድ በኩል ከብቅል ጋር ምንም ጉዳይ እንዳይይኖረኝ ዳግም ተወልጃለሁና ብቅል ባይወርድም ተጠያቂ አልሆንም ብዬ ልጽናና ሞከርኩ፡፡ነቢይ ኢዩ ጩፋ ቁመታቸው ያጠረ ሰዎችን አስረዝማለሁ በማለት ሲዳክር ያየሁት ስለነበረ እግዚአብሔር አጫጭሮችን እያስረዘመ እኔን ረጅሙን የሚያሳጥረኝ ምን አግኝተብኝ ይሁን ብዬ አሰብኩ፡፡ ቃሉ "ለሰው ሁሉ ከሚሆን በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም"( 1 ቆሮ 10፡13) ይለናል፡፡ ግን እኔ እኮ ለሰው ሁሉ ከሚሆን በቀር የተለየ ፈተና ገጥሞኛል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር አስከ አሁን ድረስ ከእኔ በቀር ቁመቱን ያሳጠረለት ሰው አልሰማሁም አላየሁም በማለት ከጌታ ጋር በቃሉ ተሟገትኩ፡፡
ጠዋት እንደምንም ነጋልኝና ቁመቴን ለማየት ወደ ማስታወትጋ ሄድኩ፡፡ እቤታችን ያለው ማስታወት ከደረት በላይ እንጂ ሙሉ ቁመት ስለማያሳይ አልተሳካልኝም፡፡ ነገር ግን ባለቤቴ ሶፋችን ላይ ቁጭ ብላ መጽሐፍ ቅዱስ እያነበበች ሳለ ጠጋ ብዬ በስሟ ጠራሁአትና “ቁመቴ ማጠሩ አያሳዝንሽም?” አልኳት፡፡ ያንን ቃል ስደግምላት አይኗን ከመጽሐፉ ነቀለችና ወደ እኔ አየት ካደረገች በኋላ ወደ ንባቧ ተመለሰች፡፡ አሁንም እንደገና ጠየቅኳት ፡፡ ከዚያ እንዲህ አለቺኝ፡፡ “ምን ሆነህ ነው ደግሞ ዛሬ? ብላ ወደ ንበቧ መለስ አለች ወዲያው ደግሞ ወደ እኔ አየት አደረገቺኝና “ትላንት የት ሄደህ ነበር? ሰሞኑን የሆነ ቦታ ሄደሃል ማለት ነው? አለችኝ፡፡ እግዚአብሔር ቁመቴ ማጠሩን በነቢይ በኩል ተናረኝ ስላት የሳቀቺው ሳቅ ራሱ አስደነገጠኝ፡፡ እኔ የቃሉ አስተማሪ ሆኜ በዚህ መታሌለን እንደ መንፈሳዊ ጅልነት አድርጋ ወሰደቺውና “እግዚአብሔር ሥራ ጨረሰና የአንተን ቁመት እየለካ መዝናናት ጀመረ ማለት ነው?” አለች፡፡ እንግዲህ ነቢያት እውነተኞች ናቸው.፣ ከእግዚአብሔር ናቸው የሚባለው በምልክት የሚነገረው ነገር ካለንበት አካላዊና ማህበራዊ ነገሮቻችን ጋር መግጠሙን ስናይ አይደል? ያ ነቢይ የነገረኝ ምልክት አብዛኛው ትክክል ነው፡፡ ግን ግልጥ የሆነውን ከኢትዮጵያ እስከ አሜሪካ ድረስ ያለው ሕዝብ በአደባባይ የሚያየውን ረጅሙን ቁመቴን አጭር ያለው እግዚአብሔር ነው ሲባል ማመኔ ባለቤቴን ምን ነካህ ቢያስብላት ምን ጥፋት አለባት?እኔም ሳስበው እግዚአብሔር ስለ እኔ የመኪና ቀለምና የቁመቴ ጉዳይ ዋና አጀንዳው አለመሆኑን የነቃሁት ብዙ ከለፋሁ በኋላ ነው፡፡ ባለቤቴ ያንን ጥያቄ ባትጠቀኝና ከእኔ ጋር ብትደነግጥ ምን ልንሆን እንደምንችል ገምቱ፡፡
ከዚህ የምንረዳው ሐሰተኞች ነቢያቶች የሚባሉት ውሸት ብቻ የሚናገሩ እንዳይደሉ ነው፡፡ ሐሰተኞች እውነት በሚመስሉ በርካታ ነገሮች ውስጥ ሐሰተኛ መርዛቸውን ሸፍነው ስለሚያቀርቡ ሐሰትነታቸውን መለየት ቀላል ሥራ አይደለም፡፡ በሰሙት ነገር ወዲያው የሚወሰዱ የእኔ ቢጤዎቹ በቀላሉ ይመረዛሉ፡፡ የሚገርመው ነገር ያ ነቢይ በቫይበር ግሩፕ ካካተታቸው ሰዎች ውስጥ የማውቀው አንድ ወዳጄ ስለነበረ መደወል አስፈከገኝ፡፡ ስለ ሁኔታው ሳጫውተውና ነቢይ ነኝ ስለተባለውም ሰው ያውቅ እንደሆነ ብዬ ስጠይቀው የነገረኝ ነገር በበለጠ አስደመመኝ፡፡ በአገር ቤት እያለ እንደሚያውቀውና ጥሩ የሆነ የአገልግሎት ሕይወት እንደነበረውም አጫወተኝ፡፡ ነገር ግን አሁን የሰዎችን ፌስ ቡክ እየወሰደ ከዚያ መረጃዎችን ከሰበሰበ በኋላ ጌታ ተናገረኝ እያለ ወደ ሰዎች እንደሚደውል አስረዳኝ፡፡ ይህ ማለት የእኔ መኪና ቀለም ጥቁር ሰማያዊ መሆኑ የተነገረው ከጌታ ሳይሆን ከፌስ ቡክ ነው ማለት ነው፡፡የቁመቴም ጉዳይ ቢሆን ከውድ ባለቤቴ ጋር ሆኜ የተነሳሁትና ለቫይበር ፕሮፋይል ያደረግኩት ፎቶ በእርግጥም የአጭር ሰው ይመስላል ፡፡ ከእርሷ ጋር እኩል ለመሆን በደረጃ ላይ ሰበር ብዬ የተነሳሁት ስለሆነ ነቢዩ ከዚያ ሊያይ እንደሚችል ገባኝ፡፡ አንዳንዶች መዘምራን ቅኔና ወይም ዜማ ከዓለማዊ ዘፈን በመቅዳታቸው እነርሱም በዘመሩበት አማኞች በየሰፈሩ በመሰደባቸው የመጣብን ቁስል እያመረቀዘና እየጠዘጠዘን ባለበት ጊዜ የትንቢትን መልእክት ከፌስ ቡክ የሚቀዱ ደፋር ነቢያት የሚያታልሉን አጋጣሚ መፈጠሩ አስተክዞኛል፡፡ በዚህ ዓይነት ሁኔታ የተታለሉ ስንቶች ይሆኑ? ምን ይበጃል ትላላችሁ?
Subscribe to:
Posts (Atom)