Thursday, May 11, 2017

የተዋረድን ቢመስለንም የክብር ቀን ይመጣል፡፡

                                                            ከመጋቢ ሳሙኤል ሾንጋ

ይህንን ጽኹፍ ለማዘጋጀት ከመጀመሪያው ዕቅድ አልነበረኝም፡፡ ነገር ግን በየ15 ቀኑ እየጓዝኩ በሚሰብክባት የሰውዝፍልድ ሚቺጋን ኢትዮጵያ ወንጌጌላዊት ቤክ አባልና አገልጋይ የሆነች እህት በራዕይ መጽሐፍ 11 ፡ 4 ላይ ስለሚገኙ ስለ ሁለት ወይራዎች ምስጥራት እንድነግራት ስለጠየቀችኝ ለእርሷ ምላሽ እንዲሆን ብዬ ያዘጋጀሁትን ምላሽ ነው አሁን የማቀርብላችሁ፡፡ መቼም በመድረክ ማገልገል በተለይም ቃሉን እየተረጎምን የምናስተምር ከሆነ ከአገልግሎት በመልስ ሌሎች ክፍሎችንም እንድናብራራላቸው የሚጠይቁ ሰዎች አሉ፡፡ ይህ ደግሞ በጣም የሚያስደስት ነገር ነው፡፡ ይህንን ክፍል እንዳብራራላት የጠየቀቺኝን እህት እያሰገንኩ እኔም አሳቡን ለመመልከት ችያለሁ፡፡ ጭንቀቴ እንደ ፓስተሯ ለምታየኝ ቅንና የቃሉ ወዳድ ለሆነቺው እህቴ የተሳሳተ ነገር እንዳልናገር ነበር፡፡ እንግዲህ አሳቡን፡ካየሁና ለእርሷም ምላሽ ከሰጠሁ በኋላ ለራሴም ትልቅ መልእክት ስለሆነኝ  ጓደኞቼም እንዲያነቡት ባደርግስ ብዬ ስላሰብኩ ይኸውና ከነማብራሪያ ከዚህ እንደሚከተለው ስላስቀመጥኩ ተቋደሱት፡፡
የዮሐንስ ራዕይ መጽሐፍ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኙ ለመተርጎም ከባድ ከምንላቸው መጻሕፍት አንዱ ነው፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት መጽሐፉ አቡቀለም ሲስ ተብሎ ከሚጠሩት መጽሓፍት ጋር የሚመደብ ስለሆነ ነው፡፡ እንደዚህ ባሉት መጽሓፍት አንዳንድ አሳቦች ከተለመደው ውጭ በሆኑ ቋንቋዎች ወይም የአገላለጽ ዘይቤዎች ስለተነገሩ ትርጉሙን በቀላሉ ማግኘት አዳጋች ይሆናል፡፡ አቡቀለም ሲስ ማለት መገለጥ ወይም ራዕይ እንደማለት ነው፡፡
በምዕራፍ 11 ቁጥር 4 ላይ የተጠቀሱ ሁለቱ ወይራዎች እነማን ናቸው የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ወደ ምንባብ ክፍል መሄድ ያስፈልጋል፡፡ በታላቁ መከራ ጊዜ በምድር ላይ ሊነሱ ስላሉት ሁለት ምስክሮች ፣ ሁለቱ ወይራዎች ወይም ሁለቱ መቅረዞች የሚናገር ሲሆን የክፍሉን ሙሉ አሳብ ለማግኘት ከቁጥር 1-13 ሙሉን ማበብ ያስፈልጋል፡፡ ይህ የንባብ ክፍል በራዕይ መጽሐፍ ውስጥ ከሚገኙ ሰባት ወዮዎች በሁለተኛው ውስጥ ያለ ነው፡፡ በተለይም ስለ ሁለቱ ምስክሮች ሦስት መሠረታዊ አሳቦችን እናገኛለን፡፡ 1. ስለ ሁለቱ ምስሮች አገልግሎት (3-6)፣ 2. ስለ ሁለቱ ምስክሮች አሟሟት( 7-10) እና 3. ስለ ሁለቱም ምስክሮች ትንሳኤ ( 11-13) እናያለን፡፡ 
ታዲያ እነዚህ ማናቸው የሚለውን ለመመለስ የሞከሩ ብዙ የስነ መለኮት አስተማሪዎችና ተማሪዎች አሉ፡፡ በዚህ ላይ የእግዚአብሔር ሰዎች በመከራው ጊዜ ስለ እምነታቸው ቢሰደዱም እግዚአብሔር ግን ለሕዝቡ የሚሆን መልእክት መስጠትን አልተወም፡፡ እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች በታላቁ መከራ ጊዜ ለእግዚአብሔር ሕዝብ እጅግ በጣም አስፈላጊዎች ነበሩ፡፡ እግዚአብሔር በዚህ ክፍል ውስጥ እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች እነማን እንደሆኑ አልገለጻም፡፡ ስለዚህ ነው የመጽሐፍ ቅዱስ ተርጓሚዎች የተለያዩ ትርጉሞችን መስጠት የቻሉት፡፡ እነዚህን የተለያዩ ትርጎሞቹን እንደሚከተለው አስቀምጬዋለሁ፡፡
1. ሙሴና ኤልያስ ናቸው፡፡ ይህንን ትርጉም የሚከተሉ ሰዎች በዮሐንስ ራዕይ ምዕራፍ 11 ላይ ያሉ ምስክሮች ሙሴና ኤልያስ በብሉይ ኪዳን ጊዜ ያደርጉ የነበሩትን አይነት ተአምራት ማድረጋቸው ስለተጠቀሰ የብሉይ ኪዳን ነቢያት የሆኑት ሙሴና ኤልያስ እንደገና ወደ ሕይወት ተመልሰው ይመጡ ይሆናል ብለው ነው የሚተረጉት፡፡
2. ሄኖክና ኤልያስ ይሆናሉ፡፡ በዚህ ትርጉም መሰረት እግዚአብሔር ሄኖክንና ሙሴን ሳይሞቱ ወደ ሰማይ እንደወሰዳቸው በብሉይ ኪዳን ስለተጸፋና አሁንም እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች ከሞት ከተነሡ በኋላ ሳይሞቱ መወሰዳቸው በምንባብ ክፍል ስለተጠቀሰ እነርሱ ይሆናሉ፡፡
3. ኤልያስና ሚልክያስ ይሆናሉ፡፡ መሲሁ ኢየሱስ ከመምጣቱ በፊት ኤልያስ ይመጣል ብሎ ሚልክያስ ስለተነበየ ኤልያስና ትንቢቱን የተናገረው ሚልክያስ ራሱ ይሆናል ብለው ያስተምራሉ፡፡
4. ያዕቆብና ጴጥሮስ ናቸው፡፡ እዚህ ሁለቱ ሮማውያን የኢየሩሳሌምን ቤተ ክርስቲያንን ባሳደዱበት ጊዜ የተገደሉና ለከፍተኛ እሥራትና ግርፋት ከዚያም ለሞት የተሰጡ በመሆናቸው በዚህ መከራ ጊዜ ከሙታን ተነስተው የሚያገለግሉ እነርሱ ይሆናሉ በሚል ነው፡፡
5. ቅዱሳን በሙሉ ናቸው፡፡ ይህንን አሳብ የሚሰጡ ሰዎች እንደሚናገሩት ሁለቱ ምስክሮች የተባሉት ሁለት ግለሰቦች ሳይሆኑ ሁለቱን የብሉይና የአዲስ ኪዳን መጻሕፍትን ይዘው በመከራ ውስጥ ላሉት ሁሉ የሚመሰክሩ ቅዱሳን ወገኖች ናቸው፡፡
እንግዲህ የምንባብ ክፍሉ ስለ ሰዎቹ ማንነት በግልጽ ባይነግረንም እነዚህ ሰዎች የእግዚአብሔርን መልእክት በጊዜው ላሉ አማኞች የሚተነብዩ ወንጌሉን የምስራች የሚሰብኩ መሆናቸው ግን እሙን ነው፡፡ አገልግሎታቸውም በትንቢተ ዳንኤል 12፡11 ላይ እንደተጠቀሰው ዓይነት ለ 1260 ቀናት ወይም 42 ወራት ነው፡፡ ያ ማለት ለሶስት ዓመት ተኩል ያገለግላሉ ማለት ነው፡፡ የዮሐንስን ራእይ በምናጠናበት ወቅት የትንቢተ ዳንኤልንም መጽሐፍን አንድ ላይ ማጥናት ያለብን ለዚህም ጭምር ነው፡፡ የትንቢተ ዳንኤልም መጽሐፍ እንደ ዮሐንስ ራዕይ ዓይነት የአቡቀለም ሲስ የሆኑ መልእክቶች አሉበት ፡፡ ስለዚህ ከዚህ ክፍል ያሉትን አሳቦች በሦስት ከፍለን እንይ፡፡
1. የሁለቱ ምስክሮች አገልግሎት
ሁለቱ ምስክሮች በሚገለግሉበት ወቅት ማቅ ለብሰው እንደሚሆን ዮሐንስ ይነግረናል፡፡ የእግዚአብሔር ቃል መጽሐፍ ቅዱስ በሙላት በሚሰበክበትና የእግዚአብሔር ክብር በምንቀሳቀስበት ወቅት በአንጻሩ ደግሞ ሰዎች ኃጢአትን ሲለማመዱ ሲያዩ ነቢያትና ነገሥታት ካህናትም ማቅን መልበሳቸው የእግዚአብሔር ፍርድ ስላለ ንስሐ መግባት በጣም አስፈላጊ መሆኑን ለማሳየት ነው፡፡ ለዚህም ኢሳ 12፡22፣ ኤር.4፡8፣ኤር 6፡26፣ ዮናስ3፡5፣6፣8፣ ማቴ 11፡21ን መመልከት ይቻላል፡፡
የሁለቱ ምስክሮች አገልግሎት ከምርኮው ወደ እሥራኤል አገር ከተመለሱ በኃላ ወደ ተሐዲሶ ለማምጣት ያገለገሉ የዜሩባበልና የካህኑ የኢያሱን አገልግሎት ይመስላል( ዘካርያስ 4፡2-3፣11-14)፡፡ ምክንያቱም እነዚህ መቅረዞች ተብለዋል፡፡ በዘካርያስ መጽሐፍ አንድ
መቅረዝ ያለ ሲሆን በዮሐንስ ራዕይ ግን ሁለት መቅረዞች ተጠቅሰዋል፡፡ በዮሐንስ ራዕይ በራሱ ደግሞ መቅረዝ የክርስቶስን ቤተ ክርሰቲያን የሚወክል መሆኑን ደግሞ በመዕራፍ አንድ ላይ መመልከት ይቻላል( 1፡12-13)፡፡ በዘካሪስ ላይ ያለው መቅረዝ መንፈስ ቅዱስን የሚያመለክት ሲሆን በታላቁ መከራ ጊዜ የሚነሡ ሁለቱ ምስክሮች ( ሁለቱ መቅረዞች) የአገልግሎታቸውን ኃይል የሚቀበሉት ከመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ይህን ኃይል ከመንፈስ ቅዱስ ከተቀበሉ በኋላ በመቅደሱ ሆነው ልክ እንደ መቅረዝ የጌታን ብርሃን የሚሳዩ የእግዚአብሔር እውነተኛ ምስክሮች ይሆናሉ፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ተደግፈው ዓለምን ሁሉ ለሚቆጣጠረው እግዚአብሔር ምስክሮች ይሆናሉ፡፡
ሁለቱ ምስክሮች ነቢዩ ኤልያስ በ2ኛ ነገስት 1፡10-14 እንዳደረገው ሊጎዱአቸው በሚመጡ ጠላቶቻቸው ላይ እሳትን ከሰማይ በመጥራት ራሳቸውን ለመከላከል የሚችሉበት እግዚአብሔር ኃይል እንደሚሰጣቸው እንመለከታለን፡፡ ከእነዚህ ምስከሮች አፍ እሳት እንደሚወጣ መናገሩ ቀጥተኛ ትርጉም ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ተአምራትን እንዲያደርጉ በኃይል እንደሚሞላቸው ከክፍሉ እናገኛለን፡፡ ልክ ሙሴና ኤልያስ ሲያደርጉ እንደነበረው ሁሉ ውሃን የመለወጥና መቅሰፍትን በምድር ላይ የማምጣትና ዝናብ እንዳይወርድ የመከልከል ሥልጣን እንደሚሰጣቸው እንመለከታለን( ዘጸአት 7፡17-21፣ 9፡14፣ 11፡10፣ 1ሳሙ.4፡8፣ ፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጓሚዎች ሁለቱ ምስክሮች ( ሁለቱ ወይራዎች) ኤልያስና ሙሴ ናቸው ያሉበት ምክንያትም ይህ ነው፡፡
2. የሁለቱ ምስክሮች ሞት
አገልጋዮች በታላቅ ኃይልና ጸጋ ሲያገለግሉ ሁል ጊዜ አድፍጦ የሚጠብቃቸው ጠላት እንዳለ ማወቅ ይኖርብናል፡፡ አውሬው እነዚህን ሰዎች ሊገድላቸው የሚችለው ግን እነርሱ ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን አገልግሎት ከጨረሱና እግዚአብሔርም የፈቀደለት እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ምስክሮቹ ከትክክለኛ ጊዜአቸው በፊት ሊሞቱ አይችሉም፡፡ የእግዚአብሔር ጊዜ ሲደርስና እነርሱም አገልግሎታቸውን ሲያጠናቅቁ እንዲገድላቸው ተፈቀደለት፡፡ ይህ አውሬ ሐሰተኛው ክርስቶስ ነው፡፡ አውሬው የሁለቱ ምስክሮች ሬሳ በመንገድ ላይ ተኝቶ ሁሉም እንዲያያቸው ማድረጉ እነርሱን ማዋረዱ ሲሆን ይህም በቀድሞ የእግዚአብሔር ቃል በተነገረባቸው ዘመናት ተከናውኗል( መዝ 79፡2,3)፡፡ ጠላት አጋጣሚውን ካገኘ በሙሉ ኃይሉ በመጠቀም የእግዚአብሔር የሆኑትን አገልጋዮች ያዋርዳል፡፡ እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች የሞቱባትና የተዋረዱባት ከተማ ከሰዶምና ከገሞራ ጋር ተመሳሳይነት ያላት፣ በከፍተኛ ሁኔታ በደል፣ የምግባር ውድቀት፣ እግዚአብሔርን አለመውደድና ሕዝብን የመጭቆን ሁኔታ የሚታይባት ናት፡፡ ጌታችን ኢየሱስ የተሰቀለባት ከተማም ከዚህ ጋር ተመሳሳይነት ያላት ናት፡፡ ምክንያቱም ሐሰተኛው ክርስቶስ ከፍተኛ ተጽእኖ እያሳደረ ስለሆነ ነው፡፡ ከላይ እንደተመለከትነው አገልግሎታቸው በታላቅ ተአምራት ሲታጀብ የነበረ ሁለቱ ወይራዎች አሁን ተገድለው ሬሣቸው በመንገድ ላይ ተጥሎ ሁሉም እየመጣ ያየው ጀመር፡፡ ጠላት የእግዚአብሔርን አገልጋዮች ሲያዋርድ እንደዚህ ነው፡፡
የእነዚህ ሰዎች ሬሳ የወደቀው በአንድ ከተማ ሲሆን ቃሉ ግን ከነገድ ከቋንቋ አህዛብ የሆኑ ሁሉ በመንገድ ላይ የወደቀውን የሁለቱ ምስክሮችን ሬሣ ለሶስት ቀን ያዩታል፡፡ እንዴት አድርገው በሁሉም ቦታ ያሉ ሰዎች ይህንን ሊያዩ ይችላሉ፡ እንግዲህ በጊዜ ከፍተኛ ስልጣኔ ስለሚሆን ምናልባት ሁሉም በያለበት ሆነው በቴሌቭዥን ወይም በሌላ የመገናኛ መንገድ ሊመለከቱት ይሆናል፡፡ ወይም ደግሞ ሕዝቦች ከተለያዩ ወገኖች ተውጣጥተው በወቅቱ እነዚህን ሰዎች ለማየት ሲሉ በኢየሩሳሌም የሚገኙበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል፡፡ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ በታላቁ መከራ ጊዜ ሰው ሁሉ የተደሰተበትን ሁኔታ የሚያሳይ ብቸኛው ታሪክ ይህ ነው፡፡ የምድር ወገኖች በእነዚህ ምስክሮች ሞት ምክንያት በጣም ይደሰታሉ ምክንያቱም ከዚያ በኋላ የእግዚአብሔርን የማዳን ወንጌል ስለማይሰሙ ነው፡፡ ልብ እንበል የወንጌል ሰባኪዎች፣ አስተማሪዎች ቅዱሳም ምስክሮች ሲወድቁና ሲዋረዱ ወንጌልን የመስበኩ ሥራ የሚቋረጥ ስለመሰለው አውሬውና ተከታዮቹ አጅግ አድርገው ይደሰታሉ፡፡ ይህኛው በምድር ላይ የመጨረሻው የሰው ልጆች ፈንጠዚያ ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ሌላ ደስታ የሚባል በምድር ላይ አይሆንም ወይም ያበቃል ማለት ነው፡፡ ይህ የሚገርም ነው፡፡
3. የሁለቱ ምስክሮች ትንሳኤ
በዚህ ክፍል የሚያስደንቀው ነገር ሁለቱ ምስክሮች ሞተዋል ተብለው ከነገድ ከቋንቋ እና ከየአገሩ ሰዎች ሁሉ ተሰብስበው ደስታቸውን ከገለጹ በኋላ እንደገና ተነስተው፣ ወደ ሕይወት ተመልሰው መታየታቸው ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ዘንድ የወጣው ሕይወት መንፈስ ለሞተው ሰውነታቸው ሕይወትን እንደሰጠ እንመለከታለን፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለሞተው ሕይወትን በመስጠት የሚታወቅ አምላክ ነው( ሕዝ 37፡5፣10፣ሮሜ 4፡17)፡፡ የሞቱ ምስክሮች በድን ሰውነታቸው በሰዎች ፊት በእግር መቆሙ በሞታቸው ለተደሰቱት ጠላቶቻቸው ሁሉ ድንጋጤ ሊፈጥር የሚችል ነው፡፡ የእግዚአብሔርንም ሆነ የሰውን የሆኑ ጠላቶችን እግዚአብሔር የሚያዋርደውና የሚስደነግጠው እንደዚህ ዓይነት ተአምራቶችን በማሳየት ነው፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን በዓይናቸው ከሚያዩት ድንቅ በተጨማሪ ከሰማይ የመጣው ድምጽ የበለጠ አስደንጋጭ የሚሆን ነበር፡፡ እንዲህ ነው የሚለው “ወዲዚህ ውጡ”፡፡ ከዚያም እነርሱም ለጣላቶቻቸው እየተመለከቱአቸው በደመና ወጡ፡፡ አውሬ ሐሰተኛው ወይም ሰይጣን መግደል ይችላል፣ ሬሳንም ማዋረድ ይችላል፣ ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚመጣውን ትንሳኤና በክብር መውጣትን ሊከለክል አይችልም፡፡ ተገድለው ሬሳቸው እንኳ እንዳይቀበር ተደርገው የተዋረዱና በውርደታቸው ጠላቶቻቸው የተደሰቱበት እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች ወደ ሰማይ የወጡት በእግዚአብሔር ድምጽ ነው፡፡ ይህ ድምጽ የጌታቸው የኢየሱስ ድምጽ ሊሆን ይችላል ምክንያቱም በራዕይ መጽሐፍ ውስጥ ለባሪያዎቹ ይገለጥና ይናገራቸው የነበረው የሞትንና የስዖልን መክፈቻ ቁልፍ የያዘውና በሰባቱ ወርቅ መቅሮች መካከል ይመላለስ የነበረው ኢየሱስ ነውና፡፡ ዛሬ በተለያዩ ሁኔታዎችና ምክንያ የተዋረዳችሁ ካላችሁ፣ የተሰበራችሁና የወደቃችሁ ካላችሁ፣ ከጠላቶቻችሁም ሲፈነጥዙባችሁ እያያችሁ ቅስማችሁ የተሰበረ ልባችሁ የወረደባችሁ ወገኖቼ ዛሬ ለእናንተ የምሥረች አለኝ፡፡ የሞትና የሲዖል መክፈቻ ቁልፍ ያለው ጌታ የናዝሬቱ ኢየሱስ ሞትን ድል አድርጎ ተነስቷል ፣ ውርደታችሁንም በክብር ይለውጥ ዘንድ አለ፡፡
እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች ወደ ሰማይ የወጡት በደመና ሲሆን ይህም “ሸክና ግሎሪ” ተብሎ የሚጠራውን የእግዚአብሔርን ክብር የሚያንጸባርቅ ነው፡፡ ደመና የእግዚአብሔር ክብር ምሳሌ ነው፡፡ እነርሱ ወደ ሰማይ የወጡበት ሁኔታ ከጌታ ከኢየሱስ አወጣጥ ጋር ይመሳሰላል፡፡ አንደኛ ሰዎች እያዩ፣ ሁለተኛ በደመና ነው የተወሰዱት( ሐዋ 1፡9)፡፡ ይህ የክብር መነጠቅ በብሉይ ኪዳን ከኤልያስ
መነጠቅ ጋር ተመሳሳይነት ያለው ነው(2ኛ ነገሥት 2፡11)፡፡ እንደዚሁም ደግሞ አማኞች በደመና እንደምንነጠቅ የእግዚአብሔር ቃል ይነግረናል( 1ኛ ተሰሎንቄ 4፡17)፡፡ በሞታቸው የተደሰቱ ፣ በውርደታቸውም የፈነጠዙና የቧረቁ ጠላቶቻቸው ዓይናቸው እያየ ፣ ጆሮአቸውም እየሰማ ሲነጠቁ ደግሞ ምንም ማለት አልተቻላቸውም፡፡ ቁጥር 13ን በምንመለከትበት ጊዜ የምድር መናወጥ 7000 ሰዎችን ሲገድል ሐሰተኛው ክርስቶስ ሊያድናቸው እንዳልቻለና በዚህ ያሉት ደግሞ ለእግዚአብሔር ክብር እንደሰጡ እንመለከታለን፡፡ ሰይጣን ለጊዜው ኃይል ያገኘ እና ያሸነፈ ይምሰል እንጂ እግዚአብሔር ግን ክብሩን ሳይወስድና ባሪዎቹንም ሳያከብር በፍጹም አይተውም፡፡ እንግዲህ ከሰባቱ ወዮዎች የሁለተኝ ወዮ የተጠናቀቀው አገልጋዮች ሞት በሕይወት፣ ውርደታቸውንም በክብር ለውጦ ራሱም ከጠላቶቹ ሁሉ ክብርን በወሰደበት አስደናቂ ክንውን ነው፡፡ ሃሌሉያ

Thursday, April 6, 2017

እንጀራው


በዚህ ሳምንት እኔና ውድ ባለቤቴ የወር አስቤዛችንን ( ቀለባችንን ማለቴ ነው) ለመሸማመት ከመኖሪያ ቦታችን ትንሽ ራቅ ብሎ ወደሚገኘው ገበያ አዳራሽ ሄድን፡፡ የገበያ ቦታው ሜድቴራኒያን ፉድ ማርኬት Mediterranean food market ተብሎ የሚጠራ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ከሌሎች ገበያ አዳራሾች ሁሉ ይልቅ ይኸኛውን አዘውትረው የሚጎብኙበት ትልቁ ምክንያት የአበሻ ምግብ ለመሥራት የሚያስችሉ ቅመማቅመሞች በየዓይነቱ ስለሚገኙበት ነው፡፡ ለምሳሌ ፡ በርበሬ፣ ኮረርማ፣ እርድ፣ ቀረፋ ፣ ጥቁር አዝሙድ፣ ምጥምጣ፣ ቡና፣ ወዘተ ሁሉም በየዓይነቱ ይሸጥበታል፡፡ ቅመሞቹ በትናንሽ ብልቃጦች እየታሸጉ በላያቸው ላይ ምንነታቸውን የሚያሳይ ጽሑፍና መለያ ቁጥር ከታተመባቸው በኋላ በተመደበላቸው መደርደሪያ ላይ በተርታ ተደርድረው ይገኛሉ፡፡ እንዲያው ባንገዛቸውም እንኳን እነዚያን ማየት ለዓይን ምግብ ነው፡፡ ታዲያ በአገር ቤት ሳለን እንደነበረው በትንሽ ብር ፌስታል ሞልቶ መመለስ ያለ እንዳይመስለን አደራ፡፡ በአንዲት ትንሽ ብልቃጥ የታሸገችው በርበሬ ዋጋ አይቶ በአገራችን ገንዘብ ካሰሉት ዋጋው ያስደነግጣል፡፡ ስለዚህ አንድ ነገር ለመግዛት ሲታሰብ በአገር ቤቱ ገንዘብ ማስላት አይታሰብም፣ ማስላቱም ተገቢ አይደለም፡፡ 
የአሜሪካኖች ምግብ በአጭር ጊዜ ውስጥ ያልታሰበ ቦርጭ እያሸከመ ስለሚያስቸግር ከዚህ ሁሉ እዳ ውድም ቢሆን የአገራችንን ምግብ ለምን አልበላውም በሚል እዚህ አገር ከገባንበት ጊዜ ጀምሮ ሽሮና እንጀራ ተለይቶን አያውቅም፡፡ ለታናሽ ልጃችን ፌቬን ደግሞ የአሜሪካኖች ምግብ ተመራጭ ብቻ ሳይሆን ከተመራጭ በላይ ነው፡፡ አልፈ አልፎ እንገዛላታለን እኛም የምንቀማምሰው በእርሷ ምክንያት ነው፡፡ ከፈቀድንላትማ ያለ እርሱ ባትበላ ደስታውን አትችለውም፡፡ እውነት መናገር ይሻላል የአሜሪካኖች ምግብ ሲጣፍጥ አይጣል ነው፡፡ ቢሆንም የሽሮን ውለታ መርሳት ጥሩ አይደለም ብለን ስለመከርናት እግዘር ይስጣትና እሺ ብላ ከእኛ ጋር የአበሻውን ምግብ በሥነሥርዓት እየበላችው ነው፡፡ ከምግብ ሁሉ ታማኝና ባለውለታችን ሽሮ ነው፡፡ መሸለም ቢያስፈልግ በመጀመሪያው የክብር መዳሊያ መጥለቅ ያለበት በሽሮ አንገት ነው፡፡ አንድም ቀን ሰልችቶን አያውቅን ፣ እኛም አንሰለቸውም፡፡ ይኸውና ሽሮአችን ባሕር ተሸግሮ በመምጣት የተለመደ አገልግሎቱን እየሰጠን ነው፡፡ ባለቤቴ ተዋበች ሌላ ማንኛውንም ምግብ ብትበላ እንጀራ ካልቀመሰች የሆነ ነገር የሚጎድልባት ይመስላታል፡፡ በፌቬንና በእርሷ መካከል ያለው ልዩነት በጣም ሰፊ ነው፡፡ እኔ ባለቤቴን አልፌ አልፎ እመክራታለሁ፡፡ ታበዥዋለሽ እላታለሁ፡፡ እምቢ ስትለኝ “ቃሉ ሁሉንም በልክ አድርጉ ይላል” ብዬ ልሰብካት ብሞክር የቱጋ ነው የጻፈው ትለኛለች፡፡ የተጻፈ ነገር ካለ ንገረኝ እንጂ ያልተጻፈውን አታንብብ ትለኛለች፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ አጠናን ዘዴ ውስጥ “አውድ” የሚባል ነገር መኖሩን በሰበብ በአስባቡ የነገርኩአትን ይዛ “አውድ ጠብቅ” እያለች ወደ እኔ ታነጣጥርብኛለች፡፡ በገዛ እጄ ስለ አውድ ነግሬአት ራሴው አፍ አጣሁ፡፡ እንዲያውም የእንጀራና የቡና ፍቅር እየባሰባት መሄዱን ሳይ “ይህ የእንጀራ ፍቅር በዝቷል፣ ወደ ሰማይም ሄደሽ እንጀራ እበላለሁ እንዳትይ እዚያ እንጀራ የሚባል ምግብ አይኖርም ይልቁንስ የተሻለና ከሁሉም የላቀ ሕይወት ነው የሚጠብቀን እንጂ” እያልኩ ሊሰብካት ቢሞክር አሁንም “ይህ ትምህርት ከእውነተኛው አስተምህሮ ጋር ስለጣጣሙ እርግጠኛ ሁን እንጂ እኔ መንግሥተ ሰማይ ሄጄ እንጀራ አልጋግርም የሚጋግርልኝም ይኖራል ብዬ አላስብም” ትለኛለች፡፡፡ ባለቤቴንና ልጀቼን ይህንን አታድርጉ ብዬ በቃል ጥቅስ ከመገሰጼ በፊት አውዱን በጥንቃቄ የመመልከት ግዴታ ውስጥ ገብቻለሁ፡፡ ያውም እኔው ራሴ አውድ context ስለሚባል ነገር ነግሬአቸው ያመጣሁት መዘዝ ነው፡፡ እኔ የሚቀለኝና ነጻነት የሚሰማኝ በመነቃቂያ ኮንፍራንስ ስሰብክ ነው፡፡ እዚያ ከየት አመጣኸው የሚል የለም፡፡ የተሳሳተም ቢሆን ተናግረው አሜን በሉ ሲባል አሜን የሚባልበት ቦታ ነው፡፡ እኔ እዚያም ቢሆን አውድ እጠብቃለሁ እንጂ ምክንያቱም ወደ ቤት ስመለስ ባለቤቴ “እሺ የዛሬው አገልግሎት እንዴት ነበር ታዲያ?" ብላ ሳትጠይቀኝ አልፋ አታውቅም፡፡ እኔም ‘ጌታ ይመስገን በጣም ጥሩ ነበር” እላታለሁ፡፡ እዚያጋ ቢያበቃ መልካም ነበር ግን አያበቃም፡፡ “ስለ ምን ሰበክ?” የሚለው ጥያቄ ይከተለኛል፡፡ ይህን ጊዜ ከስብከቴ መካከል ደግ ደጉን መርጬ በጥንቃቄ እነግራታለሁ፡፡ ባለቤቴ አገልግዬ ስመለስ በጥያቄ ማጣደፍ ብቻ ሳይሆን በጌታ የተሳካ የስብከት አገልግሎት እንዳቀርብ አጥብቃ ትጸልይልኛለችና ስለ እርሷ ጌታን አመሰግናለሁ፡፡ ታዲያ በእኔ ቤት መንፈሳዊ ነጻነት ፣ በነጻነት መስበክ፣ ጥቅስ እየጠቀስኩ አንዱን ከአንዱ ጋር አገናኝቼ ማሳመን በቀላሉ እልሆን እያለ መጥቷል፡፡ በመሆኑም ደስተኛ ነኝ፡፡ ባለቤቴንና ልጆቼን እግዚአብሔር ስለሰጠኝ ምስጋናዬም የላቀ ነው፡፡
ባለቤቴ ቡናንም ስትወድ አይጣል ነው፡፡ እኔ ደግሞ ቡና አልጠጣም፡፡ ጧትና ማታ ቡና ካላፈላሽ እያልኩ የማስቸግር ባል ባለመሆኔ ራሱ ልታመሰግነኝ ሲገባት “ባትጠጣ ሙሉ መብት አለህ፣ ማንም በግድ ጠጣ አይልህም፣ ደግሞ ብትጠጣም ችግር የለውም ለራሴ ሳፈላ እግሬ መንገዱን ትጠጣለህ” ትለናለች፡፡ይህ እኮ በእኛ ቤት የሴቶች እኩልነት ብቻ ሳይሆን የሴቶች የበላይነትም መኖሩንም ያሳያል፡፡ አሁን አሁን በተለይም ወተት በቡና የሚባለውን በትንሽ በትንሹ ስትሰጠኝ ቀየችና ለእኔ በማይገባኝ ሁኔታ የቡናውን መጠኝ ከቀን ወደ ቀን በዛ እያደረገች ምን አለፋችው በቡና ሱስ አስያዘቺኝ፡፡ አሁን በቁጥጥሯ ሥር ገብቻለሁ፡፡ በአገሬ ሳለሁ ለቡና ሱስ ያልተንበረኩ ሰው አሁን ከምሳ በኋላ ያቺን ወተት በቡና የምትለዋን ካልጠጣሁ ይደክመኝ ጀመረ፡፡ 
ለማንኛም እኔና ባለቤቴ ወደ ሜዲትራኒያን ገበያ አዳራሽ የሄድነው ጤፍ፣ ገብስና ቡና ለመግዛት ነው፡፡ እዚያ የኢትዮጵያ ቡናም አለ፡፡ባለቤቴ የምትፈልገውን ዕቃ እየመረጠች በጋሪው ላይ ስታስቀምጥ የእኔ ሥራ ጋሪውን እየገፋሁ ከኋላዋ መከተል ነው፡፡ እርሷ የመረጠችውን ብቻ ነው እንጂ የእኔ ምርጫ ውሃ አያነሳም፡፡ ከኋላዋ ሆኜ ያንን ጋሪ እየገፋው እያለ ዓይኔ በአንድ ነገር ላይ አረፈ፡፡ ከፊት ለፊታችን ባለው ጠሬጴዛ ላይ በሚያምር ንጹሕ ላስትክ ታሽጎ የተደረደረ ደስ የሚል ነገር፡፡ ምግብ ነው ታዲያ! ገበያተኞች አንዱ ከሌላው እየተከተሉ የሚያነሱት፡፡ ገበያ አዳራሹ የዐረቦች በመሆኑ ምክንያት ብዙ ዐረቦች ይገበዩበታልና እነርሱም ያንን ሲያነሱ አየሁ፣ ሶማሊያውያንም ፣ ሱዳናውያንም በየተራ እየመጡ ሲወስዱ አየሁ፡፡ እኔም ተጠጋሁና አይቼ ልቤን ደስ አለው፡፡ ለባለቤቴ አሳየሁአት፣ አየሽው ይህንን ነገር አልኩአት፡፡ ለካ እርሷ ከእኔ በፊት አይታዋለች ግን እንደ እኔው አልገረማትም፡፡ ነገሩ እንጀራ ነው፡፡ እንጀራ በዚህ ገበያ ሲሸጥ ከዚያም አልፎ ደግሞ ኢትዮጵያውያን ያልሆኑትም ጭምር ተሻምተው ሲወስዱ አታይም እንዴዬ አልኳት፡፡ ያውም እኮ ነጭ ወረቀት የመሰለ እንጀራ እኮ ነው፡፡ የእንጀራ ፍቅር የባለቤቴን ያህል ባይሆንም እንጀራን እወደዋለሁ ፡፡ የአገሬ ምግብ እንደዚያ ሲሸጥ በማየቴ ኩራት ኩራት አለኝ፡፡ በአገራችን የነጭ ጤፍ እንጀራ የሚበላው ሀብታም ሰው ቤት ነው ፡፡ ይህ ደግሞ ከንጣቱ ጋር ልስላሴው ራሱ ብላው ብላው የሚያሰኝ ነው፡፡ ነገር ግን እንጀራ ወዳድ ባለቤቴ ያሳየችው ቸልተኝነት አንድ ጥየቄ እንድጠይቃት አደረገኝ፡፡ ይህንን እንጀራ አልወደድሺውም አልኳት፡፡ እርሷም መልሳ እንዲህ አለችኝ “እንጀራ ይመስልሃል? ይህ እኮ እውነተኛ እጀራ ሳይሆን ዱቄቱን ሳልፍራይዜር ከሚባል ኬምካል ካር ቀላለቅለው ስለሚጋግሩ የነጣው በዚያ ምክንያት ነው የለሰለሰውም ለዚያ ነው፡፡ እውነተኛ እንጀራ ግን እንደዚህ አይለሰልስም አይነጣምም፡፡ ይህኛው ሁለትና ሦስት ቀን እዚህ ቢውል አይደርቅም አይሰባበርም፡፡ እውነተኛው እንጀራ ግን ጠሬጴዛ ላይ እንደዚህ አይቀመጥም ፣ በልዩ ጥንቃቄ በኮባና በሌሎች ቅጠሎች ተሸፋፍኖ በእቃ ውስጥ ነፋስ በማይነካው መልኩ ይቀመጣል፣ ይህኛው እንጀራ ከኬሚካሉ የተነሳ ለጤና ጎጂ ሲሆን እውነተኛው ግን በጣም ጤናማ ነው፣ ጤፋችን ብረት በተባለ ንጥረ ነገር የበለጸገ ስለሆነ ለጤና ጠቃሚ ነው፣ አሁን እኔ የጤፉን ዱቀት ወስጄ ስጋግረው የሚወጣው እንጀራና ይህኛው እንጀራ በምንም ሊገናኙ አይችሉም” አለችና አስዳችኝ፡፡ 
ከዛ በኋላ ራሴን ጠየቅኩኝ እነዚያ ሰዎች ታዲያ እንጀራ እንጀራ እያሉ የሚሻሙት ለምንድነው አልኩ፡፡ መልሱ እውነተኛውን እንጀራ ስለማያውቁ ነው፡፡መለስለሱንና መንጣቱን እንጂ በማስመሰል የተሠራ የሀሰት እንጀራ መሆኑን አላውቁትም ማለት ነው፡፡ ሐሰት መሆኑን የምታውቀው ኢትዮጵያዊቷ ባለቤቴ የእውነተኛው እንጀራ ጋጋሪ ኢትዮጵያዊት ስለሆነች ነው፡፡ በመሠረቱ እንጀራ ከመነሻው የኢትዮጵያውያን ባህላዊ ምግብ እንጂ የዓረቦችም የሶማሊያውያንም አይደለም፡፡ የሱዳኖችም ምግብ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያውያን ምግብ ነው፡፡ ስለዚህ ኢትየጵያውያን ሐሰተኛውን እንጀራ ከእውነተኛው የመለየት ብቃት አላቸው፡፡ ሌሎች ግን ይህ ብቃት ስሌለላቸው በብረት የበለጸገውን የጤፍ እንጀራ ሳይሆን ኬምካል የተሞጀረበትን ነጭ እንጀራ ይበሉታል፡፡ 
ከዚህ የተማርኩት አንድ መንፈሳዊ ቁም ነገር አለ፡፡ ዛሬ በቤተ ክርስቲያን የሐሰት አስተማሪዎችንና የሐሰት ትንቢቶችን፣ ተአምራቶችን እንዲሁ በቀላሉ ልንለያቸው አንችልም፡፡ እውነተኛውን ትምህርት ካላወቅን በቀላሉ እንወሰድባቸዋለን፡፡ የሐሰት ትምህርቶች ይመርካሉ፣ ብዙዎች ይከተሉአቸዋል፣ ያደንቁአቸዋልም፡፡ ነገር ግን ከእውነተኛው ትምህርት ጋር ሲያስተያዩት ውስጣቸው በገዳይ መርዝ የተመላ ነው፡፡ እውነተኛው እንጀራ ዋጋው ውድ ሲሆን ሐሰተኛው ደግሞ ቀለል ባለ ዋጋ እንደሚገኝ ሁሉ የስህተት ትምህርትቶችና ትንቢቶች እንደ ልብ ይገኛሉ፡፡ ሐሰተኛውን ከእውነተኛው ለመለየት ቀላሉ መንገድ እውነተኛውን ትምህርት በሚገባ ማወቅ ነው፡፡ባለቤቴ ኢትዮጵያዊ በመሆኗ እውነተኛውን እንጀራ ስለምትጋግር ሱዳናውያንና ሶማሊውያን የሚገዙት ሳልፍራይዜር ያለበት እንጀራ እንደምግብም አልታይ አላት፡፡ እኔም ምስጥሩም ስለማላውቅ ልቤ በዚያ እንጀራ ተማርኮ ነበር፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ቤተ ክርስቲያን በሐሰት ትምህርትና በጤናማ ትምህርት፣ በሐሰት ትንቢትና በእውነተኛ ትንቢት ፣በሀሰት ተአምራትና በእውነተኛው ተአምራት መካከል ያለውን ልዩነት ምዕመናን ተረድተው በሐሰተኛው መርዝ እንዳይጠቁ እውነተኛውን ትምህርት በማስጨበጥ ልትተጋ ይገባታል፡፡ ፈጣሪ በቸርነቱ ይጠብቀን ይርዳንም ፡፡ አሜን

ረጅም ነኝ ግን ሰሞኑን ቁመቴ የማጠሩ ነገር ኣሳሰበኝ፡፡




ረጅም ነኝ ግን ሰሞኑን ቁመቴ የማጠሩ ነገር ኣሳሰበኝ፡፡
እኔ ስለራሴ የተረዳሁትና ሰዎችም የሚመሰክሩልኝ በጣም ረጅም እንደሆንኩ ነው፡፡ እንዲያውም በቤተሰባችን ብቻ ሳይሆን በተወለድኩበት አካባቢ እንደ እኔ ያለ ረጅም ሰው የለም ማለት እችላለሁ፡፡ ለቀበሌያችንና ለወረዳችን የመረብ ኳስ ስጫወት በጣም ነበር የማስደስተው፡፡ በቤተክርስቲያን ስናገለግልም መዘምራን በደረጃ ላይ ሲቆሙ እኔ ከፊት ባለው ደረጃ ላይ ከቆምኩኝ በሶስተኛ ደረጃ ላይ ከቆሙት ጋር እኩል እሆናለሁ፡፡ በኳየር አገልግሎት ጊዜ ከኋላ መቆም የማልፈልገው ጭንቅላቴ ኮርኒሱን ስለሚነካብኝ ነው፡፡ ስለዚህ ፊቴን ወደ ሌሎች መዘምራን አዙሬ ጎኔን ለጉባኤው ሰጥቼ ከዳር በኩል እቆማለሁ፣ ከዚያ መዘምራኑ ከያዙት ከየትኛውም ደብተር ላይ እያየው መዘመር እችላለሁ፡፡
ወደ ስብከት አገልግሎት ስገባ ከመዘምራን ተለየሁ እንጂ መዘምራን ሲያገለግሉ ደስ ይለኛል፡፡ የዛሬውን አያርገውና ኳየሮች የሚዘምሩት መዝሙር ለረጅም ጊዜ ከልብ አይጠፋም ነበር፡፡ በመከራም ቀን እንደ ትንቢት ቃል የቅዱሳንን ልብ ደግፏል፡፡ ለምሳሌ “ድሉ የጌታችን ነው ፣ድሉ የአምላካችን ነው ድሉ” የሚለውን መዝሙር የሰማሁት በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በ1973ዓ.ም ማለትም ከ36 ዓመት በፊት ነው፡፡ ሌሎችም በጊዜው የተዘመሩ መዝሙሮች አይረሱኝም፡፡ በጊዜው የወላይታ ቤተ ክርስቲያን በመራራ ስደት ውስጥ ሳለች የመሠረተ ክርስቶስ ቤክ መዘምራን ወደ ቦታው ተንቀሳቅሰው በ”ኦቶና” ዓመታዊ ኮንፍራንስ ላይ ሲዘምሩና ሕዝቡ አብሮአቸው በእምባ ሲራጭ እኔና እኩያዎቼ ከመድረኩ ፊት ለፊት በመሬት በተጎዘጎዘው ሣር ላይ እንድንቀመጥ አስተናጋጀች ስላስገደዱን እዚያው ሆኜ ነው የሰማሁት፡፡ ይህ መዝሙር ዛሬም ለእግዚአብሔር ሕዝብ ትኩስ መልእክት ያለው ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በመዝሙር የማገልገል ጥማት ውስጤ ገብቶ ስለነበር እስከአሁን አራት በሚያህሉ ኳየሮች አገልግያለሁ፡፡ ታዲያ መዘምራኖቹ በቁመቴ ብቻ ሳይሆን ድምጼም ዝማሬውን ስለሚያተራምስባቸው ይቸገሩብኝ ነበር፡፡ እኔም ከመዘምራን ጋር ባገለገልኩባቸው ጊዜያቶች ቅር ያለኝ ነገር ቢኖር አብሬአቸው ፎቶ መነሳቴ ነው፡፡ ከእነርሱ ጋር የተነሳሁአቸው ፎቶዎቼ አብዛኛዎቹ ወይ ከአንጌቴ፣ ወይ ከፍንጫዬ በላይ የላቸውም፡፡ ጌታ ኃጢአቴን ሁሉ ይቅር እንዳለኝ መጽኸፉ ስለነገረኝ እኔም ይቅር ብዬአቸው ነው እንጂ ያኔ ፎቶ ባነሱን ሰዎች ላይ ቂም ቢጤ ሁሉ ቋጥሬባቸው ነበር ፡፡አጫጭሮቹ ከእግራቸውም ከጭንቅላቸውም በሌንሳቸው እንዲገቡ ብለው እኔን ከአጭሮቹ ትክክል ቆርጠውኛልና፡፡
በቤተ ክርስያቲናችን የበረውን ትልቁን ፑልፒት አጫጭሮቹ ሰባኪዎች አይወዱትም ነበር፡፡ ያንን ፑልፒት ያስቀየረን አንዱ የእነርሱ ብሶት ነው፡፡ ፑልፒቱ ስለሚከልላቸው ከሥሩ ለእነርሱ ተብሎ የተዘጋጀ ኩርሲ አይነት ነገር ስላለ ሲሰብኩ እዚያ ላይ ይወጣሉ፡፡ ከዚያ እንደምንም ብለው ከደረታቸው በላይ ይታያሉ፡፡ ሊሰብኩ እዚያ ላይ ወጥተው "እታያለሁ?"ብለው ጉባኤውን የጠየቁ ሁሉ ነበሩ ብል ታምኑኛላችሁ? አሁን ብዙ ሲዘመር አልሰማውም እንጂ አንድ "መሸሸጊያ ዋሻ 2x መከታ ጋሻችን" የሚል ተወዳጅ መዝሙር ነበርና ከምንወዳቸው ሽማግሌዎቻችን አንዱ ይህን ምዝሙር እያዘመረ ጉባኤውን ሲመራ በተለይ መሸሸጊያ ዋሻ የሚለው ቃልጋ ሲደርሱ በዚያ ፑልፒት ሥር እየተደበቀና ከዚያም ብቅ እያለ ሲመራ ጥሩ ምሳሌ ይሆንለት ነበር:: ታዲያ ከመድረኩ ጫፍ ወደ ሌላው ጫፍ የሚሯሯጥ ሰባኪ ያ ፑልፒት አይመቸውም፡፡ እኔ ስሰብክ ግን ያንን ኩርሲ ስለማልፈልግ ወደ ጎን አሽቀነጥረውና መሬቱ ላይ ቆሜ እንኳ ጉባኤው ከደረቴ ሳይሆን ከወገቤ በላይ ያየኝ ነበር፡፡ አስቡ እንግዲህ! የቤተክርሰትያናችን አባቶች ቅጽል ስም ሁላ አውጥተውልኛል፡፡ በጣም የምናከብራቸው የነበረ ጋሼ ጥላሁን “ሰማይ ዛፉ” ፣ “ብቅል አውራጅ”፣ ይሉኝ ነበር፡፡ ጋሼ ወልደአምላክማ በስሜ ከሚጠሩኝ “ቀውሌ” ሲሉኝ ይቀላቸዋል፡፡ ጋሼ ማሞ ደግም ልክ እንደ ጋሽ ጥላሁን “ሰማይ ዛፉ” እንደሚሉኝ ልንገራችሁ፡፡ የማታውቁኝ ወገኖቼ ምን ያህል ረጅም እንደሆንኩ በዚህ ይግባችሁ ብዬ ነው፡፡
በረዶ ካልዘነበ በቀር አንዳድ ጊዜ ከባለቤቴ ጋር በእግር እንጓዛለን( ባለንበት አገር ዎክ ይባላል)፡፡ ታዲያ የምንጓዘው እያወራን ነው፡፡ ምን አለፋችሁ ባለቤቴ ቀስ ብላ የመናገር ባሕሪይ ስላላት እሷ የምትለው እኔጋ አይደርስም፡፡ እኔ ከላይ ሆኜ ስለምናገር እያንዳንዱን ነገር ትሰማለች፡፡ ስንቸገር ለምን እኔና አንቺ በስልክ አናወራም እላታለሁ፡፡ አብረን እየተጓዝን ወደ አንድ የገበያ አዳራሽ ስንደርስ እርሷ የሆነ ዕቃ እንግዛ ብላኝ ወደ ውስጥ ስንገባ ህንዳዊው የሱቁ ባለቤት አላየንም ነበር ግን ኮሜዲኖው አጠገብ ቆመን ስናናግረው በሆነ ወንበር ላይ የቆምኩ መስሎት አንገቱን አሰግጎ ወደ ጫማዬ አየኝና "በምን ላይ ቆመህ ነው ?" ያለኝ ቀን እንዴት እንደሳቅኩ ልነግራችሁ አልችልም፡፡ የሰውዬው አባባል በአዲስ አበባ ቦሌ ቃለ ሕይወት ቤክ አገልግዬ ስመለስ አንዲት የሀብታም ልጅ የምትመስል ከእናቷ ጋር ስትሄድ ነበርና በአጠገባቸው ሳልፍ አይታኝ እንደመሞላቀቅ አድርጎአት "ወይኔ ጂሴስዬ....ሰውዬው ምን ያክላ.....ል" ማለቷን አስታወሰኝ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ተቃራኒውም ይገጥመኝና አቤት የጌታ ሥራ እንዴት ግሩም ነው እላላሁ፡፡ ለአገልግሎት ሌላ ቦታ ካልሄድኩ በግራድ ራፒዲስ ከተማ ወደሚገኘው ካልቬሪ ቤተክርስቲያን ሄደን የጌታን ቃል እንሰማለን፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ ትልቅ ከመሆኑ የተነሳ ስድስት የሙጪያና የመግቢያ በሮች አሉት፡፡ አንድ ቀን ግን ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ስንገባ የመጀመሪያውን ፈረቃ ተካፍለው የሚወጣውና ሁለተኛውን ለመካፈል የምንገባው ሰዎች ዌስት ጌት (የምዕራቡ መግቢያ በር) በኩል ባለው በተላለፊያ ላይ ተገናኘን፡፡ ታዲያ በፈረንጆች አካባቢ ረጅም ሰውና ሽማግሌዎችን ማየት እንደ ልብ ስለሆነ እንደ እኛ አይገርማቸውም፡፡ ግን ያን ቀን የሚወጣው ሕዝብ ሲወጣ እኛ ደግሞ ስንገባ ከፊት ለፊቴ አንዲት ዕድሜዋ በግምት ከ25-30 ውስጥ የሚሆናት ወጣት ሴት በሕዝቡ መካከል ወደ እኛ አቅጣጫ ትመጣ ነበር፡፡ ከሰው ሁሉ ከፍ ብለን የምንታየው እኔና እርሷ ብቻ ነበርን፡፡ ግን ሆን ብላ ወደ እኔ መጣችና በአጠገበ አለፈች፡፡ ታዲያ ምን አለፋችሁ ወደ አናቴ ቁልቁል እያየችኝ ስታልፍ አንዱ ሽማግሌ ፈረንጅ ተክ ብሎ ሳቀ፡፡ አንተንም የሚበልጥ መኖሩን እወቅ የሚል ይመስላል፡፡
እኔም ይህንን ሁሉ የዘከዘኩት በቁመቴ ላዝናናችሁ ወይም ላስቀናችሁ አይደለም፡፡ ቁመቴ 6.5 ሃይት መሆኑ በህግ ተረጋግጦ በመንጃ ፈቃዴና በሌሎች ሕጋዊ ሰነዶች ላይ ሰፍሮ እያለ ሰሞኑን አጭር መሆኔ ሲነገረኝ ክው ብዬ ስለ ደነገጥኩኝ የሚያጽናና መልእክት ወይም ምክር ካላችሁ እንድትለግሱልኝ በማለት ነው እንጂ፡፡ አጭር መሆኔ የተነገረኝ ከሀኪም ወይም ከሌላ ባለሙያ አይደለም፡፡ ካለሁበት አገርም አይደለም፡፡ ከነቢያት አገር ከኢትዮጵያ ነው፡፡ አንድ ሰው በቫይበር ግሩፕ ፈጠረና እኔንም እዚያው ውስጥ አካቶኝ መልእክት ስለላከብኝ ማን አንደሆነና የእኔንም ስልክ ከየት እንዳገኘ እንዲነግረኝ መልእክት ላኩበት፡፡ ከዚያ በዚያው በቫይበር ደውሎልኝ ማእረጉን በማስቀደም ስሙን ነገረኝ፡፡ ስሙን ለጊዜው ላቆይና ወንድማችን በማዕረጉ ነቢይ ነው፡፡ ፕሮፌት …….. እባላለሁ ከኢትዮጵያ አለኝ፡፡ ማዕረግ ያልኩበት ምክንያት አሁን አሁን ወንጌላዊነት ፣ መጋቢነት ፣ ወይም ሓዋሪያነትና ነቢይነት ለአገልግሎት እንደተሰጠን የጸጋ ስጦታ ሳይሆን እንደ ማዕረግ ስለሚታይና ሰዎችም በዚያ ማዕረግ ካልተጠሩ ስለሚከፋቸው ነው፡፡ እንግዲህ አሳብ እየተለዋወጥን እያለ ጌታ ስላገናኘን አመሰገነና በሰዓቱ እግዚአብሔር ስለ እኔ የሚያሳየውን ነገር ስላለው ልነግረኝ ፈቃደናነቴን ጠየቀኝ፡፡ ፕሮፌት ነኝ ስላለ እና እኔም የነቢያትን አገልግሎት ስለማከብር ንገረኝ አልኩት፡፡ ብዙ ነገር ነገሮኝ ያንን ሁሉ በምልክት ሊያጸናልኝ ፈልጎ ማረጋገጫ በምልከት ይደረድርልኝ ጀመር፡፡ “አንደኛ፣ በ1996 ዓ. መጨረሻና በ1997 መግቢያ ላይ በሕይወትህ አንድ ነገር ሆኗል፡፡ ሁለተኛ፣ አንተ ጥቁር ሰማያዊ መኪና አለችህ፡፡ ሦስተኛ፣ በግራ እግርህ ከጉልበትህ በታኝ ቆስሎ የዳነ ምልክት አለብህ፡፡ አራተኛ አንተ ረጅም ሰው አይደለህም በቁመትህ ከአጭር ሰው ትንሽ ከፍ ትላለህ፡፡ ይህንን የምነግርህ እምነት እንዲሆንህ ነው አሜን በል፣ ” አለኝ፡፡ እኔም አሜን አልኩ፡፡ ለምን አሜን አልክ አትበሉኝ
ስለ ቁመቴ ማጠር ስሰማ በጣም ደነገጥኩ፡፡ መልሼ “እኔ እኮ በጣም ረጅም ሰው ነኝ፡፡ እንዲያውም ድሮ ከጋምቤላ አካባቢ መጥተው ለአየር ኃይል መረብና ቅርጫት ኳስ የሚጫወቱ ረጃጅም ሰዎች ነበሩ:፡ ወይም ከቦረና ነገሌ መጥተው በመረብ ኳስ ሜዳ ያገኘናቸው ሰዎች ካልሆኑ እሰከአሁን በቁመት የሚያክለኝ ሰው አልገጠመኝም፣ አንተ ደግሞ ከአጭር ሰው ትንሽ ከፍ እንደምል ትነግረኛለህ፡፡ ነገሩ እንዴት ነው?” ስለው፣ “እንግዲህ እኔ የማውቀው ነገር የለም ጌታ ያሳየኝ ይህ ነው” አለኘኝ፡፡ የቁጣ መልስ ስለመሰለኝ ጨዋታችንን እዚውጋ አበቃን፡፡ ደግሜም ያንን ሰው አላገኘሁትም፡፡
ታዲያ ምን አሳሰበህ የሚል ቢኖር ከላይ በተጠቀሱት ዓመታት በሕይወቴ የሆኑ ብዙ ነገሮች ነበሩና ትክክል ነው ብዬ ተቀበልኩ፡፡ በእግሬም ላይ ገጣባ መኖሩ እውነት ነው፡፡ በልጅነቴ የአጋም ፍሬ ለመብላት ብዬ ዛፍ ላይ ወጥቼ ከአንዱ ዛፍ ወደ ሌላ እየተሸገጋርኩ እያለ የቆምኩበት እንጨት በመሰበሩ ከከፍታ ላይ ተወርውሬ ስወድቅ ከታች የቆመው ሹልና ደረቅ እንጨት ተቀብሎኝ እግሬ ውስጥ በመሸንቀሩ ምክንያት በጣም ቆስዬ ነበርና ያ ስድን ገጣባው እዚያ አለ፡፡ መኪናዬም ጥቁር ሰማያዊ ነች፡፡ እነዚህ ምልክቶች ልክ መሆናቸውን ሳይ ነው የደነገጥኩት፡፡ ይህን ሰው ከማግኜቴ ከሁለት ሳምንታት በፊት ወደ መታጠቢያ ቤት ስገባ የበሩ የላይኘው ጉበን አናቴን ደርግሞት ስለነበር ያ አሳጥሮኝ ይሆን እንዴ ብዬም አሰብኩ፡፡ ደግሞ የተናገረው ጌታ ነው ሲለኝ እንዴት አልጨነቅም? ቁመቴን የሰጠኝ ጌታ እንደሆነ ሙሉ በሙሉ አምናለሁ፡፡ በቤተ ክርስቲያኔ ከእኔ ጋር አብሮ እንዲሠራ የተመደበ መጋቢ ነበርና ሰዎችን ለመገብኘት አብረን ስንሄድ እርሱ አጭር ብቻ ሳይሆን ሆዱም ላይ ቦርጭ ነገር ጣል ስላደረገችበት እንዲያው ድቡልቡል ነው፡፡ ታዲያ አንድ ቀን አብረን ስንሄድ የእርሱ አባት በርቀት ሆነው አይተውን ኖሯልና ለምን ከዚያ ከረጅሙ ጓደኛው ጋር ይሄዳል ቢቀርበትስ ምን አለበት ብለው እቤታቸው ያወሩትን ወንድሙ ሲነግረን አይዞህ ብዬ አጽናንቼዋለሁ፡፡ አንተንም እኔንም እግዚአብሔር ግሩምና ድንቅ አድርጎ ፈጥሮናለልና ከእኔ ጋር ለመሄድ አትፍራ እለው ነበር፡፡ እጥረቱን ባደንቅለትም በሆድ ላይ ስለሚከመረው ቦርጭ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ሁሉ እነግረዋለሁ፡፡ አጭር ሰው ቦርጭ ከበዛበት ደረቱ ላይ ይወጣበትና ወደኋላ ይለጥጠዋል፡፡እንዲያውም በእርሱ ቁመት ልክ ሆነው በጣም ቦርጫም የነበሩ አቢዬ ደመቀ የሚባሉ የእኛ አካባቢ ሰው ከቦርጫቸው መብዛት የተነሳ ሆዳቸውን ወደላይ የሚያዩ ይመስላሉ፡፡ ታዲያ አብዬ ደመቀ ጫማቸውን ማየት ስለማይችሉ ጫማቸውን ሲያስጠርጉ ሊስትሮዎቹን በጣም ሲያስጠነቅቁአቸው "ጫማዬን በደንብ ጥረጉልኝ ፣ እኔ ባላይ እግዜር ያያችኋል" ይሉ እንደነበር ሁሉ ነግሬው እንደ እርሳቸው እንዳይሆን አስጠነቅቀዋለሁ-- ከዚያ ውጭ አጫጭሮች በጣም ያስፈልጉናል እነርሱ ባይኖሩ ማን ረጅም ይለናል? እኛስ ባንኖር እነርሱንስ አጭር ማለት እንዴት ይቻላል? አንዳችን ለሌላችን እናስፈልጋለን ማለት ነው፡፡ እኔን እግዚአብሔር ግሩምና ድንቅ አድርጎ በመፍጠሩ እያመሰገንኩ ስኖር ሳለ ቁመቴ ማጠሩን ከነቢይ መስማቴ እንዴት አያስደንግጠኝ? ደግሞ ረጅም መሆኔን ነግሬው ማብራሪያ ሲጠይቀው “እኔ የማውቀው ነገር የለም እግዚአብሔር ያሳየኝን ነገርኩህ” ማለቱ በበለጠ እንዳስብ አደረገኝ፡፡ ከጌታ የተቀበልኩትን ቁመት ምንም ሳልጠቀምበት ስለቀረሁ ተወሰደብኝ ማለት ነው ብዬም አሰብኩ፡፡ ያንን ጋሽ ጥላሁንና ጋሼ ማሞ ያሉኝን ብቅል እንኳ ሳላወርድ ቀርቼ ይሆናል እያልኩ ሌሊቱን ሙሉ አሰብኩ፡፡ በአንድ በኩል ከብቅል ጋር ምንም ጉዳይ እንዳይይኖረኝ ዳግም ተወልጃለሁና ብቅል ባይወርድም ተጠያቂ አልሆንም ብዬ ልጽናና ሞከርኩ፡፡ነቢይ ኢዩ ጩፋ ቁመታቸው ያጠረ ሰዎችን አስረዝማለሁ በማለት ሲዳክር ያየሁት ስለነበረ እግዚአብሔር አጫጭሮችን እያስረዘመ እኔን ረጅሙን የሚያሳጥረኝ ምን አግኝተብኝ ይሁን ብዬ አሰብኩ፡፡ ቃሉ "ለሰው ሁሉ ከሚሆን በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም"( 1 ቆሮ 10፡13) ይለናል፡፡ ግን እኔ እኮ ለሰው ሁሉ ከሚሆን በቀር የተለየ ፈተና ገጥሞኛል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር አስከ አሁን ድረስ ከእኔ በቀር ቁመቱን ያሳጠረለት ሰው አልሰማሁም አላየሁም በማለት ከጌታ ጋር በቃሉ ተሟገትኩ፡፡
ጠዋት እንደምንም ነጋልኝና ቁመቴን ለማየት ወደ ማስታወትጋ ሄድኩ፡፡ እቤታችን ያለው ማስታወት ከደረት በላይ እንጂ ሙሉ ቁመት ስለማያሳይ አልተሳካልኝም፡፡ ነገር ግን ባለቤቴ ሶፋችን ላይ ቁጭ ብላ መጽሐፍ ቅዱስ እያነበበች ሳለ ጠጋ ብዬ በስሟ ጠራሁአትና “ቁመቴ ማጠሩ አያሳዝንሽም?” አልኳት፡፡ ያንን ቃል ስደግምላት አይኗን ከመጽሐፉ ነቀለችና ወደ እኔ አየት ካደረገች በኋላ ወደ ንባቧ ተመለሰች፡፡ አሁንም እንደገና ጠየቅኳት ፡፡ ከዚያ እንዲህ አለቺኝ፡፡ “ምን ሆነህ ነው ደግሞ ዛሬ? ብላ ወደ ንበቧ መለስ አለች ወዲያው ደግሞ ወደ እኔ አየት አደረገቺኝና “ትላንት የት ሄደህ ነበር? ሰሞኑን የሆነ ቦታ ሄደሃል ማለት ነው? አለችኝ፡፡ እግዚአብሔር ቁመቴ ማጠሩን በነቢይ በኩል ተናረኝ ስላት የሳቀቺው ሳቅ ራሱ አስደነገጠኝ፡፡ እኔ የቃሉ አስተማሪ ሆኜ በዚህ መታሌለን እንደ መንፈሳዊ ጅልነት አድርጋ ወሰደቺውና “እግዚአብሔር ሥራ ጨረሰና የአንተን ቁመት እየለካ መዝናናት ጀመረ ማለት ነው?” አለች፡፡ እንግዲህ ነቢያት እውነተኞች ናቸው.፣ ከእግዚአብሔር ናቸው የሚባለው በምልክት የሚነገረው ነገር ካለንበት አካላዊና ማህበራዊ ነገሮቻችን ጋር መግጠሙን ስናይ አይደል? ያ ነቢይ የነገረኝ ምልክት አብዛኛው ትክክል ነው፡፡ ግን ግልጥ የሆነውን ከኢትዮጵያ እስከ አሜሪካ ድረስ ያለው ሕዝብ በአደባባይ የሚያየውን ረጅሙን ቁመቴን አጭር ያለው እግዚአብሔር ነው ሲባል ማመኔ ባለቤቴን ምን ነካህ ቢያስብላት ምን ጥፋት አለባት?እኔም ሳስበው እግዚአብሔር ስለ እኔ የመኪና ቀለምና የቁመቴ ጉዳይ ዋና አጀንዳው አለመሆኑን የነቃሁት ብዙ ከለፋሁ በኋላ ነው፡፡ ባለቤቴ ያንን ጥያቄ ባትጠቀኝና ከእኔ ጋር ብትደነግጥ ምን ልንሆን እንደምንችል ገምቱ፡፡
ከዚህ የምንረዳው ሐሰተኞች ነቢያቶች የሚባሉት ውሸት ብቻ የሚናገሩ እንዳይደሉ ነው፡፡ ሐሰተኞች እውነት በሚመስሉ በርካታ ነገሮች ውስጥ ሐሰተኛ መርዛቸውን ሸፍነው ስለሚያቀርቡ ሐሰትነታቸውን መለየት ቀላል ሥራ አይደለም፡፡ በሰሙት ነገር ወዲያው የሚወሰዱ የእኔ ቢጤዎቹ በቀላሉ ይመረዛሉ፡፡ የሚገርመው ነገር ያ ነቢይ በቫይበር ግሩፕ ካካተታቸው ሰዎች ውስጥ የማውቀው አንድ ወዳጄ ስለነበረ መደወል አስፈከገኝ፡፡ ስለ ሁኔታው ሳጫውተውና ነቢይ ነኝ ስለተባለውም ሰው ያውቅ እንደሆነ ብዬ ስጠይቀው የነገረኝ ነገር በበለጠ አስደመመኝ፡፡ በአገር ቤት እያለ እንደሚያውቀውና ጥሩ የሆነ የአገልግሎት ሕይወት እንደነበረውም አጫወተኝ፡፡ ነገር ግን አሁን የሰዎችን ፌስ ቡክ እየወሰደ ከዚያ መረጃዎችን ከሰበሰበ በኋላ ጌታ ተናገረኝ እያለ ወደ ሰዎች እንደሚደውል አስረዳኝ፡፡ ይህ ማለት የእኔ መኪና ቀለም ጥቁር ሰማያዊ መሆኑ የተነገረው ከጌታ ሳይሆን ከፌስ ቡክ ነው ማለት ነው፡፡የቁመቴም ጉዳይ ቢሆን ከውድ ባለቤቴ ጋር ሆኜ የተነሳሁትና ለቫይበር ፕሮፋይል ያደረግኩት ፎቶ በእርግጥም የአጭር ሰው ይመስላል ፡፡ ከእርሷ ጋር እኩል ለመሆን በደረጃ ላይ ሰበር ብዬ የተነሳሁት ስለሆነ ነቢዩ ከዚያ ሊያይ እንደሚችል ገባኝ፡፡ አንዳንዶች መዘምራን ቅኔና ወይም ዜማ ከዓለማዊ ዘፈን በመቅዳታቸው እነርሱም በዘመሩበት አማኞች በየሰፈሩ በመሰደባቸው የመጣብን ቁስል እያመረቀዘና እየጠዘጠዘን ባለበት ጊዜ የትንቢትን መልእክት ከፌስ ቡክ የሚቀዱ ደፋር ነቢያት የሚያታልሉን አጋጣሚ መፈጠሩ አስተክዞኛል፡፡ በዚህ ዓይነት ሁኔታ የተታለሉ ስንቶች ይሆኑ? ምን ይበጃል ትላላችሁ?
LikeShow more reactions
Comment

Thursday, February 23, 2017

     በአገልግሎታችን ቅዱሳንን እንዴት መጥቀም እንደሚገባን ( 2017-35)
                                                                                                   

                                                                                           ከመጋቢ ሳሙኤል ሾንጋ

እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር 1993 ዓ.ም. በደቡብ ሱዳን ከፍተኛ ድርቅ በመከሰቱ ምክንያት የበርካታ እንስሳትና የሰው ሕይወት ጠፍቶ ነበር፡፡ በጊዜው የተከሰተው ተፈጥሮአዊ አደጋ በጣም አስከፊ በመሆኑ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት/United Nations  በጉዳት ላይ ለነበረው ሕዝብ ሰብአዊ ርዳታ እንዲሰጡ የተለያዩ ዘርፍ ባለሙያ ሰዎችን ወደ ደቡብ ሱዳን መላኩ ይታወሳል፡፡ በጊዜው የህክምና ባለሙያዎች፣ የሰብአዊ ርዳታ ሰጪ አካላት ወዘተ  መድኃኒት፣ ምግብና ሌሎች አሰፈላጊ  ቁሳቁሶችን ይዘው ወደ ቦታው ተንቀሳቅሰዋል፡፡ በወቅቱ ከተንቀሳቀሱት ውስጥ ዓለም አቀፍ ጋዘጤኞችም የነበሩበት ሲሆን ታዋቂ ፎቶጆርናሊስት ደቡብ አፍሪካዊው ኬቪን ካርቴር ይገኝበታል፡፡ ኬቪን ከልዑካን ቡድኑ ጋር ወደ ደቡብ ሱዳን ከደረሰ በኋላ በካሜራው ያነሳቸው ፎቶግራፎች በጣም ተደናቂነትን ያኙና በሥፍራው ስለነበረው የድርቅ ሁኔታ በጣም በኃይለኛው ሁኔታ የሚገልጹ ነበሩ፡፡ ለምሳሌ ልጆች ውሃ ከማጣታቸው የተነሳ ላሞች ሽንት ሲሸኑ ከስር ቀርበው ሲጠጡ፣ ወይም ጭንቅላታቸውን አስጠግተው ሲታጠቡ ኬቪን በካሜራው አንስቷል፡፡ ከሁሉም ፎቶዎቹ ይልቅ ግን በወቅቱ ሁሉንም ያስደነቀችና የኬቪንንም ዝና እጅግ ያወጣችው ፎቶ ሌላ ነበረች፡፡ አንዲት በረሀብ በጣም ከመጎዳቷ የተነሳ ሰውነቷን መሸከም ያቃታት፣ በአካላቷ  ላይ ምንም ሥጋ የሌላት ፣ ቆዳዋና አጥንቷ የተጣበቀ የሚመስል ሕጻን ልጅ በአንድ በረሀማ በሚመስል ቦታ  ፣ በሰውነቷ ላይ ምንም ልብስ ሳይኖር ራቁቷን ሆና ጭንቅላቷን በሁለት እግሮቿ መካከል አድርጋ በግምባሯ ተደፍታ ፣  በአጠገቧ ምንም ሰው ሳይኖር ነገር ግን ከኋላ አንድ የፈረጠመ ጆፌ አሞራ ተንሰፍስፎ ሲጠብቃት ሳለ ኬቪን በካሜራው አነሳና ለዓለም ሕዝብ አሳየ፡፡ ያ ፎቶግራፍ በደቡብ ሱዳን የነበረው ድርቅ አስከፍነቱ ምን ያህል ጥልቅ እንደሆነ የሚያስረዳ በመሆኑ በጊዜው የዓመቱ ምርጥ ፎቶ ተብሎ ተመረጠ፡፡ በዩናይትድ ስቴት ኦፍ አሜሪካ ያለው በሥነ ጽሑፍ፣ በጋዜጠኝነት፣ በሙዚቃ ድርሰት የላቀ አስተዋጽኦ ላበረቱት ሽልማት የሚሰጠው Pultizer price የተሰኘው ድርጅት የሚሰጠውን ሽልማት ያሸነፈ አስደናቂ ፎቶ ሆኖ ተመረጠ፡፡ ከዚያ በኋላ የኬቪን ዝና እጅግ ወጣ፣ በዓለም ዙሪያ ሁሉ ገናናና እና ታዋቂ ሆነ፡፡ የኬቪን ፎቶ የፓልትዘርን ሽልማት ስላሸነፈ የሽልማት ስነሥርዓት በተባበሩት መንግሥታት ዋና ጽሕፈት ቤት ተዘጋጀለት፡፡ ከተለያዩ የሙያ ባለሙያዎች፣ የኪነ ጥበብ ሰዎች፣ ከጋዘጠኞችና የፊልም ባለሙያዎች የእንኳን ደስ ያለህ መልእክት ከየአቅጣጫው ጎረፈለት፡፡ የሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ወቅት በታዳሚዎች ፊት  በሙያውም ስኬታማ ሊሆን የቻለው እንዴት እንደሆነ ከጋዘጠኞች ለሚቀርብለት ጥያቄ መልስ እየሰጠና በደቡብ ሱዳን በረሀ ላይ ያቺን ሕጻን እንዴት በካሜራው እንዳገኛት ስለብልሃቱና ስለጥበቡ  እያብራራ ከሁሉም ሰው አድናቆትን  እያኘ ሳለ ከጉባኤ በስተ መጨረሻ በኩል አንድ ሰው አንድ ወሳኝ ጥያቄ አቀረበለት፡፡ ጥያቄውም እንዲህ የሚል ነበረ፡፡ “የልጅቷ መጨረሻ ምን ሆነ?”  በዚህን ጊዜ ኬቪን ደነገጠ፡፡ አንደበቱ ተሳሰረ፡፡ በዓይነ  ሂሊናው ወደ ደቡብ ሱዳን በረሀ ጭልጥ ብሎ ሄደ፡፡ ሰውነቱ ይንቀጠቀጥ ጀመር፡፡ ልጅቷ ምን ሆነች ለሚለው ጥያቄ በሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኘውን ሕዝብ አስተሳሰብ በአንዴ ቀየረው፡፡ ጉባኤተኛው ሕዝብ ኬቪን ለዚህ ጥያቄ ምን መልስ ይሰጥ ይሆን ብሎ በጉጉት እየጠበቁ ሳለ  እርሱ ምንም ሳይመለስ ያን ጥያቄ ያቀረበው ሰው ሌላ ጥያቄ በከፍተኛ  ጩኼት “ ልጅቷን አዳንካት ወይ “ በሚል አስከተለበት፡፡ ኬቪን ልቡ ይመታ ጀመር፡፡ ራሱን በዚያ ሥፍራ ማቆየት ስላልቻለ ከወንበሩ ተነስቶ ወደ ውጭ ወጣ፡፡ በዚያው ወደ አዳራሹ ሳይመለስ ወደ ትውልድ አገሩ ወደ ደቡብ አፍሪካ አቀና፡፡ ቢሆንም ከህልናው ክስ መሸሽ ስላልቻለና ስለተሰቃየ በተወለደ በ33 ዓመቱ አንድ ወረቀት ጽፎ አጠገቡ አስቀመጠና ራሱን ሰቅሎ ሞተ፡፡
ኬቪን ወደ ደቡብ ሱዳን የተላከበት ዋንኛ ምክንያት ለራሱ ዝና እንዲሠራ አልነበረም፣ የሌሎችን ሕይወት ለማዳን እንጂ፡፡ እንደዚያች ላሉ ሕጻናትና ለሌሎች በድርቁ ለተጎዱት ሰዎች የነፍስ አድን ርዳታ እንዲያደርስላቸው ነበር፡፡ ነገር ግን የዚያች ልጅ ሕይወት እየመጣባት ካለው አሞራ ማዳን ሲችል ተልዕኮውን ወደ ጎን በመተው የራሱን ዝና ለማውጣት የሚችለውን ሥራ ብቻ ሥርቶ ልጅቷን በዚያ በረሀ ለአሞራ ተዋት፡፡ ሌሎችን ለመጥቀም የተሰጠውን ተልዕኮ ዘንግቶ ራሱን መጥቀም ፣ በሰዎች ጉዳት እርሱ የመክበርን መንገድ ተከተለ፡፡ በመጨረሻም በጣም ወሳኝ ወቅት ላይ ልጅቷን አዳንካት ወይ የሚል የቀረበለት ጥያቄ ያንን ክብርና ዝናውን ሁሉ አበላሸበት፡፡
ይህ በእግዚአብሔር ቤት ቅዱሳንን ለመጥቀም ከጌታ የአገልግሎትን አደራ ለተቀበልን ሁሉ ማንቂያ ደወል ሊሆን የሚችል ምሳሌያዊ አሳብ ነው፡፡ እኛ የተጠራነውና አገልግሎትን የተቀበልነው ሌሎችን ለመጥቀም ነው፡፡ አገልግሎት የሚለው አሳብ ራሱ ሌላውን ማገዝ፣ መጥቀም፣ መርዳት ወይም ለሌሎች ጥቅም መኖር ማለት ነው፡፡ ይሁን አንጂ በአሁኑ ጊዜ አገልግሎትና አገልጋይ ማለት የተሳሳተ ሥፍራ ላይ እየዋለ ይገኛል፡፡ ከቅርበ ጊዜ ወዲህ በቤተ ክርስቲያን አገልጋይ መሆን ሌሎችን የመጥቀም ጉዳይ መሆኑ ቀርቶ  በሰዎች መጠቀም፣ የተገኘውን ዕድል ሁሉ ለራስ መውሰድ( taking an Advantage to own self ) መሆን እየመሰለ መጣ፡፡ ሰዎችን አዋርደን እኛ ክብር ማግኘት፣ ሰዎችን ዝቅ አድርገናቸው ወይም ጎድተናቸው እኛ ዝናን ማግኘት፣ ድፍረት በባይሆነኝም የሰዎችን ኪስ አራቁተን እኛ ማለትም አገልጋዮች የሆንንው እኛ ብቻ  መበልጸግን ልማድ እያደረግን እንገኛለን፡፡ እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያንና ለአገልጋዮች የሰጠን ተልእኮ ወደ ጎን የተተወ ይመስለኛል፡፡ ልክ የፎቶግራፍ ጋዜጠኛው ኬቪን የተባበሩት መንግሥታት የሰጡት ተልእኮ የተጎዳውን ሕዝብ እንዲያድን ሆኖ ሳለ እርሱ ግን ያንን ሰውን የማዳን ሥራ ወደ ጎን ትቶ የተራቡ ሕጻናትን ለአሞራ ሰጥቶ ለራሱ ክብር ዝና፣ ገንዘብ ሽልማት፣ ታዋቂነትን የሚያተርፍበትን መንገድ እንደተከተለ ሁሉ ዛሬ እኛም አገልግሎታችንን ለሌሎች ጥቅም መስጠት ትተን ለራሳችን ክብርና ዝና የምንኖር እንዳይሆን መጠንቀቅ እንዳለብን የሚያሳስበንን መልእክት ሐዋሪያው ጳውሎስ ከኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ከተናገረው አሳብ እንመለከታለን፡፡
ሐዋሪያው ጳውሎስ በመልእክቱ መግቢያ ላይ እንዲህ ይላል፡፡
ከሚሊጢንም ወደ ኤፌሶን ልኮ የቤተክርስቲያንን ሽማግሌዎች አስጠራቸው፤ ወደ እርሱም በመጡ ጊዜ እንዲህ አላቸው፦ ወደ እስያ ከገባሁበት ከመጀመሪያ ቀን ጀምሮ፥ በትሕትና ሁሉና በእንባ ከአይሁድም ሴራ በደረሰብኝ ፈተና ለጌታ እየተገዛሁ ዘመኑን ሁሉ ከእናንተ ጋር እንዴት እንደ ኖርሁ እናንተው ታውቃላችሁ፤ ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ንስሐንና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች እየመሰከርሁ በጉባኤም በየቤታችሁም አወራሁላችሁና አስተማርኋችሁ እንጂ፥ ከሚጠቅማችሁ ነገር አንዳች ስንኳ አላስቀረሁባችሁም።
ጳውሎስ ሌሎችን የመጥቀሙን አገልግሎት በኤፌሶን ላሉት አማኞች በትክክል አስመስከሯል፡፡ እንዲያውም እርሱ በዚያ ሲያገለግል ሁለት ዓይነት ሰዎች እንደነበሩ ከክፍሉ አጠቃላይ አሳብ እንረዳለን፡፡ አንደኛዎቹ የሐሰት ትምህርት አስተማሪዎች ናቸው፡፡ ጳውሎስ ስለ እነርሱ ሲገልጽ ከተኩላ ጋር ይመስላቸዋል፡፡ ከአውሬዎች ጋር ይመስላቸዋል፡፡ ነጣቂዎች ናቸው ይላቸዋል፡፡ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች ይላቸዋል፡፡ ደቀመዛሙርትን ወደ ኋላ  የሚስቡ፣ ጠማማ ነገርን የሚናገሩ እንደሆኑ ያሳስባል( ቁ 29-30)፡፡ አገልጋዮች ናቸው፣ የወንጌል አገልጋዮች፣ ሰባኪዎች ናቸው ግን በመንጋው ላይ የሚጨክኑ ፣ የአውሬነትና የተኩላነት ልብ ያላቸው፣ የሚነጥቁና የሚያጣምሙ መሆናቸው በጣም የሚያስገርም ነው፡፡ አንድ ሰው ወደ አገልግሎት ሲገባ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ልጥቀም ብሎ ካልሆነ የራሱን የሚመግብ ጨካኝና ነጣቂ ነው የሚሆነው፡፡ ያ ደግሞ መጥፎ መርገም ነው፡፡ ልክ ኬቪን ልጅቷ አዳንካት ወይ የሚል ጥያቄ ሲቀርብለት ግራ እንደተጋባና ራሱን ከሥፍራው እንዳገለለ ሁሉ አገልጋዮች አንድ ቀን መጠየቃችን አይቀርም፡፡
ሁለተኛው ጳውሎስ ራሱ ሲሆን የኖረው ለአማኞች ጥቅም ሲል እንደሆነ ይናገራል፡፡ በእስያ  ለሦስት ዓመታት ኖሯል፡፡ በዚያን ጊዜ ጢራኖስ በሚባል የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ቤት እያስተማረ ለሁለት ዓመታት መኖሩን በሐዋሪያት ሥራ ምዕራፍ 20 ላይ እናገኛለን፡፡ ከዚያም በላይ ዘመናትን ኖሮ ሊሆን ይችላል ግን በኖረባቸው ጊዜያቶች ሁሉ ለቅዱሳን የሚጠቅመውን አድርጓል፡፡ ከሽማግሌዎች ጋር ሆኖ የሦስት ዓመት አገልግሎቱን ሲገግምና ሲከልስ የእግዚአብሔርን ሰዎች ከሚጠቅማቸው ነገር አንዱንም እንዳላስቀረ በልበ ሙሉነት ይናገራል፡፡
በዚህ ክፍል ሐዋሪያው ርግጠኛ ሆኖ የሚናገረው ከቤተ ክርሰቲያን ሕዝብ ከሚጠቅማቸው ነገር አንድ እንኳ እንዳላስቀረባቸው ነው፡፡ የሚያደርጋቸውን ሁሉ ነገሮች ያደረገው ለአማኖቹ እንድጠቅማቸው ብሎ ነው፡፡ የእውነተኛ አገልጋይነት ሕይወትም እኮ እ ሌላውን በመጥቀም ነው፡፡ ወንጌላችን ራሱ ሌሎችን መጥቀም ነው፡፡ ጳውሎስ በሌላም ሥፍራ ሰዎችን ለመጥቀም ራሱን እንደሰጠ ሲናር እንዲህ አለ፡፡
ከሰው ሁሉ አርነት የወጣሁ ስሆን የሚበልጡትን እንድጠቅም እንደ ባሪያ ራሴን ለሁሉ አስገዛለሁ። አይሁድንእጠቅም ዘንድ ከአይሁድ ጋር እንደ አይሁዳዊ ሆንሁ፤ ከሕግ በታች ያሉትን እጠቅም ዘንድ፥ እኔ ራሴ ከሕግ በታች ሳልሆን፥ ከሕግ በታች ላሉት ከሕግ በታች እንዳለሁ ሆንሁ፤ ሕግ የሌላቸውን እጠቅም ዘንድ፥ ያለ እግዚአብሔር ህግ ሳልኖር ነገር ግን በክርስቶስ ሕግ በታች ሳለሁ፥ ሕግ ለሌላቸው ሕግ እንደ ሌለኝ ሆንሁ፤ ደካሞችን እጠቅም ዘንድ ለደካሞች እንደ ደካማ ሆንሁ፤ በሁሉ መንገድ አንዳንዶችን አድን ዘንድ፥ ከሁሉ ጋር በሁሉ ነገር እንደ እነርሱ ሆንሁ(1 ቆሮ 9፡19-22)።
ጳውሎስ ለተለያዩ ሰዎች ወንጌልን ሰብኮ እነርሱ ደህነነትን የሚያገኙበት መንገድ ሲናገር እነርሱን መጥቀም ይለዋል፡፡ በሌላም ሥፍራ ለፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን አማኞች ስናገር በምድር መኖሩ ራሱ ለራሱ ጥቅም ሳይሆን ለአማኞች ጥቅም እንደሆነ ይናገራል፡፡ ለእርሱ ወደ ክርስቶስ መሄድ እጅግ የተሻለና የበለጠ ነገር እንደሆነ ቢያምንም በሥጋ ከእነርሱ ጋር መኖር ግን ከእርሱ ይልቅ ለእነርሱ/ ለአማኞቹ/ ጥቅም እንደሆነ ያስረዳል፡፡ እንዲህም ሲል፡
ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ፥ ሞትም ጥቅም ነውና። ነገር ግን በስጋ መኖር ለእኔ የሥራ ፍሬ ቢሆን፥ ምን እንድመርጥ ኣላስታውቅም። በእነዚህም በሁለቱ እጨነቃለሁ፤ ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፥ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና፤ ነገር ግን በሥጋ መኖሬ ስለ እናንተ እጅግ የሚያስፈልግ ነው( ፊልጵስዩስ 1፡19-23)።
እኛስ ዛሬ ራሳችንን ስንፈትሽ  እግዚአብሔር በሰጠን ዘመን ባገለገልንባቸው ሥፍራዎች ሁሉ የእግዚአብሔርን ሕዝብ የሚጠቅም አገልግሎት እንደሰጠን እርግጠኞች ነንን? ለእግዚአብሔር ሕዝብ የምንጠቅም አገልጋዮች እንድንሆን እግዚአብሔር ይፈልጋል፡፡ በእውነት በዚህ ዘመን እግዚአብሔር ይርዳን፡፡ ሐዋሪያው ጳውሎስ ለኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ካስተማረው ትምህርት በአገልገሎታችን እንዴት ቅዱሳንን መጥቀም እንደምንችል አራት መሠረታዊ ነጥቦችን እንመለከታለን፡፡ በአገልግሎታችን ሌሎችን መጥቀም የምንችለው እንዴት ነው?
1.    ለአገልጋይነት የሚገባ ባሕሪይ /An aproprate character/ ሲኖረን ነው፡፡

ወደ እስያ ከገባሁበት ከመጀመሪያ ቀን ጀምሮ፥ በትሕትና ሁሉና በእንባ ከአይሁድም ሴራ በደረሰብኝ ፈተና ለጌታ እየተገዛሁ ዘመኑን ሁሉ ከእናንተ ጋር እንዴት እንደ ኖርሁ እናንተው ታውቃላችሁ፤ ጳውሎስ በዚህ ሥፍራ ወደ ሌሎች አሳቦች ሁሉ ከመግባቱ በፊት ስለ ራሱ የአገልጋይነት ባሕሪይ አጠንክሮ ይናገራል፡፡ በአማኞች መካከል በተመላለሰባቸው ጊዜያቶች ሁሉ 3 ዋና ዋና የአገልጋይ ባሕሪያትን ማሳየቱን በልበ ሙሉነት ይገልጻል፡፡ 1. ትሁት ነው፡፡ 2. የእምባ ሰው ነው፡፡ 3. ለጌታ የተገዛ ሰው ነው፡፡ ትህትና የሌለው ሰው በእግዚአብሔር አገልግሎት ቢሰማራም ቅዱሳንን ሊጠቅም አይችልም፡፡ እንዲያውም የእርሱ አገልጋይነት ለቤተ ክርስቲያን ሸክምና ፈተና ነው፡፡ ትህትና የትዕቢት ተቃራኒ ሲሆን በምድር ላይ እጅግ አስቸጋሪ ኃጢአት ቢኖር ትዕቢት ነው፡፡ ትዕቢተኛ ሰው መንፈሳዊ ፍሬ ሊያፈራ አይችልም፡፡ ቅዱሳንን ይጎዳል፣ አገልግሎትንም ያበላሻል፡፡  ትሁታን ባሉበት ግን ፍሬ አለ፣ ነጻነት አለ፣ ሰላምም አለ፣ ሁም በደስታ ጌታን ያልካል ያገለግላልም፡፡ ጳውሎስ በዚህ ሕይወቱ የተመላለሰ አገልጋይ ነበር፡፡ እርሱ ትሁት ብቻ ሳይሆን የእምባ ሰው ነው፡፡ ስለ አማኞች በእግዚአብሕር ፊት የሚያነባ ሰው ነው፡፡ አማኞችን ሲያስተምራቸውና ሲገስጻቸውም ሁሉ በእምባ ነበር (ስለዚህ ሦስት ዓመት ሌሊትና ቀን በእንባ እያንዳንዳችሁን ከመገሠጽ እንዳላቋረጥሁ እያሰባችሁ ትጉ ቁ 31)፡፡ የምናገለግለው አገልግሎት ከእውቀት ፣ ከትምህርት፣ ከልምድ ሁሉ በላይ እምባን የሚጠይቅ ነው፡፡ ከዚህም ጋር ጨምሮ በዘመኑ ሁሉ ለጌታ የተገዛ ሰው መሆን ይገባል፡፡ ጳውሎስ ከአይሁዶች ሴራና ዛቻ ቢደርስበትም እንኳ በሕይወቱ አንድም ቀን የትዕቢት ነገር አልታየበትም፡፡ይልቁንም ከእምባ ጋር ለጌታ እየተገዛ ዘመመኑን ሊኖር የቻለ ሰው ነው፡፡ የጌታ ባሪያ ጳውሎስ እነዚህ ሦስት ዋና ዋና መልካም ባሕሪያት የታየበት ድንቅ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነው፡፡
በዛሬዋ ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ ግምት የሚሰጠው አንድ ሰው የአገልግሎት ስጦታ መኖሩን ብቻ ነው፡፡ ሰባኪ፣ ዘማሪ፣ የፈውስ አገልጋይ፣ ተአምራት የሚያደርግ መሆኑን ብቻ ነው፡፡ እኛም አገልጋዮች የሆንነው የምናተኩረው በዚያ ላይ ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የሚባርከን በእኛ አገልግሎትም ሌሎችን የሚባርካቸው ባለን መንፈሳዊ ሕይወት ለውጥና ባሕሪይ(Charactor) መሰረት ነው፡፡ ይህ በጣም መሠረታዊ ነገር ነው፡፡  ጳውሎስ በምዕመናን መካካል ሲመላለስ እነዚህን ቁልፍ ባሕሪያትና ያሳየው ለአንድ ጊዜ ቆይታ ብቻ ወይም የሆነ ነገር ሲፈልግ ፣ ወይም አንድ ነገር እንዲሆንለት ሰዎችን ሊያማልል ያደረገው የግብዝነት ነገር አልነበረም፡፡ ነገር ግን የሁል ጊዜ የሕይወቱ ተሞክሮ እንደሆነ ሲገልጽ ወደ እስያ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ እነዚህ ባሕሪያት የታዩበት እንደነበረ ይናገራል፡፡ ስለዚህ በአጥቢያ ቤተ ክርስቲያንም ሆነ በሌሎች የአገልግሎት  ክፍሎች ተሰማርተን ስናገለገል በእውነት ሌሎችን እንጥቀማቸው ካልን ወደ መሠረቱ መመለስ ይኖርባናል፡፡ ያውም ከተሰጡን የጸጋ ሥጦታዎች በላይ በእግዚአብሔርና በሕዝቡፊት ያለን የሕይወት ለውጥ ምን እንደምመስል መገምገምና መረዳት ያስፈልገናል፡፡

2.   አገልግሎታችን ሥልታዊነት Strategy ያለው ሲሆን ነው፡፡

 የምንሰጠውን አገልግሎት የትና እንዴት እንደምንሰጥ በትክክል ማወቅ ቅዱሳንን ለመርዳት የሚያግዘን አንዱ መንገድ ነው፡፡ ሐዋሪያው የአገልግሎቱ ሽፋን( a ministerial scope) ለማን፣ ለምንና   እንደሆና ከየት እስከ የትም መሆን እንዳለበት የተረዳ ሰው መሆኑን በዚህ ክፍል ያሳየናል፡፡ (ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ንስሐንና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች እየመሰከርሁ በጉባኤም በየቤታችሁም አወራሁላችሁና አስተማርኋችሁ፣ቁ.20-21)፡፡ ጳውሎስ በዚህ አሳቡ ማንን እንደሚጠቅም ያውቅ ነበር፣ የት እንደሚጠቅማቸውም ያውቅ ነበር፡፡ በእርሱ አገልግሎት የሚጠቀሙት ሰዎች ሁሉ ማለትም አይሁድም አሕዛብም ናቸው፡፡ በዚያ ጊዜ የዓለም ሕዝብ አይሁድና አሕዛብ ተብሎ በሁለት ጎራዎች የተከፈሉ ቢሆንም የጳውሎስ አገልግሎት ግን  ለሁሉም ነበረ፡፡  እርሱ ራሱ ሁሉንም የሚጠቅም አገልጋይ ነበረ፡፡ ሁሉንም ማገልገሉና መጥቀሙ የሕይወቱ መመሪያ ስለነበረ ለፊልጵስዪስ ሰዎች ሲጽፍ ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ወይም በከንቱ ውዳሴ ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ፥ ነገር ግን እያንዳንዱ ባልንጀራው ከራሱ ይልቅ እንዲሻል በትሕትና ይቍጠር፤እያንዳንዱ ለራሱ የሚጠቅመውን አይመልከት፥ ለባልንጀራው ደግሞ እንጂ(ፊልጵ 2፡4) በማለት ጠንካራ መመሪያ ሰጥቶ አለፈ፡፡  የጳውሎስ ሥረ- መሠረቱ አይሁዳዊ ቢሆንም እርሱ ግን አህዛብ የሆኑ ግሪኮችንም ይጠቅማቸው ነበር፡፡ ደካሞችን ይጠቅማቸው ነበር፡፡ የተጠቁትን፣ የተጣሉትን፣ የተገለሉትን፣ አምላክ የላቸውም የተባሉትን፣ አገርም የሌላቸው የተባሉትን፣ ያልተገረዙ የተባሉትን ሁሉ ለመጥቀም ያገለግል ነበረ፡፡ በጳውሎስ አገልግሎት ውስጥ ልዩነት የሚባል ነገር ስላልነበረ እርሱ ለሁሉም የሚጠቅም አገልጋይ ሆነ፡፡
ጳውሎስ  የአገልግሎቱን ተደራሲያን ብቻ ሳይሆን የት ማገልገል እንዳለበትም የተረዳ ሰው ነበረ፡፡  አገልግሎቱ ጉባኤም በየቤታቸውም  ሁሉ ነበር፡፡ የሐሰት አስተማሪዎች ትልቁ ትኩረታቸው ቤት ለቤት እየዞሩ የቅዱሳንን ቤት መብላት፣ በእምነታቸው ያልበረቱትና አንዳንድ ቅምጥል ሰዎችን ማሳት ነው፡፡ በኢየሱስም ጊዜ የፈሪሳውያን ትልቅ ስህተት ከነበረው አንዱ ቤት ለቤት እየዞሩ የመበለቶችን ቤት መብላት ነው፡፡ በአንጻሩም ደግሞ እውነተኞች አገልጋዮች እውነተኛና ጤናማ የሆነ አገልግሎት ይዘው ወደ የቤቱ ሄደዋል፡፡ ኢየሱስም ወደ የቤቱ ሁሉ ሂዱ ስትሄዱም ሰላም ለዚህ ቤት ይሁን በሉ፣ ያቀረቡላችሁንም ብሉ ያለው አገልጋዮች ወንጌልን ለመስበክም ሆነ አማኞችን በእምነታቸው ለማጽናት የቤት ቤት አገልግሎት በጣም ተፈላጊ ስለነበረ ነው፡፡ አሁንም ይህ ሊተኮርበት ይገባል፡፡ ዛሬ በኢትዮጵያ በአገልጋይነት ስም  ብዙ ሰዎች ቤት ለቤት እየተዘዋወሩ የቅዱሳንን እምነት እየሸረሸሩ እንደሆነ በግልጽ የሚታይነው፡፡ አንዳንዶች ደግሞ ቤት ለቤት አገልግሎትን እያስቀሩ ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ፣ በቤተ ክርስቲያን የሚደረገው የፈውስ አገልሎት መልካም ቢሆንም አስተምሮአዊ መርሆ ግን ሙሉ በሙሉ እየተረሳ ነው፡፡ በያዕብ 1፡16 ላይ ማንም የታመመ ቢኖር የቤተ ክርስቲያንን ሽማግሌዎች ወደ ራሱ ይጥራ እነርሱም በጌታ ስም ዘይት ቀብተው ይጸልዩ ይላል፡፡ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮን ለመጣሷ ይህ ምሳሌ ነው፡፡ ሰዎች በአደባባይ ግሩም ክርስቲያኖች ቢመስሉም እቤታቸው የሚኖሩበት ሕይወት መታየት ይኖርበታል፡፡ በቤታቸው መከራን የሚቀበሉ፣ ሕይወት የተበላሸባቸው፣ የቅዱሳንን ድጋፍና ምክር የሚፈልጉ ሲኖሩ በጉባኤ አገልግሎት ብቻ መፍትሔ ልናስገኝላቸውና ልንጠቅማቸው አንችልም፡፡ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ወደ እነዚያ ሰዎች በማቅናት ባሉበት ሁኔታ ሲገለግሉአቸው ይገባል፡፡ በተለይም የቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ከጌታ የተሰጣቸውን መንፈሳዊ ሥልጣን ከሚገልጹባቸው መንገዶች አንዱ ወደታመሙ ሰዎች ቤት በመሄድ ቃሉን ማስተማር ፣ አስፈላጊውን ምክር በመስጠት ፣በጌታ ስም ዘይት ቀብተው በመፀለይ ድዊውን የመፈወስአገልግሎት ነው፡፡ በቤተክርስቲያን ጉባኤ ላይ የሚደረገው የፈውስ አገልግሎት ለወንጌል ሥርጭት ጠቃሚ ነው፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔር ቃል በግልጽ የሚያስተምረን ግን ማንም የታመመ ቢኖር የቤተ ክርስያንን ሽማግሌዎች ወደ ቤቱ እንዲጠራና አገልግሎቱን እንዲካፈል ነው፡፡ የቤት ለቤት አገልግሎት ቃሉን ለማስተማር፣ መንፈሳዊ ምክርንም ለመስጠት ፣ የቅዱሳንን የእርስ በርስ ህብረት ለማጠናከርና የስተት ትምህርቶች ለመከላከል የሚረዳበመሆኑ በአደባባይ ያለውን አገልግሎት ከማካሄድ ጎን ይህኛውንም ማጠናከር ተገቢ ነው፡፡ ከመድረክ አገልግሎት ይልቅ ቤት ለቤት ተዘዋውሮ ማገልገል በጣም አድካሚ ነው፣ታዋቂም አያስብልም፡፡ ስለዚህ ብዙዎች አይሞክሩትም፣ አይፈልጉትምም፡፡ በተለይም መድረክ ተኮር መጋቢዎች መዕመናን ወደ እነርሱ እንዲመጡ እንጂ ወደ መዕመናን ወርደው በቤታቸው ማገልገል አያስቡትም፡፡ ቅዱሳንን በመንፈሳዊ ሕይወታቸው የሚጠቅም የእረኝነት  ልብ ያላቸው መጋቢያን ግን የኢየሱስንና የጳውሎስን ፈለግ ተከትለው የሚያለግሉአቸውን ምዕመናን በቤትም በጉባኤም ያለግሉአቸዋል፡፡
ከጳውሎስ አገልግሎትየምንማረውሌላው ቁም ነገር የሚያገለግላቸውን ሰዎችና ቦታን ለይቶ ማወቅ ብቻ ሳይሆን እንዴት እንደሚያገለግልም ያውቅ ነበር፡፡ እርሱ በበጉባኤም ሆነ  በቤትም ያደረገው ምንድነው; ሦስቱ የአገልግሎቱ ስልቶች ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ እነርሱም ማስተማር፣ በስበክ( እየመሰከርኩ አወራሁላችሁላችሁ ይላል እርሱ)ቁ 20፣ መገሰጽ( ቁ.31) ናቸው፡፡ ሐዋሪያት ፣ ነቢያት፣ አስተማሪዎች፣ የወንጌል ሰባኪዎችና እረኞች ሽማግሌዎች አሁን በእጃቸው የለውን ሕዝብ ቤቤቱ እየገቡ ቢያስተምሩ፣ ቢሰብኩ፣ በድካማሙም አባታዊና መጋቢያዊ ግሳጼ እየሰጡ ማገልገል ከቻሉ በእውነት ጠቅመዋል ማለት ነው፡፡ በዛሬው ጊዜ ወደ ሰዎች ቤት የሚሄዱ አገልጋዮች አሉ፡፡ መነሳት ያለበት ጥያቄ ግን የሚሄዱት እነማን ናቸው፣ ማንስ ጋ ይሄዳሉ፣ ሄደውስ ምን ያድርጋሉ የሚለው ነው፡፡ ይህ በትክክል መለስ ማግኘት ይኖርበታል፡፡ ወደ ሰዎች ቤት መሄድ ያለባት ቤተክርስቲያን ናት፣ ወይም ደግሞ ቤተክርስቲያን የወከለቻቸው አገልጋዮች በዓላማና በመርሀ ግብር ፣ ያለምንም ልዩነት ወደ እያንዳዱ ምዕመን በመግባት ሕይወታቸውን ማደስ ማስተማር፣ መምከር፣መገሰጽ ይኖርቸዋል፡፡ ካልሆነ ግን ሀሰተኞች ተኩላዎች መንጋውን ይበሉባቸዋል፡፡    
         

3.   አገልግሎታችን ቁም ነገርና ይዘት /substance and content/ ያለው ሲሆን ነው፡፡

ሰዎችን በአገልግሎታችን የምንጠቅመው በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዲጠናከሩ የሚያደርገውን ነገር ሁሉ በመስጠት ነው ፡፡  ጳውሎስ እንዲህ ይላል፡፡ ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ንስሐንና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች እየመሰከርሁ በጉባኤም በየቤታችሁም አወራሁላችሁና አስተማርኋችሁ እንጂ፥ ከሚጠቅማችሁ ነገር አንዳች ስንኳ አላስቀረሁባችሁም(20-21)። አሁንም፥ እነሆ፥ እኔ የእግዚአብሔርን መንግሥት እየሰበክሁ በመካከላችሁ የዞርሁ ሁላችሁ ከእንግዲህ ወዲህ ፊቴን እንዳትዩ አውቃለሁ( ቁ.25)። የእግዚአብሔርን ምክር ሁሉ ነግሬአችኋለሁና፥ ምንም አላስቀረሁባችሁም(ቁ 27)። ጳውሎስ እንደሚነግረን እርሱ ወደየቤቱም በየጉባኤ ምን ያደርግ ነበር  የሚለው ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ወደ ሰዎች ቤት መሄድ ወይም በጉባኤ ፊት መቆም ብቻ ሳይሆን ምን አደረጉ የሚለው ነው መታየት ያለበት፡፡ ጳውሎስ አስተማረ፣አወራላቸው( ሰበከላቸው) ፣ በቁጥር 31 ላይ እንደምንመለከተው ያለማቋረጥ ሌሊትና ቀን ያውም በእምባ ሆኖ ይገስጻቸው ነበር፡፡ ሲሰብክና ሲያስተምርም መንፈሳዊ ቁም ነገር ያለበትን ስብከትና ትምህርት ያስተላልፍ እንደ ነበርከፍ ብሎ አይተናል፡፡ የመልእክቱ ይዘትስ ምን እንደነበር መረዳት በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ሰዎች ወደ ሰዎች ቤት መሄዳቸው ወይም ለአገልግሎትመድረክ ላይ መውጣታችን ብቻ ሳይሆን የምንለው ምንድነው የሚለው ደግሞ ሌላው ወሳኝ አሳብ ነው፡፡ ባለፈው ሁለት ዓመት አካባቢ ወደ ጌታ የሰበበሱቡት  ተወዳጁ የቅዱሳት መጻሕፍት አቀንቃኝ፣ አስተማሪና ሰባኪ የነበሩ ዶር ጆን ስቶት በአንድ ስብከታቸው ላይ እንዲህ ብለው ነበር፡፡ “ኢየሱስ ካልተዘመረ ዘማሪው መዝሙሩን አልዘመረውም፣ ኢየሱስ ካልተሰበከ ሰባኪው ስብከቱን አልሰባከውም፣የኢየሱስ ሥልጣን ካልታከለበት ጸሎቱም አልተጸለየም”፡፡ ይህ የቀድሞ ሐዋሪያት ያደረጉት  አባቶቻችንም የተከተሉት ሲሆን እኛም ጠንክረን ሊናደርገው የሚገባ ተግባር ነው፡፡ ሓዋሪያው ጳውሎስ መልእክቱም ለሰዎች ያስተላፈው ስለ ንስሐና በኢየሱስ ክርስቶስ ስለማመን(ቁ 20-21)፣ እና  ስለ እግዚአብሔር መንግሥት(ቁ.25) ይስብክና ያስተምር ነበር፡፡ እንደዚህ ዓነቱን አገልግሎት ስንሰጥ ሰዎች ይጠቀማሉ፣ይጠነክራሉ፡፡ ጳውሎስ ለራሱ ጥቅምና ዝና የሆነውን ስብከት አይሰብከም፣ እንደዚያ ያለውንም ትምህርት አያስተምርም፡፡ ራሱን አያወድስም ይልቁንስ ኢየሱስን ነው ያሳየው፡፡ ያ አገልግሎቱ እስከ ዛሬ ድረስ ወደ እኛ ዘለቀ፡፡ ዛሬ በየመድረኩ የሚሰበኩትና የሚተላለፉት ስብከቶችና ትምህርቶች ምን ይዘት አላቸው የሚለው አሳሳቢ እየሆነ በመጣበት ዘመን ላይ ነን፡፡ ሰውን ለማስደሰት ተብሎ በሚደረጉ ውድድሮች ከቁም ነገሩ ይልቅ ገለባው እየበዛ ነው፡፡ ከሰማያዊው ትምህርት ይልቅ ምድራዊ ብልጽግና ፣ ስኬት፣ የመሳሰሉት ይተኮርበታል፡፡ ካልሆነም ደግሞ የግለሰቦች ማንነት የኢየሱስን አዳኝነትና ክብር እስክሸፍን ድረስ አየተወራና እየተነገረ ነው፡፡ ይህንን ትምህርት እያዘጋጀሁ ሳለ ወደ አገር ቤት ሲደውልና ስለ አንዳንድ መንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ሲጠይቅ የአንድ ዕድሜ ጠገብ  ስለሆኑ አባት ይነግሩኝ ነበር፡፡ እኒህ ሰው አቶ ባንጫ በመባል የሚታወቁ ሲሆን ዶር ላምቤ ወደ ወላይታ ገብተው ወንጌል ሲሰብኩ የዶክተሩን በቅሎ በመጎተት ከረዱአቸው ወጣቶች አንዱ ሲሆኑ በወላይታ ውስጥ ወንጌልን በማሰራጭትና ቤተ ክርስቲያንንም በመምራት ትልቅ ዋጋ የከፈሉ ሰው ናቸው፡፡ እኒህ ሰው ጓደኞቻቸው ሁሉ ወደ ጌታ ተሰብስበው እርሳቸው ብቻ በሕይወት ያሉ ናቸው፡፡ ሰዎች ስለእሳቸው አገልግሎትና ታሪክ ለመጻፍ ፈልገው ሲጠይቋቸው የመለሱላቸው መልስ የሚገርም ነው፡፡ እኔ በሕይወት እያሁ የእኔን ታሪክ አትጻፉ፣ መጻፍ ከፈለጋችሁም የኢየሱስን ሥራና ታሪክ ጻፉ እንጂ የእኔን እንድትጽፉ አልፈልግም በማለት ነው፡፡ ይህ አስገርሞኛል፡፡ ሰው ራሱን ለማሳየት፣ ዝናውን ለማግኘት፣ ክብርንም ለማግኘት ብዙ ነገሮችን በሚያደርግበት ወቅት የእኔ ታሪክ አይጻፍም ማለት፣ ያውም የተሠራ የሚታይ ታሪክ እያለ አለመፍቀድ እንዴት ያለ አስደናቂ ጉዳይ ነው፡፡  በአገልግሎታችን ሰዎችን መጥቀም  የምንችለው መንፈሳዊ ቁም ነገርና ይዘት ያለበትን መልእክት ፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ የሆነውን እውነት፣ ሥነ-መለኮታዊና አስተምህሮአዊ የሆነውን በታማኝነት ያቀረብንላቸው እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ያስተማርናቸው፣ የሰበክናቸው፣ እና በትጋት የገሠጽናቸው እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ያለዚያ እያሳሳትናቸውና እየበደልናቸው መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ እግዚአብሔር ግን ቅዱሳንን እንድንጠቅም ስለሚፈልግ ከሰጠን መንገድ አንዱ ቁም ነገርን መናር፣ ቁም ነገርን ማስተማር፣ ቁምነገርን ማድረግም ነው፡፡   

4.   በአገልግሎታችን የቁርጠኝነት ሕይወት/ Determination/  ሲኖረን ነው፡፡

አሁንም፥ እነሆ፥ እኔ በመንፈስ ታስሬ ወደ ኢየሩሳሌም እሄዳለሁ፥ በዚያም የሚያገኘኝ ምን እንደ ሆነ አላውቅም፤ ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ እስራትና መከራ ይቆይሃል ብሎ በየከተማው ሁሉ ይመሰክርልኛል። ነገር ግን ሩጫዬንና ከጌታ ከኢየሱስ የተቀበልሁትን አገልግሎት እርሱም የእግዚአብሔርን ጸጋ ወንጌልን መመስከር እፈጽም ዘንድ ነፍሴን በእኔ ዘንድ እንደማትከብር እንደ ከንቱ ነገር እቆጥራለሁ (ቁ.22-24) ።


አሁን ጳውሎስ ወደ ኢየሩሳሌም እየሄደ ነው፡፡ በዚያ ምን እንደሚገጥመው አያውቅም ግን መከራ እንደሚደርስበት ከመንፈስ ቅዱስ ተረድቷል፡፡ ቢሆንም ግን መከራ ተቀብሎም ቢሆን በኢየሩሳሌም ያሉ ቅዱሳንን በወንጌል ለመጥቀም ቆረጠ፡፡ እንዲሁም ሰዎች መከራ መኖሩን ተረድተው ወደ ኢየሩሳሌም እንዳይሄድ አጥብቀው ቢለምኑትም በኢየሩሳሌም ለመሞትም እንኳ ዝግጁ መሆኑን በቁርጠኝነት ተናገረ፡፡  ሰዎች ከሚናገሩት ይልቅ ጳውሎስን ይገዛው የነበረው እርሱ የተቀበለው የእግዚአብሔር መንፈስ ነው፡፡ ወደ ወንጌል አገልግሎት የሚሄደው በእግዚአብሔር መንፈስ ቁጥጥር ሥር ሆኖ ነው፡፡ እርሱን የሚመራው የእግዚአብሔር መንፈስ ስለሆነ ምንም እንኳ  ወደ ኢየሩሳሌም ሲደርስ የሚጠብቀው መከራና ስደት ቢሆንም በእግዚአብሔር መንፈስ ተሥሮ ወደዚያ ሥፍራ እንደሚጓዝ በግልጽ ተናራቸው፡፡  ጳውሎስ በኢየሩሳሌም የሚጠብቀው መከራ ወንጌልን በመስበኩ ምክንያት ከአይሁዶች የሚደርስት ስደት ሊሆን ይችላል፡፡ ቢሆንም ግን እርሱ ወደ ኢየሩሳሌም የሚሄደው በመንፈስ ታሥሮ መሆኑን ግልጽ አደረገላቸው፡፡ በወንጌል አገልገሎት ውስጥ  ይህን የሚመስል ዋጋ መክፈል የሚስፈልገው ለምንድነው? መስዋዕትነት  ከፍሎ ማገለገል የሚያስፈልግበት ምክንያትማ የተሰጠው አገልግሎት  ስለነበረው ነው፡፡ እንዲሮጥ የተሰጠው ሩጫ ስላለ ነው፡፡ከኢየሱስ የተቀበለው አገልግሎት መፈጸም ስላለበት ነው፡፡ ይህን ሩጫ ማጠናቀቅና አገልግሎትን መፈጸም ሲባል መከራና ስደት መኖሩ በግልጽ እየተነገረም ቢሆን ወደ አገልሎቱ እንዲንገሰግሥ ያስገድደናል፡፡ ነፍሴ በእኔ ዘንድ እንደማትከብር እንደ ከንቱ ነገር እቆጣራታለሁ ያለው ለዚህ ነው፡፡ ይህ ሐዋሪያው ጳውሎስ ለወንጌል አገልግሎትና በወንጌል ሌሎችን ለመጥቀም ምን ያልህ እንደተሰጠ የሚመለክት ነው፡፡ እርሱ ገና በኤፌሶን ከተማ ወንጌልን መስበክ በጀመረበት ወቅት መከራና ስዴት አንዲሁም በሚሰብከው ወንጌል እውነት ምክንያት በከተማው ውስጥ ሁከት ከተነሳት ጊዜ ጀምሮ ወንጌልን በመከራ መስበክን ተለማምዷል፡፡በገና በደማስቆመንገድ ሲጠራ በጌታ ስም መከራን የሚቀበል አገልጋይ እን ደሚሆን በጌታ የተነገረለት ሰው ስለነበርና ያንን ሁሉ አልፌ እዚያጋ ስለደረሰ በኢየሩሳሌም ሰለሚጠብቀው  መከራ የሚፈራበት ምክንያት አልነበረውም፡፡   ለእግዚአብሔር አገልሎት ታማኝ የሆኑ አገልጋዮች በመከራም ውስጥ ሆነው ጌታን ያገለግሉታል፡፡ እኛ ሁላችንም እኮ ከእኛ በፊት የሄዱ ሰዎች የከፈሉበት ዋጋ ውጤቶች ነን፡፡ የቀደሙት አባቶቻችን እኛ ከዳንን ይበቃናል ብለው አልተቀመጡም፡፡ ወንጌልን በብዙ መስዋዕትነት ለእኛ ሰበኩልን፡፡ እግዚአብሔር በመስዋዕትነት የምናለግለውን አገልግሎት እጅግ በጣም አድርጎ ያከብረዋል፡፡ ቁርጠኝነት ካላቸው አገልጋዮች ጋር እግዚአብሔር ይቆማል፡፡ ስለዚህ  ከጌታየተቀበልነውን አገልግሎትና ሩጫ በመፈጸም የእግዚአብሔርን መንጋ ለመጥቀም እንድንችል እግዚአብሔር ይርዳን፡፡  

Thursday, February 9, 2017

ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካ ባትሳተፍስ?

ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካ ባትሳተፍስ?
ከመጋቢ ሳሙኤል ሾንጋ

 የፖለቲካ ጉዳይ ከነባሕሪዩ አስቸጋሪ፣ ለመተንተን አደጋች፣  በተለይም እንደ እኔ ላለ ፖለቲካ ላልቀመሰ ሰው ደግሞ የባሰ አደናጋሪ ነው፡፡ ለነገሩ ምሁራኑም ቢሆን ፖለቲካን እንደ ቀላል አያዩትም፡፡ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካ መሳተፍ የለባትም እያልን ከጎኑ ደግሞ ባለመሳተፏ የሚመጣባት  የጎንዮሽ ጉዳት ሳያስጨንቀን አልቀረም፡፡ በፖለቲካ ካለመሳተፍና ከመሳተፍ መቼም ቢሆን ከሁለት አንዱ የተሻለ መሆኑ ግድ ነው፡፡ ለማንኛውም ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው ባትሳተፍ የምትቸገርባቸው አቅጣጫዎች እነሆ
1.          አገዛዙ ዓለማዊ መሆን፡
ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው ባትሳተፍ የፖለቲካውና የመንግሥት አመራር ሙሉ በሙሉ በዓለማውያን እጅ ይገባል፡፡ የመንግሥትን አመራር እግዚአብሔርን የማያውቁ፣ ፈርሃ እግዚአብሔር የሌላቸው ሰዎች ከተቆጣጠሩት  በምድር ላይ የከፋ አመጽ ይከተላል፡፡ ቤተ ክርስቲያንና አማኞች ከለሉበት የአገር ፓርላማ ያለአንዳች ተከላካይ ቢያንስ የልዩነት አሳብ የሚያቀርብ እንኳ ሳይኖር  በሙሉ ኃይሉና አቅሙ ለቤተክርስቲያን እንቅስቃሴ እንቅፋት የሚሆን ውሳኔ ሊያስተላልፍ ይችላል፡፡ አማኞችም እንደ አናሳ ቡድን (Minority group) ስለሚታሰቡ አስፍተው መራመድ ፣ በአደባባይ መናገር፣ ሁሉ እየቀረ ይመጣል ማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ፓርላማ በርከት ያሉ ጠንካራ አማኞች ስላልነበሩና ቤተክርስቲያን በዚያ ቦታ በብቃት መሳተፍ ባለመቻሏ የወታደራዊ መንግሥት ሙሉ በሙሉ ስለተቆጣጠረው ፓርላማው የሚያወጣው አዋጅና መመሪያ ጸረ እግዚአብሔር፣ ፀረ -ክርስትና ሆኖ ለ17 ዓመት ዘለቀ፡፡  በዚያን ወቅት ጥቂት ክርስቲያኖች መንቀሳቀሳ ሲጀምሩ ብዙም ሳይራመዱ ወጥመድ ይበዛባቸው ጀመረ፡፡ በቤተ ክርስቲያንም አጠቃላይ እንቅቃሴና እምነት ላይ አደጋዎች እየተበራከቱ መጡ፡፡ ያነ ግን አማኞች( ፍርሃ እግዚአብሔርና የክርስትና ልብ ያላቸውን ማለቴ ነው) በርከት ብለው በፓርላማውና በመንግስት ምክር ቤት ተገኝተው ቢሆን ኖሮ ያ ሁሉ ጥፋት አቅም ባላገኘና በእዚያ የነበሩ ጥቂት ወገኖችም አፍ ባላጡ ነበር፡፡ የአሥራ ሰባት ዓመቱ የኮሚዩኑዝም ሥርዓት በአገራችን አደባባዮች እግዚአብሔርንም አምላኪዎቹንም ባለ በሌለ ኃይሉ ይዳሰብ የነበረው  ፖለቲካው ሙሉ በሙሉ  በከሃዲዎች እጅ ስለገባ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ የአሁኑዋም ቤተ ክርስቲያን ከዚያ ልምድ በመውሰድ በተለይም ከአሁን በኋላ በሚመጡ መንግሥታትና በዘመናቸው የባለፈው ዓይነት ቀውስ እንዳይከሰት ራሷን ማዘጋጀት ይኖርባታል፡፡
2.   የመብት መገደብ፡
አማኞች ወይም ቤተ ክርስቲያን ከፖለቲካው ከራቁ  የቤተ ክርስቲያን እና የክርስትና መብት ይገደባል፡፡ የማምለክ መብት፣ ወንጌልን በአደባባይ የመስበክ መብት፣ ነጻነታችን ሁሉ ይገደባል፡፡ በግል ክርስቶስን መከተል ባይከለከልም እንደ ቤተክርስቲያን በጋራ አዳራሽ ሞልተን አደባባይ አጣብበን ማምለክ፣ መዘመርና ማእለል ሁሉ ይገደባል፡፡ ቤተ ክርስቲያንና ሚኒስትሪ መክፈት፣ በየቀበለው ከፍተኛ የድምፅ ማጉያ  ተክለን ስብከታችንንም ሆነ ምስጥራዊ ሊሆኑ የሚገባቸውን ጸሎቶቻችንን ሁሉ ጭምር ለአቅራቢያው እስክናሰማ ድረስ የምናደርገው አካሄድ እያጠረ ፣ ቀስ በቀስ አንዳንዴ በፍጥነትም ሁሉም እየተሰፈረ መሰጠት ይጀምራል፡፡ የአምልኮ ቦታ በሕጋዊ መንገድ የመጠየቅ መብት እንደበፊቱ በነጻነት አይሆንም፣ ገመዱ እያጠረ ይሄዳል፡፡ አሁን አስፍተን የምያናቸውን ሁሉ በቀዳዳ በኩል  በአንድ ዓይን እንድናያቸው የሚያደርግ ጫና ሊደረብን ይችላል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ መንግሥት በሓይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም፣ ሃይማኖትም በመንግሥት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም የሚለውን መርህ  አየት ማድረጉ አይከፋም፡፡ ይህ ለብዙዎቻችን በጣም ተራማጅና መልካም አሳብ ይመስለናል፡፡ መንግሥት ቤተ ክርስቲያንን እንደዚህ አድርገሽ ስበኪ ወይም አስተምሪ ፣ የጸሎትሽም ይዘት እንደዚህ ይሁን እንጂ ሌላ አልፈልግም እያለ ማድረግ ያለባትን እየመዘነ አይሰጥም ማለት ብቻ ይመስለናል፡፡ ግን ከዚያም ያለፈ ጣጣም አለው፡፡ መንግሥትና ሃይማኖት ተለያዩ ማለት ማንም ሰው የፈለገውን እምነት የመከተል መብት እንዲኖረውና ቤተ እምነቶችም በሚከተሉአቸው የእምነት አቋማቸው ላይ መንግሥት እጁን አያስገባም ማለት ቢሆንም በአንጻሩ ደግሞ  ማንም ሌላውን ሰው ይህንን እምነት ተከተል ይህንን ደግሞ አትከተል ማለት  እንደማይችልም የሚደነግግም ነው፡፡ በሌላ አባባል ወንጌል በመስበክ የሰዎችን ሃይማኖት ማስቀየር ሊያስከስስ ይችላል እንደማለትም ነው፡፡ ኢየሱስ ያድናለና ጌታን ተቀበል ማለት ሊያስወነጅል የሚችል ይሆና እደማለት ነው፡፡ የመንግሥትና የሃይማኖት ልዩነትን ፍልስፍና ከመጀመሪያውም የጠነሰሱት  የአሜሪካን የመብት አንቀጽ አርቃቂ የነበሩ እንደ ጃምስ ማዲሴን ያሉ ሲሆኑ አሳባቸው ቤተ ክርስቲያን ወይም ሃይማኖት ከማህበረሰቡ ሥልጣን ውጭ ብትሆንም የአንድ አገር ሕጋዊ ሥልጣን እንደሚመለከታት አልሸሸጉም፡፡ እንደ ማዲሴን አባባል መንግሥትና ሃይማኖት መለያየት ሁለቱም በሚያደርጉት ውሳኔ የሌላ እጅ ጣልቃ የማይገባበትና የመንግሥትም ሆነ የሃይማኖት ንጽሕና እንዲጠበቅ ያስችላል፡፡ ስለዚህ ይህ ጉዳይ በተለያዩ ጊዜያቶች ተተችቶበት ለ25 ጊዜ ያህል ወደ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቀርቦ ነው ውሳኔን ያገኘው፡፡  መንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ አይገባም ፣ ሃይማኖትም በመንግሥት ጣልቃ አይገባም የሚለውን መርሀ ቃል በራሳቸው መንገድ የተረጎሙ እንደ ሞርሞን፣የይሖዋ ምስክሮች፣አሚሾችና ሌሎች የመሳሰሉትም ኢየሱስ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 18፡36 ላይ “የእኔ መንግሥት ከዚህ ዓለም አይደለችም፣ መንግሥቴ ከዚህ ዓለም ቢሆን ኖሮ ሠራዊቶቼ ይዋጉልኝ ነበረ” ያለውን አሳብ አክለውበት የእኛ መንግሥት ከዚህ ዓለም ስላይደለ የዚህ ምድር መንግሥት በሚያደርገው ሁሉ አንሳተፍም የሚል አቋም ያዙ፡፡ ይህ ማለት መንግሥትን አንደግፍም፣ አገርን አንከላከልም፣ ግብር አንከፍልም ወዘተ የሚል ጥግ ይዘው ተገኙ ማለት ነው፡፡  ነገር ግን የካቶሊክ ቤተ ክርሰቲያን ማንም ሰው እንደፈለገው የሃይማኖት ነጻነት ሊኖረው ይገባል ግን ያ የሃይማኖት ነጻነት በአገሪቱ ሕገ መንግሥት እውቅናን ማግኘት ይኖርበታል የሚል አቋም ያዙ፡፡ ከዚህም ጋራ በመጨመር የካቶሊክ ቤተክርስቲያን የሃይማኖትና የመንግሥት መለያየት ስለማይዋጥላት  መንግስት የሚወስዳቸው ውሳኔዎች ሚዛን እንዲጠብቁ ለማድረግ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው በቂ ሚና መጫወት ይኖርባታል የሚለውን መርህ አጠንክራ ያዘች፡፡ የሆነ ሆኖ መንግሥትና ሃይማኖት የመለያየታቸው ጉዳይ የፍርድ ቤት ውሳኔ ካገኘ በኋላ ክርስቲያኖች ከአምልኮ ሥፍራ ውጪ የሚያደርጉአቸው መንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ገደብ ይበጅላቸው ጀመር፡፡ በመንግሥት ትምህርት ቤቶችና በሠራተኞች መሰብሰቢያ ቦታዎች ላይ የተሰቀሉ አሥርቱ ትዕዛዛትን የያዙ ጽሑፎች እንዲወርዱ ተጠየቀ፣ወረዱም፡፡ በግልም ሆነ በመንግሥት ትምህርት ቤቶች ትምህርት ከመጀመሩ በፊት የሚደረገው ጸሎት እንዲቀር ተጠየቀ፣ ቀረም፡፡ በየትኛው ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ክፍል ውስጥ የቡድን መጽኸፍ ቅዱስ ጥናት እንዳይደረግ፣ በግል ትምህርት ቤቶችም ቢሆን የመጽሐፍ ቅዱስ ነክ ትምህርት እንዳይሰጥ ክልከላ እየተደረገ መጣ ፡፡ በአገራችንም መንግሥት በሃይማኖት፣ ሃይማኖትም በመንግስት ጉዳይ ጣልቃ አይገቡም እና በቤተክርስቲያን ትምህርት ቤቶች ውስጥ ለተማሪዎች መንፈሳዊ ትምህርት ማድረግ ፣ ወንጌልን መስበክ፣ መጽሐፍ ቅዱስን እንደ አንድ ትምህርት መስጠት የማይቻል እየሆነ መጣ፡፡ ይህም በመሆኑ መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ፣ ሃይማኖትም በመንግሥት ጉዳዮች ጣልቃ አይገባም የሚለው መርህ ቤተ ክርሰቲያን መንግሥት በሚያደርገው ጥፋት ድምጽ እንዳታሰማ ሊከለክል የሚችል ነው፡፡ ምክንያቱም ሃይማኖት በመንግሥት ጉዳይ ጣልቃ አይገባምና፡፡    
3.   ፍትህ መጉደል፡
አማኞች እና ቤተ ክርስቲያን አማኝ ባልሆኑና በሌሎች ድርጅቶ የታቀደ ጥቃት ሊደርስባቸው ሰሚ ዳኛ ሊያጡ ይችላሉ፡፡ በተለይም የመንግሥት ባለሥልጣናት ክርስትናን የሚቃወሙና የሚጠሉ ከሆነ በየሰበቡ ክርስቲያኖች ይጠቃሉ፡፡ ከቀበሌ እስከ ሚኒስትሮች ምክር ቤት ባሉ የሥልጣን እርከኖችና መምሪያዎች አማኞች የሉም ማለት በቤተ ክርስቲያን ላይ ሁኔታዎች ከበድ ያለ መሆኑን ያሳያል፡፡ የቀበሌ ሊቀመንበር፣ የወረዳው ባለሥልጣናት፣ የፖሊስ አዘዦች፣ የማዘጋጃ ቤት ሹሞችና የመምሪያ ኃላፊች( DEPERETMENTS HEADS ) የክልል ርዕሰ መስተዳድሮች ፣ ሚኒስትሮች ፣ ዴኤታዎች ፣ ከስራቸውም ያሉ የመምሪያ ኃላፊዎች እግዚአብሔርን የማይፈሩና የቤተ ክርስቲያንን መኖር የማይፈልጉ ከሆነ ቤተ ክርስቲያን የሚደርስባትን ጥቃት ለመቃወምና መብቷን ለማስከበር አቤት የምትልበት ሥፍራ ታጣለች፡፡  የተቀበረውን ሬሳ ከጉድጓድ አውጥተው ሜዳ ላይ ሲጥሉ ወይም እንጨት ላይ ሲያንጠለጥሉ የሟች ቤተሰብ  የሚደርስበትን በደል ለማን እንደሚናገር መላ የሚጠፋው አስተዳደሩ ፀረ ክርስትና  ሲሆን ነው፡፡ የድርጊቱ ተዋኒያንን የሚሸፍን መሪ ባለስልጣን ባለበት አካባቢ ይህ ሲሆን አይተናል፣ ይኸውም ዴሞክራሲ አለ በሚባል አገር!  ባለፈው ሳምንት በናይጄሪያ አምላካቸውን እያመለኩ ባሉ ክርስቲያኖች ላይ ሌላ እምነት  ተከታዮች ከፍተኛ ጥቃት አደረሱ፡፡ በቤተ ክርስቲያኑ ግቢ የነበሩ የቅዱሳንን  መኪናዎች አንድ በአንድ በእሳት ካያያዙት በኋላ ወደ ቤተ ክርስቲያን ውስጥም ዘልቀው በመግባት አማኞች መደብደብና መግደል ጀመሩ፡፡ ያ የሆነበት ምክንያት ሴሌጃ በሚባል በዚያ ግዛት ውስጥ ከሙስሊሞች በስተቀር ሌላ እምነት፣ ከዓርብ በቀር ሌላ የአምልኮ ቀን መኖር የለበትም በሚል ነው፡፡ ይህ ሲሆን ክርስቲያኖች የጸጥታ አካል ወደሆነው ክፍል ቢደውል ፖሊስ የተላከው ሁሉም ነገር ከወደመ በኋላ ነበር፡፡ የናይጄሪያው ክርስቲያን ህብረት ዋና ዳይሬክተር ቄስ ሙሳ አስኬ የመንግሥትን ቸልተኝነት አስመልክተው ሲናገሩ : “መንግሥት ራሱ ክርስቲያኖችን ከዚህ አገር ለማጥፋት ይፈልጋል፡፡ ለሌሎች ሃይማኖቶች ያደላል፡፡ እኛ በዚህ አገር እንደ ሁለተኛ ዜጋ እንታያለን፡፡ በዚህ አገር ያሉ የጸጥታና የዋስትና ኤጄንቶች ሁሉ በሰሜኑ ሰዎች እጅ ሥር ናቸው፣ በሰሜን የአገሪቱ ክፍሎችስ ክርስቲያኖች የሉንምን ? አሁን ክርስቲያኖች ተገልለናል ግፍም እየደረሰብን ነው፡፡ እኛ ጥቃት እየሰድረብን እያለ መንግስት ለሌሎች ሃይማኖቶች ስለሚያደላ እኛ እንደ ሁለተኛ ዜጋ ተቆጥረናል፣ ግድ የለም አምላካችን ግን አልተኛም” በማለት ሆድ የሚያብስ ነገር ተናገረ፡፡ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በክረምት ወር 1984 ዓ.ም በአዲሰ አባባ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደው የአብያተ ክርስቲያናት መሪዎች ኮንፍራንስ ላይ ዶር አዲዬሞ ቱኩንቦ የተናገረውም ይህንን የሚመስል ነገር ነው፡፡ ዶር ቱኩምቦ ቤተ ክርስቲያን በናይጄሪያ በየጊዜው የሚደርስባትን ጥቃት አስመልክቶ ሰፊ ምስክርነት ከሰጡ በኋላ በኢትዮጵያም ሆነ በሌሎች አገሮች ያሉ ክርስቲያኖች ከሌሎች ጥቃት ሲደርስባቸው መንግሥት ዋስትና ካልሰጠ ራሳቸውን ለማዳን ድምጻቸውን ማሰማት መቻል አለባቸው ይል ነበር፡፡ ካቀረባቸው መብትሔ አሳቦች አንዱ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ የሚል ይገኝበታል፡፡ ይህ እንግዲህ ከ25 ዓመት በፊት ነው፡፡ ዶር ቱኩምቦ እንደተናገሩት አስቀድመው ክርስቲያኖች በእጃቸውን ያለውን ሥልጣንና መብት ቸል በማለታቸው  ሌሎች ስለተጠቀሙበት ያ ሁሉ ችግር ደረሰባቸው፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያኖችም ፖለቲካን በሩቁ ካሉና ምንም እንቅስቃሴ ካላደረጉ በቆይታ ወይ ከመንግሥት ወይ ከሀይማኖት አካላት ተመሳሳይ ችግር ሊደርስባት ይችላል፡፡ ክርስቲያኖች በፖለቲካው ጉዳይ ቸል ካሉ በእነርሱ ላይ ጥቃት ሲደርስባቸው ቸል የሚል መንግስት በአገር ላይ እንዲሾም እየፈቀዱ ናቸው፡፡
እንግዲህ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካ መሳተፍ የለባትም በፖለቲካ ባትሳተፍም ችግር ይገጥማታል ካልን የቱጋ እንሆናለን የትኛው ነው የሚያስፈልጋት የሚለውን መፍታት ይኖርብናል፡፡ 
ከአገርና ከፖለቲካ ውጥረቱ አንጸር ቤተ ክርሰቲያን ምን ታድርግ;
 እስከ አሁን ቤተ ክርሰቲያን በፖለቲካ መሳተፍ አለባት የለባትም በሚለው አሳብ ላይ ብዙ ስናወጋ እዚህ ደርሰናል፡፡ እኔ በበኩሌ ቤተ ክርስቲያናችን በፖለቲካ ከመሳተፍዋ በፊት ተሰጣትን ሥራ ትጨርስ እንጂ ፖለቲካ ውስጥ ካልገባች ብለን ያልተሰጣትን እንድትሠራ አናስገድዳት እያልኩ ቆየሁ፡፡ አሁንም እንደዚያው ነኝ፡፡ በፖለቲካው ባትሳተፍ ግን የሚገጥማት ተግዳሮት መኖሩንም ደግሞ እንደ አቅሜ አስቀምጫለሁ፡፡ ይህንን ስል  ቤተ ክርስቲያን በአገር ጉዳይ ምንም አያገባትም እያልኩ እንዳልሆነ አስምሬበት አልፌአለሁ፡፡ በዛሬው ጽሑፌ የማሳየው ቤተ ክርሰቲያን እንደ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው ተሳታፊ ሆና፣ ወንበርም ተዘጋጅቶላት በፓርላማ ስተቀመጥ ብናይ ሞቅ ሊለን ይችል ይሆናል ፣ ግን ያ ብቻውን የሚሰጠን ረብ ሊኖረው አይችልም፡፡   ሁላችንም እንደምናምነው ቤተ ክርስቲያን የአገር ፍቅር ፣ የአገር ኃላፊነት፣ የሕዝቦች ሸክም ሊሰማት ይገባታል፡፡ በተለይም ደግሞ የወንጌላውያን አማኞች ያለ ምንም ልዩነት የዓለምን ሕዝቦች መውደድ ይኖርባቸዋል፡፡ የእግዚአብሔር ቃል እንደሚያስተምረው  በማድረግ የሕዝቦችን ችግር ማቅለል የምትችለው ቤተ ክርስቲያን ነች፡፡ እኛ በርዕሰ ጉዳያችን የምንናገረው ስለ ፖለቲካው ስለሆነ ነው እንጂ የቤተክርስቲያን ኃላፊነት በሁሉም አንጸር ነው፡፡  መንግሥት ተፈጥሮን በቁጥጥራችን ሥር እናደርጋለን ቢልም ዝናብ ሲጠፋ ፣ ሰዎችና እንስሳት ከውሃ እጥረት የተነሳ ሲያልቁ ተፈጥሮን በቁጥጥር ሥር እናደርጋለን የሚለው ሁሉ ፉከራ ሳይሥራ ቀርቶ  አይተናል፡፡ ታዲያ ቤተ ክርስቲያን ምን ታድርግ ለሚለው የሚታየኝ ከዚህ በታች ባሉ አምስት አቅጣጫዎች Aspects  ማትኮር ይገባታል ባይ ነኝ፡፡ ከዚየ ቦኃላ ራሷ በቀጥታም ሆነ በተዘዋሪ መንገድ አባላት እንዲሳተፉ በማዘጋት ኃላፊነቷን መወጣት ትችላለች፡፡ ቤተ ክርሰቲያን በፖለቲካ ከምትሳተፍ አማኞች እንደ ግለሰብ ቢሳተፉና ጠንክረው ቢታገሉ የተሻለ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያ እንደ ድርጅት ሰትካፈልና አማኞች ሲሳተፉት አንድ አይደለም፡፡ ልዩነቱን መተንተን የሚያስፈልው አይመስለኝም ግን ከአምስቱ አቅጣጫዎች ለዛሬ ሦስቱ እነሆ፡

1.      መንፈሳዊ አቅጣጫዎች Spiritual Aspects :

ቤተ ክርስቲያን መንግሥትን  ወይም ደግሞ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አባላትን እንድትቋቋመው የሚፈልጉ ወገኖች ሁሉ አስቀድመው የቤተ ክርስቲያንን ተልዕኮ ማሰብ ይኖርባቸዋል ባይ ነኝ፡፡  ጌታ እግዚአብሔር ፣ ኃያሉ አምላክ በልጁ ደም የዋጃት ቤተክርቲያኑ ክብርትና ንጽሕት እንዲትሆን ይፈልጋል፡፡ ለዓለም ሕዝቦች ሁሉ ክርስቶስን የምትገልጽ የእርሱ አምባሳደር እንድትሆን ይጠበቅባታል፡፡ ይህ ለቤተ ክርስቲያን የማንነቷ ጉዳይ ፣ ከምንም ጋር የማታወዳድረው ሀብቷ የምንጊዜም መታወቂያዋ ነው፡፡ ሞገስዋና ጉልበቷ (መንፈሳዊ አቅሟ ማለቴ እንደሆነ ይሰመርልኝ) ያለው እዚህ ውስጥ ነው፡፡ በምድር ላይ ያለቺው ቤተ ክርስቲያ የቱንም ያህል መንግሥትን ብትቃውም ወይም ብትደግፍ ክብሯንና ንጽሕናዋን ፣ የተፈጠረችብትንም ማንነት የጣለችና ያጣች እንደሆነ በምታደርገው ሁሉ አንድ የፖለቲካ ድርጅት ከሚያደርገው በላይ የከበደ ነገር ሊኖራት አይችልም፡፡ ሐዋሪያት የኢየሩሳሌምን ከተማ እና በአካባቢው ያለውን ግዛት ያነቃነቁት መንፈሳዊ ማንነታቸውን ጠብቀው ስለቆሙ ነው፡፡ ከአሁኑዋም ቤተ ክርስቲያን የተሰጣት አምላካዊ ተልእኮ አለ፡፡ ያውም ወንጌልን ለሰው ልጆች ሁሉ መስበክ፣ ያመኑትን ደቀ መዛሙርት ማድረግ፣ እግዚአብሔር በእውነትና በመንፈስ እንዲመለክ ቅዱሳን ማነሳሳትና ማገዝ ነው፡፡ የምድሩም ጉዳይ ስለሚያገባት አጥብቃ መጸለይ የተሰጣት ተልዕኮ መሆኑን ብሉይም ሆነ አዲስ ኪዳናት የሚያስስቧት ነው( 2ዜና 7፡14፣ 1 ጢሞቴዎስ 2፡1-5)፡፡ መንግሥት ጨካኝና አሬሜአዊ እንኳ ቢሆን የተሰጣት ሃላፊነት መጸለይ ነው፡፡  ሐዋሪያው ጳውሎስ ልመናና ጸሎት ምልጃና  ምስጋናም ስለ ሰዎች ሁሉ ስለ ነገሥታትም ስለ መኳንንትም ሁሉ እንዲደረግ ከሁሉ በፊት እመክራለሁ ሲል ነገሥታትና መኳንንት እኮ እንደነ ኔሮ ያሉ ጨካኞችና አብረው ያሉት አይደሉምን? ናቸው እንጂ! በጸሎትና በጸሎት ኃይል እናምናለን እያልን የመንግሥት አቋም አልዋጥ ብሎን በሚጎመዝዘን ሰዓት የተቃውሞ ሰልፍ ማስተባበርና የአቋም መግለጫ ማውጣት ቤተ ክርስቲያን ከተሰጣት ተልዕኮ ጋር አይገጥምም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን ከመስበክና ጸሎት ከማድረጉ ጎን ለራሷ ቅድስትና ንጽሐት መሆኗን ማረጋገጥ ይኖርባታል፡፡ ስለ ቅድስና መስበክ የሚያስፈራን ለምንድነው? እግዚአብሔርን ስለመፍራት ማስተማር እንደጦር የሚያስጋን ምን ብንሆን ነው? ነገራችን እየባሰበት መጥቶ  ፊቺ፣ ዘረኝነት፣ ስርቆት ፣ ዝሙት፣ አመንዝራነት እና የእርስ በርስ መካሰስ ዙፋናቸውን ዘርግተውብን የሚነካቸውም ሆነ የሚደረፍራቸው የታጠው ለምንድነው ማለት አያስፈልግምን? ከዚህ አንጸር ቤተ ክርሰቲያን ሥር ነቀል ተሀዲሶ የሚያስፈልጋት ናት እንጂ መንግሥትን ለመቃወም የሚያስችል ማንነትና መንፈሳዊ ሥልጣን አላት ማለት የሚቻል አይደለም፡፡ እኔ መንግሥትን የሚሾመው እግዚአብሔር እንደሆነና ሰው ሁሉ ለተሸመው ሥልጣን ማስገዛት እንዳበት( ሮሜ 13፡1-) አምናለሁ፡፡ ስልጣን ስንል የመንግሥት ሥልጣን ብቻ ሳይሆን የቤተሰብንም የቤተ ክርስቲያንንም፣ የድርጅትንም ሥልጣን ሁሉ የሚያካትት እንደሆነ መካድ አልፈልግም፡፡ መንግሥት ከእግዚአብሔር የተሰጠውን ሥልጣን ያለቦታው ሲጠቀምና በሕዝብ ላይ በደል ሲያደርስ ቤተ ክርስቲያን የእኔ ሥራ መጸለይና መስበክ ነውና በሚል በሯን ዘግታ፣ ጭንቅላቷንም አሸዋ ውስጥ ቀብራ አላየሁም፣ አልሰማሁም  ትበል የሚል አቋም የለኝም፡፡ የጨለማውን ሥራ ሁሉ መግለጥ፣ አፍ ላጡ አፍ፣ ድምጽ ላጡ ድምጽ መሆን ይጠበቅባታል፡፡ ያንን ከማድረግ በፊት አስቀድማ ግን የጣለቸውን ማንሳት፣ የለበሰቺውን ድሪቶ ማውለቅ፣ ቤቷንና ጓዳዋን ከቆሻሻ ማጽዳት ይኖርባታል፡፡  እንደገና ጌታንና ከእግዚአብሔር የሚሰጣትን መንፈሳዊና መለኮታዊ ሥልጣን መልበስ ይኖርባታል፡፡ ያኔ መንግሥትም በውስጧ ለተቀመጠው ሥልጣን ቀኝ እጁን ይሰጣል ባይሰጥ ከቤተ ክርሰቲያን ጋር ያለውን የእግዚአብሔርን መኖር ይለማመደዋል ማለት ነው፡፡ 
     
2.     ኢኮኖሚያዊ አቅጣጫ Economical Aspect

 ገንዘብ የማይገባበት ሥፍራ የለም፡፡ ስልጣንና ገንዘብ አብረው የሚሄዱ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ስለ ገንዘብ ያላት አመለካከት ራሱ በብዙ አንጻር  ተሃዲሶ የሚያስፈልገው ነው፡፡ አንዳንዶች በባሕታዊነት የሚያምኑ ሲሆን ሌሎች ደግሞ የብልጽግና ወንጌልን መስበክ ያስደስታቸዋል፡፡ ባህታዊነትና የገዳምን ሕይወት የሚያምኑ አገልጋዮቻቸው ገና ወደ ገዳም ሳይገቡ የባህታዊነትን ሕይወት እንዲኖሩ የሚፈልጉ፣ ያንኑንም የጽድቅ መንገድ አድርገው የሚወስዱ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ሳገለግል ከጓደኛዬ ጋር ምሳ ከበላን በኋላ በአንድ ካፍቴሪያ ሻይ እየጠጣን ሳለ ኬክም አዝዘን ስንበላ እግር ጥሎአቸው ወደነበርንበት ካፍቴሪያ የመጡ አንድ የቤተ ክርስቲያን መሪ ተቆጡን ፣ ወንጌላውያን ሆናችሁ እንዴት ኬክ ትበላላችሁ በሚል፡፡ እውነት ለመናገር እኛ በጊዜው ኬክ ምንበላው በሁለት ወር አንዴ ያውም አንዱን ኬክ ለሁለት ነበር( አጋጭተን ማለት ነው)፡፡ ያንኑንም ባንበላ ኬክ ቀርቶብን እንደምንጎዳ አንቆጥርም ነበር፡፡  ጊዜያትን ቆጥረን ለሁለት አጋጭተን በበላንባት ቀንም ቢሆን እኒያ አባታችን ወደዚያ ካፍተሪያ ገቡና አዩብን፡፡ ሲቆጡ እውነት አድርገን አልወሰድንም፣ የሚቀልዱ መስሎን እኛም ሳቅ ሳቅ ማለታችን በበለጠ አስቆጣቸው፡፡ የምራቸው መሆኑ ሲገባን ስሜታችን ልውጥውጥ ስልብን ጊዜ ክርስትናችን እንዳይከዳን ብለን እንደምንም ያቺን ደቂቃ ችልን ማለፋችንን አስታውሳለሁ፡፡ ወንጌላዊ ኬክ መብላት መሪውን እስክያስቆጣ ድረስ ወንጀል የሆነበት ምክንያት እስከ አሁንም አልገባኝም፣ ሊገባኝም አይችልም፡፡ በእሳቸውና በብጤዎቻቸው አስተያየት ኬክ መብላት ለወንጌላዊ የተከለከለ፣ የበላ እንደሆነ  በኃጢአት እንደሚወድቅ ፣ እሳቸው ልጆቻቸውና ሌሎች አይደለም ኬክ ሌላም አልፈው ቢበሉ ግን የፈቀደ ነው፡፡ ለማንኛውም ቤተ ክርስቲያን ስለ ባሕታዊነትም ሆነ ስለ ብልጽግና ብትሰብክ ስለ ገንዘብ ያላት አቋሟ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሆን አለበት፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ስለ ገንዘብ የምትሰብከው ምዕመናን አሥራታቸውን በጊዜ እንዲሰጡ፣ ለሕንጻ ግንባታ ገንዘብ ማሰባሰቢያ ጊዜ ዳጎስ ያለ ገንዘብ፣ ወርቅና  ሌላም ንብረት በመስጠት ውድድር እንዲሽቀዳደሙ ነው፡፡ የስብከቱም ርዕስ ስጡ ይሰጣችኃል፣ ስጡ ትባረካላችሁ ወዘተ ነው፡፡ በገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ሊሰብኩ መጥተው የእኔ ሥራ በየሄድኩበት ኪስ ማስወለቅ ነው ብለው ያለምንም እፍረት የሚናሩ ሰባኪዎች አሉ፡፡ አሁን የምስተዋለው የቤተ ክርስያናት የገንዘብ አመለካከትና ገንዘብን የማግኛ ዓላማና መንገድ ከላይ ካየናቸው እውነታ ብዙም የዘለሉ አይደሉም፡፡ ይሁን እንጂ የእግዚአብሔር ቃል ስለ ገንዘብ የሚለው ተዝቆ የማያልቅ ትምህርት አለ፡፡ ገንዘብን በጽድቅ ስለ ማግኘትና በጽድቅ ስለ ማውጣት፣ በገንዘብ ቤተ ክርስቲያንን ስለማገልገልና ስለ መስጠት ቃሉ በጥልቀት ያስተምራል፡፡ ገንዘብና አማኞች ሊኖራቸው ስለሚገባቸው መሠረታዊ እውነት ትልቅ ነገረ መለኮት ሊበጅለት ይችላል፡፡ በንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩ አባሎቻችን ንግዳቸው በትምህርትና በእውቀት የተደገፈ እንዲሆን በማሰልጠን በተሰማሩበት ሙያ እድገት እያሳዩ ለራሳቸውም ለቤተክርስቲያንም ሆነ ለምድሩ በረከት እንዲሆኑ የማዘጋጀት ሥራ መሥራት የቤተ ክርስያን ኃላፊነት ነው፡፡ አማኞች የገንዘቡን ቁልፍ ቦታ እንዲይዙ፣ እንዲያድጉ፣ ከማጭበርበር ነጻ በሆነ መንገድ እየነገዱ በአገሪቱ ምጣኔ ሀብት ተወዳዳሪነታቸውን ማሳየት እንዲችሉ ለማድረግ ቤተ ክርስቲያን በእጇ ያሉትን ሰዎች በትጋት ማሰልጠን፣ ማስታጠቅ፣ በሀብታቸው እንዲያድጉ ማበረታታት ይኖርባታል፡፡ ስጡ ይሰጣችኋል፣ ትባረካላችሁ የሚለው ትምህርት ኪስ ለማውለቅ ብቻ የሚደረግ የመድረክ መታለያ ከመመስል ማለፍ ይኖርበታል፡፡ ፖለቲከኞች ገንዘብ ላላቸው እንደ ቅቤ ይቀልጣሉ አሊያም በሰበብ በአስባቡ ይጠፉአቸዋል፡፡ ምክንያቱም እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ደሀ አገር የፖለቲካው ጨዋታም ቢሆን የሚሰምረው ከገንዘብ ጋር ነው፡፡ ገንዘብ ከእውቀት በላይ ይጮሃል፣ ይሰማልም፡፡ ከመሸታ ቤት ወጥቶ ወደ ቤተ መንግሥት ሲገባ ፈቃድ አይጠይቅም ሰተት ብሎ በፓርላማ ይቀመጣል፡፡ ድምጹም ያስጋባል፡፡ ከዚያ ሲወጣ በሴትኛ አዳሪ ቤት አልፎ ወደ ቤተ መቅደስ ሲመጣ በእለቱ መርሀ ግብር ሴሌዳ ውስጥ ለብቻው ጊዜ ይመደብለታል፡፡ በሰማይ መንገድ እንዳለው ንጣፍ ዓለትን ያለ መሰርሰሪያ በስቶ የመግባት ችሎታ ባለቤት እንደሆነ የሚያምኑ ብዙ ናቸው፡፡ ስለዚህ ከልጅ እስከ አዋቂ ፣ ከምሁር እስከ አላዋቂ፣ ከመምህር እስከ ተማሪ፣ ከካህን እስከ ምዕመን ፣ ከአገር መሪ እስከ ቤተሰብ አስተዳዳሪ ድረስ ለገንዘብ ያልተንበረከከ፣ በገንዘብም ያልተፈተነና ያልተሸነፈ አለ ማለት ያስታዝባል፣ ዋሾም ያደርጋል፡፡  ለገንዘብ ሲል ሲሉ ባልገባቸው ፖለቲካ ውስጥ የሚንደፋደፉ፣ አገር ለቀው የኮበለሉ፣ እምነታቸውን የለወጡ ፣ ነቢያት ሳይሆኑ ነቢያት ነን ያሉ፣ ሐዋሪት ሳይሆኑ ሐዋሪያት ነን ያሉ ከቁጥር በላይ ናቸው፡፡ ከፈለገ እንደ አምላክ ሰውን ይገዛል፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያናችን በአገሪቱ ፖለቲካ ውስጥ መሳተፍ አለባት ካልን በአገሪቱ መዋዕለ ንዋይ ወይ ምጣኔ ሀብቱ ጉልህ ሚና የሚጫወቱ አባላትን የሚታዘጋጅበት ስልት መቀየስ ይኖርባታል፡፡ ስጡ ትባረካላችሁ፣ ከምትለው ትምህርቷ ባለፈ ገንዘብን የማግኘት መንገዱ ይህ ነው፣ በዚህ መንገድ ሂዱና በልጽጉ፣እደጉ፣ ከዚያ ቤተሰባችሁን ፣ ቤተ ክርስያናችሁንና አገራችሁን አገልግሉ የሚለውን ትምህርት አጥብቃ ማስተማር ይኖርባታል፡፡ የነጋዴዎችና የባለሙያዎች አገልግሎት መደራጀት አለበት፡፡ አገልገሎቱም እንዲያድግ በባለሙያዎች አማካይነት ተከታታይ ትምህርትና ሥልጠና እየተሰጠ ነጋዴዎች በንግዳቸው ክህሎትም ተግባራዊነትም እንዲኖራቸው ማድረግ ይገባል፡፡ እግዚአብሔርም እንዲባርካቸው መጸለይ ይገባል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው ዓለም ተጽእኖ ሊታመጣ አትችልም፡፡ መንግሥት ሙስናን እዋጋለሁ ሲል ቤተ ክርስቲያን  የጽድቅን አሠራር ይዛ ሥርቆት ኃጢአት ነው፣ ጉቦ ኃጢአት ነው፣ ማጭበርበር ኃጢአት ነው የምትልና ልሳኗ የሚሆኑ ንጹሐን ነጋዴችን ማሰማራት ከቻለች በፓርላማ ወንበር ባይኖራት እንኳ በፖለቲካው ለውጥ የሚያመጣ አንድ ርምጃ ፈቀቅ ብላለች ማለት ይቻላል፡፡ በገንዘብ ላይ ግልጽነትን ልማዷ መሆን አለበት፡፡ በየእሁዱ ሳምታዊ የገቢና የወጪ ሪፐርት በአጭሩ ለምዕመናን የሚያቀርቡ ቤተ ክርሰቲያናት ያሉ አይመስለኝም፡፡ ግን መለመድ ያበት ነው፡፡ በጥቅሉ ቤተ ክርሰቲያን በአገሪቱ ኢኮኖሚ ግንባታ ቀደም የሚሆኑ ሊኖሩ ይገባቸዋል፣ እርሷም በዘርፉ መሰለፍ ይኖርባታል፡፡ ይህ ከሆነ በፖለቲካው ላይ ለውጥ ማምጣት ትችላለች ባይ ነኝ፡፡ 
                
3.     የትምህርት አቅጣጫዎች Educational Aspect

ቤተ ክርቲያን በፖለቲካ ትሳተፍ የሚሉ ወገኖችን አልቃወማቸውም ግን መቼም ቢሆን ወደ ሥራ ሲገባ መሣሪያ ያስፈልጋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ወደ ፖለቲካው ስትገባ ውጤታማ እንድትሆን የሚያደርጉ  መሣሪያዎች ( tools)ያስፈልጉአታል፡፡ ከመሣሪዎች አንዱ የትምህርት  ብቃት ነው፡፡ ፖለቲካ ራሱ እውቀትን የሚጠይቅ መሆኑ በማንም ሊካድ አይገባም፡፡ እግዚአብሔር የኢትዮጵያ ወንጌላውያ አብያተ ክርሰቲያናትን በተማሩ ሰዎች ባርኮአታል፡፡ ብዙ የህክምና ባለሙያዎችና የመረጃ ተክኖሎጂ አባላት አሉአት፡፡ ባለሙያዎቻችን አብዛኛዎቹ ሐኪሞች ወይም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሮፌሴሮች ናቸው፡፡ ሚሲዮናውያን ከዋሉልን ዉለታዎች አንዱ ብዙ የቤተ ክርስቲያን ሰዎች የሕክምና ሙያ እንዲሰለጥኑ በማድረጋቸው ወላጆች ልጆቻቸውን የሕክምና ዶክተሮች  እንዲሆኑ ማበረታታት የባህል ያህል ቦታ ያለው ነው፡፡ ከዚህ የተነሳ ከሌላው ሙያ ጋር ሲነጻጸር ዶክተሮች ብዙ ናቸው፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ፖለቲካ እንደ ኃጢአት ስለተወደሰ በፖለቲካ ትምህርት የተካኑ አባላት አሉ ማለት ያስቸግራል፡፡ ፖለቲካዊ ሳይንስ(political science ) የሚማሩ ክርስቲያን ተማሪዎች ምን ያህል ናቸው፡፡ የአመራር ትምህርት ( leadership)በከፍተኛ ዲግሪ የሚማሩ ለዚህም ዝንባሌ ያላቸው አባላት እና የአባላት ልጆች አሉን ወይ;፣አገራዊ( national)፣አህጉራዊና (continental) ዓለም አቀፋዊ( global) ሕግ ጠበብት አሉን ወይ; ካሉን ደግሞ  ቤተ ክርስቲያን በገንዘብም ቢሆን ደግፋ ከፍተኛ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ለማስቻል የተንቀሳቀሰችበት አጋጣሚ አለ ወይ? የሚሉ መሰል ጥያቄች መልስ ማግኘት ያበት ይመስለኛል፡፡ የሥነ መለኮትን ትምህርት ( Theology) የሚማሩ አገልጋዮቿን ገንዘብ ከፍላ እንደምታስምር ሁሉ በፖለቲካና በሕግ እንዲሁም  አመራር አስተማማኝ አቅም ለመገንባት ገንዘቤተ ክርስቲያን  አውጥታ በመስኩ የሚማሩትን ሰዎች ማፍራት አለባት ባይ ነኝ ፡፡ ተሳሳትክ ትሉኝ ይሆን? የህክምና ባለሙያዎች በረከት ሆነውልናል፣ የሥነ መለኮት ተማሪዎችም የእግዚአብሔርን ቃል አስታጠቀውናል፡፡  ፖለቲካ ግን ሙያቸው ስላይደለ እነርሱን ከዚህ አንጻር  መጠበቅ የለብንም፡፡ ፖለቲከኛ መሆን ግን ሌላ ብቃትና ክህሎትን እውቀትንም የሚጠይቅ ስለሆነ በጉዳዩ ማሰብ ተገቢ ነው፡፡ ሥነ መለኮት ተቋማት በእነዚህ ዘርፎች ሰዎችን ማሰልጠን ቢችሉስ ኃጢአቱ  እምኑ ላይ ነው? በአመራር በኩል የተጀመረ አስደሳች ነገር አለ፡፡ ወንጌላውያን አብያ ክርስቲያናት ተባብረው የፖለቲካ ትምህርት ከፍተው አባሎቻቸውን በከፍተኛ ዲግሪ ቢያሰለጥኑና የአገሪቱን ፖለቲካ እንዲመሩ የሚያስችል ክህሎት ቢያስታጥቁአቸው ራዕይ የጣሉ ያስመስልባቸው ይሆን? እኔ ግን ይህ መሆን አለበት ባይ ነኝ፡፡  ክርስቲያን በፖለተካዊ ሳይንስ ብቻ ሳይሆን በሁሉም የትምህርት ዘርፍ ተጽዕኖ ፈጣሪ  አባላት እንዲኖሩአት መጸለይና መሥራት  ይኖርባታል፡፡ ያለዚያ ግን ወደ ፖሊቲካው ሜዳ ወጥታ ያለ በቂ መሣሪያ ወደ ጦር ሜዳ እንደሄደ ተዋጊ ሠራዊት ትሆናለች፡፡ 
ቤተክርስቲያን በዚህ ምድር ላይ የሕበረተሰቡ አካል እንደመሆኑዋ መጠን ሕብረተሰቡን የሚለከት ነገር ሁሉ እርሷን ወደ ጎን ስለማይተዋት በህብረተሰቡ እልተእለት ጉዳዮች ላይ መግባት አለባት የሚል ሙግት በብዙ ይደመጣል፡፡ ሕብረተሰቡ ከሚጋፈጣቸው እለትተእለት ጉዳዮች አንዱ ፖለቲካና ከፖለቲካ ጋር ተያይዞ የሚመጣ ነው፡፡  እኔ በበኩሌ ቤተ ክርስቲያን ሠርታ ልትጨርሰው የማትችለው በጣም ብዙ ሥራ ስላላት ያንኑን ትወጣው ፣ ፖለቲካውን ለፖለቲከኞች ትተውላቸው እያልኩ ግን እንዲያው የግድ በፖለቲካ መሳተፍ አለባት ካልን መወሰድ ስላለባቸው ቅድመ ሁኔታዎች አስቀምጫለሁ፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው ውጤታማ እንዲትሆን ከፈለግን ተወዳዳሪነቷ ሊታሳይባቸው ከሚገባ ጠርዞች ሦስቱን ማለትም በመንፈሳዊ ሕይወት፣ በትምህርት፣ በኢኮኖሚ ተወዳዳሪ መሆን እንዳለባት ለማሳየት ሞክሬአለሁ፡፡ አሁን ደግሞ ትንታኔዬን ካቆምኩበት ልቀጥል፡፡ 
4
5.      የፖለቲካው አቅጣጫዎች Political Aspect

 ቤተክርስቲያን  የሕብረተሰቡ አካል እንደመሆኑዋ መጠን በህብረተሰቡ እለት ተእለት ጉዳዮች ላይ መግባት አለባት የሚል ሙግት በብዙ ይደመጣል፡፡ ሕብረተሰቡ ከሚጋፈጣቸው እለት ተእለት ጉዳዮች አንዱ ፖለቲካና ከፖለቲካ ጋር ተያይዞ የሚመጣ ነው፡፡  እኔ በበኩሌ ቤተ ክርስቲያን ሠርታ ያልጨረሰቺው በጣም ብዙ ሥራ ስላላት ያንኑን ትወጣው ፣ ፖለቲካውን ለፖለቲከኞች ትተውላቸው እያልኩ ግን እንዲያው የግድ በፖለቲካ መሳተፍ አለባት ካልን መወሰድ ስላለባቸው ቅድመ ሁኔታዎች አሳቤን አስቀምጫለሁ፡፡ እንደ እኔ  ቤተክርስቲያናችን መንግሥት ለምክርና ለጸሎት እስክፈልጋት ድረስ የከበደችና የተሞገሰች እንድትሆን እንናፍቃለን፡፡ መንግሥት  በከባባድ ጉዳዮቹ ላይ የቤተ ክርስቲያንን የጸሎት ርዳታ የሚሻበት እና በአገራዊ ጉዳይ መፍትሔ አመንጪና የችግሮችም ፈቺ እንደሆነች ተቀብሎ ራሱ ነይ ታስፈልጊናለሽ እያለ የሚያማክራት ቢሆን እንዴት በተደሰትን! ታላላቅ የአሜሪካን መሪዎች የተወደዱ አገልጋይ የሆኑ ዶር ቢሊ ግርሃምን እየጠሩ እንዲጸልዩላቸው ያደረጉበት ጊዜያቶች ብዙ ነበሩ፡፡ ለምሳሌ በጆርጅ ዴቭልዩ ቡሽ  ፕሬዝዳንታዊ በዓለ ስመቱን በጸሎት የመሩት ዶር ቢሊ ነበሩ፡፡ ቢሊ በአጭሩ እንደሚከተለው ጸልየው ፕሬዝዳንቱን ለሥራ አሠማሩ፡
 And now we come to a new era in our history. In Thy sovereignty Thou hast permitted George Bush to lead us at this momentous hour of our history for the next four years. As he today places his hand upon the Bible and solemnly swears before Thee to preserve, protect and defend the Constitution, give him the wisdom, integrity and courage to help this become a nation that is gentle and kind. Protect him from physical danger, and in the lonely moments of decision grant him Thy wisdom to know what is morally right and an uncompromising courage to do it. Give him a cool head and a warm heart. Give him a compassion for those in physical, moral and spiritual need. O God, we consecrate today George Herbert Walker Bush to the presidency of these United States with the assurance that from this hour on, as he and his family move into the White House, they will have the presence and power of the One who said, “I will never leave thee or forsake thee. [Hebrews 13:5(  የቢሊ ግርሃም ልጅ ፍራንክሊን ግርሃም ከጻፈው የኢሜይል መልእክት የተወሰደ)፡፡

 የኢትዮጵያ መንግሥትም ፕሬዝዳንቱንና ጠቅላይ ሚኒስትሩን ሲሰይም እጃቸውን ጭነው ተሽዋሚውንና አገሩን በጸሎት ለእግዚአብሔር አሳልፈው የሚሰጡ መሪዎች እንዲኖሩን ብንጸልይና ብንሠራበትስ! በአገራችን ላይ የእግዚአብሔር ሉዓላዊ አመራር እንዲሰፍን  ብንቃትትስ? ፓርላማው ስብሰባውን ከመጀመሩ በፊት የቤተ ክርስቲያን ቡራኬና ጸሎት የሚያስቀድምበት ሥርዓት እንዲኖር ለማድረግ መንፈሳዊ ጦርነት ብንዋጋስ? ሌላውን ሁሉ ትተን በዚህ በኩል ብንተጋ የበለጠ መልካም ይመስለኛል፡፡
ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው መሳተፍ ግድ ነው ካልንና በመስኩ  ውጤታማ እንዲትሆን ከፈለግን ተወዳዳሪነቷን ሊታሳይባቸው ከሚገባ ጠርዞች ሦስቱን ማለትም በመንፈሳዊ ሕይወት፣ በትምህርት፣ በኢኮኖሚ ተወዳዳሪ መሆን እንዳለባት ለማሳየት ሞክሬአለሁ፡፡ አሁን ደግሞ ትንታኔዬን ካቆምኩበት ልቀጥል፡፡ 
በፖለቲካ ውጤታማ መሆን እንዴት እንደሚቻል ከእኔ ይልቅ የዚያ ዘርፍ ባለሙያዎች ቢናገሩ የበለጠ ክብደት ይኖረዋል፣ ሰሚውም ጆሮውን የሚሰጠው ያኔ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ከአጠቃላይ ምልኬታዬ ተነስቼ የሚከተሉት ነጥቦች ትኩረት ሊሰጣቸው ይገባል ባይ ነኝ፡፡   የፖለቲካውን ሳይንስ መማር አስፈላጊ ቢሆንም ከዚያ ጋር አብረው የሚሄዱ ተጓዳኝ ነገሮች የመኖራቸው ሐቅ ሊሸሸግ አይችልም፡፡ ፖለቲከኛ መሆን ብዙ ረግዳሮት የሚበዛበት፣ ብዙ ተቃዋሚም ጠላትምንም የሚያፈሩበት ፣ ከተሳካም ደግሞ ለብዙ ሽልማትና ክብር የሚያበቃ ከፍ ያለ ሙያ ነው፡፡ ይህ ሙያ በህብረተሰቡ ውስጥ ልዩነትን የሚያመጣ በመሆኑ የዚያኑ ያህል አቅም የሚጠይቅ ነው፡፡ በሙያው ውጤታማ ለመሆን ጥንክሮ ከመሥራት ጋር ጠቢብ መሆንም ያስፈልጋል፡፡ ግን ውጤታማ ፖለቲከኛ ምን ዓይነት ነው፡፡
·         ተናጋሪነት( Eloquency)፡
የንግግር ችሎታ በፖለቲካው ዓለም ቀዳሚና ተወዳጅ ጉዳይ ነው፡፡ እውቀትን በንግግር መግለጽ የማይችሉ ሰዎች የፖለቲካው መሪ መሆን  ያስቸግራቸዋል፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠር ሕዝብ ትኩረት ከሳቡና አድማጫቸውን ማስከተል ከቻሉ የዓለም የፖለቲካ መሪዎች በርካታ ቁጥር ያላቸው በአንድ ርዕሰ -አሳብ ተናግረው የማሳመን ችሎታ ያላቸው ናቸው፡፡ ስለዚህ ነው በፖለቲካው ትምህርት ቤት በሕዝብ ፊት የመናገር Public speaking እና ግንኙነት communication የመሳሰሉት እንደ ዋና ኮርስ ተደርገው የሚሰጡት፡፡ ውስጣቸው በእውቀት የታመቀ ብዙ ምሁራን ቢኖሩንም ፊት ለፊት የሚታዩት ግን ተናጋሪዎች ናቸው፡፡ የሚናገሩ ሰዎች ይደመጣሉ፡፡
በዓለማችን ፖለቲካዊ ተሳትፎ የሚታይ ለውጥ ያመጡ  የቤተ ክርስያቲን መሪዎች እንዳሉ ታሪክ ይመሰክራል፡፡ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች የደቡብ አፍሪካው ዴድሞንድ ቱቱ የደቡብ አፍሪካ አንግሊካን ቤተ ክርሰቲያን ካህን ነበር፡፡ ቱቱ በጆሐንስቤርግ  በሚገኘው ቅዱስ ጴጥሮስ ስነ መለኮት ኮሌጅ St Peter Theological College ገብቶ ከተማረ በኋላ ከኪነግስ ኮሌጅ/ King”s College/ በሥነ መለኮት የመጀመሪያ ዲግሪ አገኘ፡፡ ከመንፈሳዊ ትምህርቱ ጋር ለቤተ ክርስቲያን የሰጠው አገልግሎት ከፍተኛ ሥፍራ ያለው ነው፡፡ በተለይም ከቅዱስ ጴጥሮስ ኮሌጅ ከተመረቀ በኋላ የአንግሊካን ቤተ ክርስቲያን ካህን ሆኖ ተሾመ፡፡  ወደ እንግሊዝ አገር በማቅናት  የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት የሚያስተዳድረው የሥነ መለኮት ትምህርት ቤቶች ፌንድ (Theoogical Education fund of the World councel of Churches) በተባለው ድርጅት ውስጥ ምክትል ፕሬዝዳንት ሆኖው አገልግሏል፡፡ ከእንግልዝ የ3 ዓመት ቆይታ በኋላ ወደ ደቡብ አፍሪካ ሲመለስ ደግሞ  የቅድስት ማሪያም ካቴድራል( Dean of St Mary’s Catedral) ዲን ሆነው ተሸመዋል፡፡ ታዲያ ቱቱ ኤች ኤ ቪ ኤዲስን፣ የዘር መድሎን፣ ድህነት፣ ወሲባዊ ትንኮሳን፣እና መሳሰሉትን በጥብቅ በመዋጋቱና በዚህ ረገድ ባስመዘገበው አመርቂ ውጤት የተለያዩ ዓለም አቀፍ ሽልማቶችን ለመቀበል ችሏል፡፡ ዴስሞንድ ቱቱ በትምህርት ብቃቱ እርሱን በብዙ የሚበልጡ ሰዎች ቢኖሩም ግን የንግግር ችሎታው በበለጠ አጉልቶታል፡፡ እንደ ሶቅራጥስ ፣ ሸክስፔር፣ አሌክሳንደር ፖፔ እና የከሳሰሉት የዓለማችን እውቅ  ፈላስፋዎችና መሪዎች የተናገሩት አሳብ እንደ እንደሚጠቀስ ሁሉ የዴስሞንድ ቱቱም ጥቅሶች በርካታዎች ናቸው፡፡ ሌላው አስገራሚ ተናጋሪ ሰው የአሜሪካው የጥቁሮች መብት ተሟጋች የነበረው ማርቲን ሉተር ኪንግ ነው፡፡ ሉተር ስለ ሰብዓዊ መብት የሚከራከር ቢሆንም የመጥመቃውያን ቤተ ክርሰቲያን መጋቢ ነበር፡፡ አባቱም ሆኑ አያቱ በአትላንታ ጆርጂያ ባለው የአቤንኤዜር መጥመቂያውያን ቤተ ክርስቲያን መጋቢዎች በመሆናቸው ሉተር ከልጅነቱ ጀምሮ ከቤተሰቡ መንፈሳዊ ነገር እየተመገበ አድጎ እንደወላጆቹ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ራሱን የሰጠ ሰው ነበር፡፡ በአልባማ ሜንቶጎሞሪ የሚገኘው የዳክስተር መጥመቃውያን ቤተ ክርሰቲያን ዋና መጋቢ ሆኖ እስከሞት እለቱ ድረስ አገልገሏል፡፡ ከቤተክርስቲያን አገልግሎቱ ጎን ፍትህ በተጓደሉባቸው ቦታዎች ሁሉ በመገኘት ስለ ሰዎች ልጆች መብት ለመከራከር 6 ሚሊዮን ማይልስ በመጓዝ 25 ሺህ ጊዜ ንግግር አድርጓል፡፡ በተለይም 250000 ሕዝብ በተሰበሰበበት በዋሽንግተን ባደረገው “እኔ ሕልም አለኝ / I have a dream /” በተሰኘው ንግግሩ ታይም መጋዝይን  የተሰኘው መጽሔት  “ man of the year (የዘመኑ ሰው )” የሚል ስም ሰጥተውታል፡፡ ከሰብኣዊ መብት ጋር በተያያዘ 25 መጻሕፍትን ጽፎ ከሕዝብ አስነብቧል፡፡  ለሰብአዊ መብት ባደረገው ተጋድሎ ጥቁሮች ከነጮች ጋር እኩል በሕዝብ አውቶቡስ እንድሳፈሩ እስከማድረግ ከመድረሱም በላይ ባደረገው መስዋዕትነት በተሞላው እንቅስቃሴው ምክንያት ከኖቬል በሽልማት የተገኘውን 54 123 የአሜሪካን ዶላር ከሰብአዊ መብት እንቅስቃሴ እንዲውል አበርክቷል፡፡ በእነዚያ ጊዜያቶች ሁሉ ኪንግ በነጮች ፖሊስ እየተያዘ ወደ እሥር ቤት ወርዷል፣ ቤቱም በቦምብ ጋይቷል፡፡ በመጨረሻም በዚህ እንቅቃሴው ምክንያት በባላንጣዎቹ ደረሰበት ጥቃት ሕይወቱን ሊያጣ ችሏል፡፡ በእነዚያ ሁሉ ጊዜያቶች የሚያሰማቸው ንግግሮች የአድማጩን ትኩረት በመሳብ ልዩነቶች ማምጣት ችለዋል፡፡
ሌላው ሰው ፈራክሊን ግርሃም ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ወንጌላዊው ፍራንክሊን በፖለቲካ መሪዎች ዘንድ ትልቅ ግምት ያገኘው ስለ ፖለቲካ ተናግሮ ሳይሆን ለውጥ የሚያመጣ እንቅስቃሴ አድርጎ ነው፡፡ በቅርብ ጊዜ ካደረጋቸው አውራ ተግባራት የተወሰኑትን ብንጠቅስ  ፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ የግብረ ሰዶማዊን ጋብቻ በጠቅላይ ፍርድ ቤት አስወስነው አንጀታችንን ባሳረሩበት ወቅት ጋብቻን የሚደነግግ እግዚአብሔር እንጂ መንግሥት ወይም ጠቅላይ ፍርድ ቤት አይደለም በማለት ቀጥተኛ ተቃውሞ በማሰማት ግንባር ቀደም ሰው ሊሆን ቻለ፡፡ የአሜሪካው ሕዝብ ፕሬዝዳንታቸውን ለመምረጥ በሚዘጋጁት ወቅት በ50ዎቹ ግዛቶች በመዘዋወር የአደባባይ ጸሎት እንዲደረግ ሕዝበ ክርስቲያኑንን አንቀሳቅሷል፡፡  እኔ በምኖርበት የሚቺጋን ግዛት ጸሎቱ የተካሄደው በግዛቱ ገዥ ቢሮ ግቢ ውስጥ ሜዳ ላይ በብዙ ሺህ የሚቆጡ ወንጌላውያ አማኞች በተሰበሰቡበት ሲሆን አሜሪካውያን በጸሎት ሰዓት ተንሰቅስቀው ሲያለቅሱ ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁት በዚህ የጸሎት ፕሮግራም ነው፡፡ ፍራንክሊንም በንግግር ችሎታው የተመሰገነ በመሆኑ የታላላቅ መሪዎችን ጆሮና ልብ እየማረከ ያለ የዘመናችን እውቅ አገልጋይ ነው፡፡    
ለመጥቀስ ያህል ብቻ እንጂ እነዚህን የሚመስሉ ብዙ የእግዚአብሔር ሰዎችና  ታሪኮቻቸው አሉ፡፡ ስለዚህ እኛ ከእነርሱ ብዙ መማር እንችላል፡፡ አማኞችና አገልጋዮች በፖለቲካው ተሳትፈው ለውጥ እንዲያመጡ እንጂ በፖለቲካው መሳተፋቸው ቁጥር ለመሙላት ብቻ እንዲሆን ይገባል ብዬ የማምንበት አቅም እስከአሁን አላገኘሁም፡፡ ተናጋሪዎች የሆኑ ፣ ፖለቲካን በየአንጓው እየሰበሩ ማስቀመጥና ለሚፈልገውም መስጠት የሚችሉ አባሎቻችን ካሉ እናበረታታቸውና ይሳተፉበት፡፡ መንግሥትንም በእኩይ ተግባሩ ይቃወሙት፣ በመልካም ሥራውም ያወዲሱት እላለሁ፡፡
ባለፈው በአገራችን በሕዝብና በመንግሥት መካከል በተፈጠረው ግጭት ምክንያት መንግሥት የተቃዋሚ የፖለቲካ መሪዎችንና ሌሎችን ለውይይት ጋብዞ ነበር፡፡ በዚያ ውስጥ የወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት መሪዎችም ነበሩ( የሃይማኖት መሪዎች ስለሆኑ ነው የተጠሩት ማለት ነው)፡፡ እነዚህ ወገኖች በዚያ ሥፍራ ተገኝተው የሚባለውን ሰሙ፣ ከገዥ ፓርቲም ሆነ ከተቃዋሚ የፖለቲካ አባላት የሚወረወረውን ክርክር አደመጡ፣ ከዚያም ወደ ቤታቸው መጡ፡፡ በዚያ ፎረም መሳተፋቸውንም ያወቅነው ምስላቸውን ቴሌቭዥን ስናይ ነው፡፡ ይህም በመሆኑ በጣም ደስ ይለናል፡፡ መሪዎቻችን በስብሰባው በተገኙበት አጋጣሚ ከገዥው ፓሪቲም ሆነ ለተቃዋሚ የፖለቲካ ተቋማት፣ ለመንግሥትና ለሕብረተሰብ የሚሆን ነገር ሲናገሩ ግን አልሰማናቸውም፡፡ በቤተ ክርስቲያናቸው ጣሪያ ሲያርገበግቡ ፣ መድረኩንም ሲያናውጡ የምናያቸው ሰባኪዎች በቤተ መንግስት አካባቢ ጸጥ ረጭ ያሉት ምን ነክቶአቸው ነው ባንል ይሻላል፡፡  እነዚህ ሰዎች የጸሎት ሰዎች ናቸው፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ሰዎች ናቸው እንጂ ፖለቲካን የሚያውቁ አይደሉም፡፡ የቤተ ክርስቲያን ቋንቋ እንጂ የፖለቲካ ነገር ውስጣቸው የለም፡፡ ስለዚህ ምን እንዲሉ ይጠበቃል?  መሄድ ሄደዋል፣ መሳተፍንም ተሳትፈዋል፣ የተጠሩበት ቦታ ሁሉ  ዋናውን  መሪ መላክ የቤተ ክርሰቲያን የቆየ ባህል ስለሆነ ያንን ልማድ ይዘው እዚያ ቦታ ሄዱ እንጂ ምን እንደሚያደርጉ ገብቶአቸው  አልነበረም፡፡ እንዳይናገሩ የአገሪቱን የፖቲካ አካሄድ አያውቁትም፣ የፖለቲካው ቃላትም/ terminology/ የላቸውም ፡፡ እነርሱ ያላቸው የሥነ መለኮታዊ ቃል  theological terms ነው፡፡ ያንን እዚያ ቢናገሩ የሚያደምጣቸውም የሚረዳቸውም የለም፡፡  በቤተ ክርስቲያን አካባቢ ያለን አገልጋዮች በሕዝብ ፊት ቆመን የመናገር እድላችን ከፖለቲካኞች ይልቅ የሰፋ ነው፡፡ የምንናገረው ግን የአንድ አቅጣጫ ንግግር/ Monologue/ የሚባል ዓይነት ነው ፡፡ ያውም አንደዳንዴ ተፋልሶ የበዛበት ቢሆንም ማንም አያርመውም፡፡ አንዳንዴ ሰፊ ሰዓት ተጠቅመን በተናርነው ነገር ውስጥ እዚህ ግባ የሚባል ቁም ነገር ሳንሰጥ ከመድረክ ስንወርድ አድማጩ እግዚአብሔር ይባርክህ ብሎ ይመርቀናል፡፡ ሰባኪዎች ሁሉ እንደዚያ ናቸው እያልኩ አይደለም፡፡ ይህ አሳብ በጣም በሚገርም ሁኔታ አስተምረውን  የቤተ ክርስቲያንን ያሳደጉ የተባረኩ አስተማሪዎቻችንን አይመለከትም፡፡ አንዳንድ ትርጉም የሌለው እንጨት እንጨት የሚል ነገር  እየተናገሩ ሕዝቡን የግድ አሜን እንድል ወይም እንዲያጨበጭብ የሚያድርጉ ፣ ቤተ መቅደሱንም በሁኬትና በጩኸት ሞልተው የሚወርዱ የዘመናችን ሰባኪዎችን ነው እንጂ፡፡ እንዲያም ሆኖ ጉባኤያችን ይባርካቸዋል፣ ይመርቃቸዋልም፡፡ በዚህ ልማድ የኖረ ሰው ወደ ሌላው አደባባይ ቢሄድና እናገራለሁ ቢል አሜን የሚለው የለም፣ ተከራካሪ ነው ያለው፡፡ ፖለቲካ በመንፈስ ሳይሆን በአእምሮ የሚሠራ ሰለሆነ አንድ ዓረፍተ ነገር ጣል ባደረግን ቁጥር ሁሉ አሜን በሉ የምንበልበት ቦታ አይደለም፡፡ እስቲ መድረኮቻችንን፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሚተላለፉ መልእክቶችን ፣ የመልእከቶችንም ይዘት ፣ ከእግዚአብሔር ዘላለማዊ ቃልም ጋር  ስላላቸው መስማማት ተመልከቱ፡፡ በሰማናቸው ቁጥር ምነው መካሪ በተገኘ የሚያሰኙ ናቸው፡፡ ምነው እነዚህን ሰባኪዎች እጃቸውን ይዞ የሚመራ የታጣው ያስብላል፡፡ ይህንን ስናይ ቤተ ክርሰቲያ በፖለቲካው ትሳተፍ ለማለት አቅም ያንሰናል፡፡ ምን ይዛ ፣ ማንን ይዛ የሚለው መሰመር ይኖርበታል፡፡  ስለዚህ ቤተክርስቲያን  በንግግር ችሎታቸው ላቅ ያሉና  ተከራክረው ሌላውን መቋቋም የሚችል  ፣ የሚናገሩትንም ነገር የሚያውዉና ፣ የራሳቸውንም አሳብ ከጥቃት የመመከት ብቃት ያላቸውን  ሰዎችን በፖለቲካው ማሰለፍ ከቻለች ውጤታ ትሆናለች እላለሁ፡፡ ያለዚያ ግን በፖለቲካው እንድትሳተፍ ባንመክራት ይሻላል፡፡  
·         ቆራጥነት፡
ለሰዎች ልጆች መብት ተከራክረው ውጤት ያሰመዘገቡ ቆራጥ አቋም ያላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ የሚኖሩት ከራሳቸው ሳይሆን ለሰው ስለሆነ ሞታቸውንም ስለ ሰው ነጻነት ሲሉ ሞተዋል፣፣ በየአሥር ቤቶቹ ተንገላተዋል፡፡ በፖለቲካ መሳተፍ የሚፈልግ ሰው ሁሉ ቆራጥ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ የሚያስከፍለው ዋጋ መኖሩን ማወቅና ዋጋውንም ለመክፈል መዘጋጀት ይኖርበታል ፡፡ እነ ማርቲን ሉተር ኪንግ ያደረጉት ይህንን ነው፡፡  ለወንጌላዊ ያሬድ ጣላሁን ትልቅ አክብሮት አለኝ፡፡ ለኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ቀጥታ ደብዳቤ ጽፎ በማህበራዊ መገናኛ ለጥፏልና፣ ወንጌላዊ ያሬድ በጽሑፍ ካስተላለፈው መልእክት በተጨማሪ በሕዝብ ፊት ቀርበው ንግግር አድርጓል፡፡ በጣም ጠንካራ አሳቦችን ተናገሯል፡፡ በሕዝቦች መካከል የተፈጠረውን ጥላቻ  በማውገዝ በመናገሩ አደንቀዋለሁ፡፡ ጨለማ ጨለማን ስለሚወልድ  መንግሥት በሕዝብ ገንዘብ በተገዛው መሣሪያ ሕዝብን መልሶ መግደልን እንዲተው፣ ጦር ሠራዊቱ የጠመንጃ አፈሙዙን እንዲያዘቀዝቅ  መንግሥት መማጸኑ በጀ የሚያስብለው ነው፡፡ ድፍረትና የአገር ፍቅር የተሞላበት ንግግር ነው፡፡ “ይህንን ተማጽኖ በኢትዮጵያ ላይ ሰላም ሰፍኖ በፖለቲካ ኃይሎች መካከል ገንቢ የሆነ ድርድር ተደርጎ የሁሉም ሕዝብ ድምጽ ተሰምቶ በሰዎች መካከል እኩልነት ተከብሮ እስከማይ ድረስ ይህንን ጩኼቴን አላቆምም፡፡” በማለት ቃል ገባ፣ ጉባኤተኛውም አጨበጨበለት፡፡ እኔም ስሰማው እንደ አገራችን አባባል በልቤ “ አንበሳ” አልኩት፣ አሁን ቆራጥ የቤተ ክርስቲያናችን ልጅ ተገኘ አልኩ፡፡ በተለይም የአገራችን ሕዝቦች መታሰር፣ መገረፍ፣ አገር ጥሎ መሰደደድ ብቻ ሳይሆን በአገር ውስጥ ያለው ወጣት እየደረሰበት ያለው የህልና ስብራት ከፍተኛ መሆኑን መናገሩ ያስመሰግነዋል፣ የአገርና የሕዝብ ተቆርቋርነቱን ያሳያል፡፡በዚሁ ቢቀጥልበት መልካም ነው ብዬ ተመኘሁለት፡፡  ይህንን ስል ከልቤ ነው፡፡ ወንጌላዊ ያሬድ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ በጻፉት ደብዳቤ ምክንያት ሰው ሁሉ ሰግቶ የት እንዳለ ስልክ እየደወሉ እንደጠየቁት ይናገር ነበር፡፡ ግን እኮ ከወንጌላዊ ያሬድ በፊት ወንጌላዊ ጸጋአብ በቀለ ብስለት የተሞላውን ደብዳቤ ጽፏል፡፡ ታዲያ  እነ ወንጌላዊ ያሬድ ጥላሁን ምን ዋጣቸው? እንደዚያ ግዳይ እንደጣለ ሰው በጣም ሲንጎማለሉ የነበሩ ምንነው ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በኃዋላ የውሃ ሽታ ሆኑ? የሆነ ሕዝባዊ ሰልፍ እየተጠበቁ ነው ማለት ነው? ትግሌን እቀጥላሁ አልተውም ሲሉ የነበሩ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሲታወጅ ሕዝቡ ወደ ቤቱ ሲገባ እነርሱም አብረው ቤታቸው ገቡ፡፡ ከመጀመሪያውም ቢሆን የሕዝብ እንቅስቃሴ አይተው አለሁ ለማለት ያደረጉት እንጂ እውነተኛ አቋም ኖሮአቸው ፣ በራሳቸውም ተነሳስተው የሕዝብ ጉዳት ከንክኖአቸው አይደለም እንዳያስብላቸው ፈራሁላቸው፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከታወጀ በኋላስ ቢሆን ሰዎች አላታሠሩም? የመንግሥት ተቃዋሚዎች እስከዛሬ ዝም አላሉም፡፡ የወንጌል ሰባኪዎች ነን ያሉ ግን ለሕዝብ እታገላለሁ፣ ትግሌንና ተቃውሞዬን አልተውም ብለው በዓለም መድረክ ተናግረው ከዚያ ወዳጅ ያፈሩ ወንጌላውያኖቻችን አፋቸውን ዘጉ፡፡ ለነገሩ ወንጌላው ያሬድ መልእክቱን ከመጻፉ ቀደም ብሎ ወንጌላዊ ጸጋአብ በቀለ ጠንካራ መልእክት ጽፏል የሚራግብለትን አላገኘም አንዲ፡፡ ታዲያ ጸጋአብ እስከ አሁን ማን ነካው? ነገሮችን ካካበድናቸው ሳናውቅ የራሳችን አድናቂዎች እንሆናለን፡፡   እኔ እንዲያው ሳየው  ወንጌላዊ ያሬድ ሁለት ችግሮች ተስተውሎበታል፡፡ አንደኛ ምንም የመንግሥት አካል በሌለበት ተቃዋሚዎች ብቻ በተሰበሰቡበት፣ ለንግግሩ ምላሽ የሚሰጠውና ሰምተውም የለውጥ ርምጃ የሚወስድ በሌለበት ፣ በእያንዳንዱ ዐረፍተ ነገር መካካል የሚያጨበጭብ ጉባኤ ፊት ብቻ ነው የተናገረው፡፡ ይህ ብቻ ቆራጥነትን አያሳይም፡፡ በእርግጥ ንግግሩ ጭብጨባ ያንሰዋል የሚያስብል ነው፡፡ በቤተ ክርሰቲያን ያለው ሕዝብ በገባውም ባልገባውም እንዲያጨበጭብ አጨብጭቡ እንጂ አያልን ሕዝባችንን እንዲያው አጭብጫቢ አድርገነዋል፣ ያንን ይዘን ደግሞ ወደ ሌሎች አደባባይ እየሄድን ነው፡፡ አጨብጫቢዎች ሲከተሉአቸው ደስ የሚላቸው መሪዎች ለስህተት የተጋለጡ ናቸው፡፡ ወንጌላዊ ያሬድም ለሚያጨበጭቡ ብቻ ከመናገር እልፍ እንዲል ይጠበቅበታል፡፡ ማርቲን ሉተር ኪንግ  ለውጥ ያመጡት ፍትህ ተጓደለ ወደተባለው ሥፍራ ሁሉ በመንቀሳቀስ በአደባባይ  የመንግሥት አመራር አካላትን ወታደሮቻቸውን ጭምሮ ከ25000 በላይ ሕዝብ በአንድ መቀመጥ የሚያደምጡትን  ንግግር በማድረግ ነው፡፡  በአጭብጫቢው ፊት በተዘጋ ቤት ውስጥ ብቻ ተናግሮ ቢሆን ኖሮ ተደብቆ ድንጋይ የመወርወር፣ በጨለማም የማፍጠጥ ያህል ብቻ ሆኖ በቀረበት ነበር፡፡ ወንጌላዊ ያሬድም  እልፍ ማለት ይገባዋል ባይ ነኝ፡፡ ሁሉም እኮ በየቦታው እንደዚያ ይናገራል፡፡ ለምሳሌ ወንጌላዊ ዳንኤል ጣሰውም እኮ በአንድ ቦታ ንግግር አድርጓል፣ እርሱም ያራገበለት የለም እንጂ፡፡ እርሱ እንዲያውም ሕዝብ ለሰላማዊ ሰልፍ ከመውጣቱ በፊት ነው ይናገር የነበረው፡፡   ወንጌላዊ ያሬድ  እንደ መካለለኛ nutral ሰው ሳይሆን እንደ ፓለቲካኛና እንደ መንግሥት ተቃዋሚ ሰው ነው የተናገረው፡፡ ይህ ደግሞ ከአንድ ወገን ብቻ እንዲደመጥ ያደርገዋል፡፡ ያንን ንግግር ለተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችና አንድ ጥግ ለያዙ ሰዎች ብቻ ሳይሆን ለመንግስትም መናገር ነበረበት፡፡ መንግሥት ይህን ሰምቶ የለውጥ ርምጃ ወሰደ አልወሰደ መንግሥትን ማሰማት ይገባል፡፡ ሁለተኛ የእግዚአብሔርን ቃል ያለቦታው መጥቀሱ አግባብ አይደለም፡፡ ይህ ቤተ ክርስቲያን ሰባኪዎቿ  አጥብቃ የሚታሳስበውና የምትወተውተው ግን ሊታረም ያልቻለ ድክመታችን ነው፡፡ ቃሉን ከሚገጥመው አሳብ ጋር ካላዘመድነው አድማጩን እናሳስተዋለን፡፡ የእግዚአብሔር ቃል  አማኞች የአንድ አካል ብልቶች፣ ቤተ ክርሰቲያንም የክርሰቶስ የአካል ብልት እንደሆነች ይናገራል፡፡ ይህን ትምህርት ግን አገርና የአገር ሕዝቦች የአንድ አካል እንደሆኑ ለማስተማር መጠቀም ቃሉን እየቦጨቁ ያለቦታው መደረት ይሆናል፡፡ የሕዝቦች አንድነት ለማሳየትና ለመስበክ ከተፈለገ ሌላ ክፍል መምረጥ ይቻል የለምን? “ባሪያ በነገሠ ጊዜ ሰነፍም እንጀራን በጠገበ ጊዜ የተጠላች ገጊዜ ምድር ትናወጣለች” /መጽሐፈ ምሳ 30፡21-22/ የሚለውን የጠቢቡ ሰለሞንን ምሳሌ የጠቀሙ ራሱ በጣም ወጣ ያለ ነው፡፡ እነዚህን መጠቀማቸውን ስናይ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ያለ ቦታቸው የተለጠፉ ናቸውና ይታሰብበት ለማለት ነው፡፡
ለወደፊትም ቢሆን ለብዙ ዘመናት በአገልጋይነት ቆይቻለሁ፣ ሰባኪ፣ ወንጌላዊ ቄስ ወዘተ ነኝ እያልን ፖለቲካውን ደግሞ መነካካት ስንጀምር ቀጣዩንም ውስብስብ መንገድ ለመጓዝ ቆራጥነትን እንደሚስፈልግ ስለማሰቡ የእኔ ምክር ከሚያስፈልጋቸው ልክ በላይ የላቁ አገልጋዮች ስላሉን በዚሁ ላቁምና አሳቤን ልቋጭ፡፡ የገብሷን እሸት ከመብላት በፊት በደንብ ማሸት፣ ያለዚያ ሳሉ አያስተኛምና እንዲሉ በአንድ ነገር ውስጥ ከመግባት በፊት ማሰብ ፣ የሚያስከፍለውንም ዋጋ መተመን የሚያሻ ይመስለኛል፡፡  ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካ ትሳተፍ ስንል ብቅ ብለው ጥፍት የሚሉ ፣ ነገር ሲሞቅ የሚግሉ፣ ገና ሊበርድ ሲል ደግሞ ቀድመው ወደበረዶነት የሚቀየሩ ሳይሆን በእርግጥ ዋጋ ከፍዬ ለሕዝቤና ለምድሬ ለውጥ አመጣለሁ የሚሉ የቁርጥ ቀን ልጆች ሊኖሩአት እንደሚያስፈልግ እናስምርበት፡፡