Thursday, February 23, 2017

     በአገልግሎታችን ቅዱሳንን እንዴት መጥቀም እንደሚገባን ( 2017-35)
                                                                                                   

                                                                                           ከመጋቢ ሳሙኤል ሾንጋ

እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር 1993 ዓ.ም. በደቡብ ሱዳን ከፍተኛ ድርቅ በመከሰቱ ምክንያት የበርካታ እንስሳትና የሰው ሕይወት ጠፍቶ ነበር፡፡ በጊዜው የተከሰተው ተፈጥሮአዊ አደጋ በጣም አስከፊ በመሆኑ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት/United Nations  በጉዳት ላይ ለነበረው ሕዝብ ሰብአዊ ርዳታ እንዲሰጡ የተለያዩ ዘርፍ ባለሙያ ሰዎችን ወደ ደቡብ ሱዳን መላኩ ይታወሳል፡፡ በጊዜው የህክምና ባለሙያዎች፣ የሰብአዊ ርዳታ ሰጪ አካላት ወዘተ  መድኃኒት፣ ምግብና ሌሎች አሰፈላጊ  ቁሳቁሶችን ይዘው ወደ ቦታው ተንቀሳቅሰዋል፡፡ በወቅቱ ከተንቀሳቀሱት ውስጥ ዓለም አቀፍ ጋዘጤኞችም የነበሩበት ሲሆን ታዋቂ ፎቶጆርናሊስት ደቡብ አፍሪካዊው ኬቪን ካርቴር ይገኝበታል፡፡ ኬቪን ከልዑካን ቡድኑ ጋር ወደ ደቡብ ሱዳን ከደረሰ በኋላ በካሜራው ያነሳቸው ፎቶግራፎች በጣም ተደናቂነትን ያኙና በሥፍራው ስለነበረው የድርቅ ሁኔታ በጣም በኃይለኛው ሁኔታ የሚገልጹ ነበሩ፡፡ ለምሳሌ ልጆች ውሃ ከማጣታቸው የተነሳ ላሞች ሽንት ሲሸኑ ከስር ቀርበው ሲጠጡ፣ ወይም ጭንቅላታቸውን አስጠግተው ሲታጠቡ ኬቪን በካሜራው አንስቷል፡፡ ከሁሉም ፎቶዎቹ ይልቅ ግን በወቅቱ ሁሉንም ያስደነቀችና የኬቪንንም ዝና እጅግ ያወጣችው ፎቶ ሌላ ነበረች፡፡ አንዲት በረሀብ በጣም ከመጎዳቷ የተነሳ ሰውነቷን መሸከም ያቃታት፣ በአካላቷ  ላይ ምንም ሥጋ የሌላት ፣ ቆዳዋና አጥንቷ የተጣበቀ የሚመስል ሕጻን ልጅ በአንድ በረሀማ በሚመስል ቦታ  ፣ በሰውነቷ ላይ ምንም ልብስ ሳይኖር ራቁቷን ሆና ጭንቅላቷን በሁለት እግሮቿ መካከል አድርጋ በግምባሯ ተደፍታ ፣  በአጠገቧ ምንም ሰው ሳይኖር ነገር ግን ከኋላ አንድ የፈረጠመ ጆፌ አሞራ ተንሰፍስፎ ሲጠብቃት ሳለ ኬቪን በካሜራው አነሳና ለዓለም ሕዝብ አሳየ፡፡ ያ ፎቶግራፍ በደቡብ ሱዳን የነበረው ድርቅ አስከፍነቱ ምን ያህል ጥልቅ እንደሆነ የሚያስረዳ በመሆኑ በጊዜው የዓመቱ ምርጥ ፎቶ ተብሎ ተመረጠ፡፡ በዩናይትድ ስቴት ኦፍ አሜሪካ ያለው በሥነ ጽሑፍ፣ በጋዜጠኝነት፣ በሙዚቃ ድርሰት የላቀ አስተዋጽኦ ላበረቱት ሽልማት የሚሰጠው Pultizer price የተሰኘው ድርጅት የሚሰጠውን ሽልማት ያሸነፈ አስደናቂ ፎቶ ሆኖ ተመረጠ፡፡ ከዚያ በኋላ የኬቪን ዝና እጅግ ወጣ፣ በዓለም ዙሪያ ሁሉ ገናናና እና ታዋቂ ሆነ፡፡ የኬቪን ፎቶ የፓልትዘርን ሽልማት ስላሸነፈ የሽልማት ስነሥርዓት በተባበሩት መንግሥታት ዋና ጽሕፈት ቤት ተዘጋጀለት፡፡ ከተለያዩ የሙያ ባለሙያዎች፣ የኪነ ጥበብ ሰዎች፣ ከጋዘጠኞችና የፊልም ባለሙያዎች የእንኳን ደስ ያለህ መልእክት ከየአቅጣጫው ጎረፈለት፡፡ የሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ወቅት በታዳሚዎች ፊት  በሙያውም ስኬታማ ሊሆን የቻለው እንዴት እንደሆነ ከጋዘጠኞች ለሚቀርብለት ጥያቄ መልስ እየሰጠና በደቡብ ሱዳን በረሀ ላይ ያቺን ሕጻን እንዴት በካሜራው እንዳገኛት ስለብልሃቱና ስለጥበቡ  እያብራራ ከሁሉም ሰው አድናቆትን  እያኘ ሳለ ከጉባኤ በስተ መጨረሻ በኩል አንድ ሰው አንድ ወሳኝ ጥያቄ አቀረበለት፡፡ ጥያቄውም እንዲህ የሚል ነበረ፡፡ “የልጅቷ መጨረሻ ምን ሆነ?”  በዚህን ጊዜ ኬቪን ደነገጠ፡፡ አንደበቱ ተሳሰረ፡፡ በዓይነ  ሂሊናው ወደ ደቡብ ሱዳን በረሀ ጭልጥ ብሎ ሄደ፡፡ ሰውነቱ ይንቀጠቀጥ ጀመር፡፡ ልጅቷ ምን ሆነች ለሚለው ጥያቄ በሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኘውን ሕዝብ አስተሳሰብ በአንዴ ቀየረው፡፡ ጉባኤተኛው ሕዝብ ኬቪን ለዚህ ጥያቄ ምን መልስ ይሰጥ ይሆን ብሎ በጉጉት እየጠበቁ ሳለ  እርሱ ምንም ሳይመለስ ያን ጥያቄ ያቀረበው ሰው ሌላ ጥያቄ በከፍተኛ  ጩኼት “ ልጅቷን አዳንካት ወይ “ በሚል አስከተለበት፡፡ ኬቪን ልቡ ይመታ ጀመር፡፡ ራሱን በዚያ ሥፍራ ማቆየት ስላልቻለ ከወንበሩ ተነስቶ ወደ ውጭ ወጣ፡፡ በዚያው ወደ አዳራሹ ሳይመለስ ወደ ትውልድ አገሩ ወደ ደቡብ አፍሪካ አቀና፡፡ ቢሆንም ከህልናው ክስ መሸሽ ስላልቻለና ስለተሰቃየ በተወለደ በ33 ዓመቱ አንድ ወረቀት ጽፎ አጠገቡ አስቀመጠና ራሱን ሰቅሎ ሞተ፡፡
ኬቪን ወደ ደቡብ ሱዳን የተላከበት ዋንኛ ምክንያት ለራሱ ዝና እንዲሠራ አልነበረም፣ የሌሎችን ሕይወት ለማዳን እንጂ፡፡ እንደዚያች ላሉ ሕጻናትና ለሌሎች በድርቁ ለተጎዱት ሰዎች የነፍስ አድን ርዳታ እንዲያደርስላቸው ነበር፡፡ ነገር ግን የዚያች ልጅ ሕይወት እየመጣባት ካለው አሞራ ማዳን ሲችል ተልዕኮውን ወደ ጎን በመተው የራሱን ዝና ለማውጣት የሚችለውን ሥራ ብቻ ሥርቶ ልጅቷን በዚያ በረሀ ለአሞራ ተዋት፡፡ ሌሎችን ለመጥቀም የተሰጠውን ተልዕኮ ዘንግቶ ራሱን መጥቀም ፣ በሰዎች ጉዳት እርሱ የመክበርን መንገድ ተከተለ፡፡ በመጨረሻም በጣም ወሳኝ ወቅት ላይ ልጅቷን አዳንካት ወይ የሚል የቀረበለት ጥያቄ ያንን ክብርና ዝናውን ሁሉ አበላሸበት፡፡
ይህ በእግዚአብሔር ቤት ቅዱሳንን ለመጥቀም ከጌታ የአገልግሎትን አደራ ለተቀበልን ሁሉ ማንቂያ ደወል ሊሆን የሚችል ምሳሌያዊ አሳብ ነው፡፡ እኛ የተጠራነውና አገልግሎትን የተቀበልነው ሌሎችን ለመጥቀም ነው፡፡ አገልግሎት የሚለው አሳብ ራሱ ሌላውን ማገዝ፣ መጥቀም፣ መርዳት ወይም ለሌሎች ጥቅም መኖር ማለት ነው፡፡ ይሁን አንጂ በአሁኑ ጊዜ አገልግሎትና አገልጋይ ማለት የተሳሳተ ሥፍራ ላይ እየዋለ ይገኛል፡፡ ከቅርበ ጊዜ ወዲህ በቤተ ክርስቲያን አገልጋይ መሆን ሌሎችን የመጥቀም ጉዳይ መሆኑ ቀርቶ  በሰዎች መጠቀም፣ የተገኘውን ዕድል ሁሉ ለራስ መውሰድ( taking an Advantage to own self ) መሆን እየመሰለ መጣ፡፡ ሰዎችን አዋርደን እኛ ክብር ማግኘት፣ ሰዎችን ዝቅ አድርገናቸው ወይም ጎድተናቸው እኛ ዝናን ማግኘት፣ ድፍረት በባይሆነኝም የሰዎችን ኪስ አራቁተን እኛ ማለትም አገልጋዮች የሆንንው እኛ ብቻ  መበልጸግን ልማድ እያደረግን እንገኛለን፡፡ እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያንና ለአገልጋዮች የሰጠን ተልእኮ ወደ ጎን የተተወ ይመስለኛል፡፡ ልክ የፎቶግራፍ ጋዜጠኛው ኬቪን የተባበሩት መንግሥታት የሰጡት ተልእኮ የተጎዳውን ሕዝብ እንዲያድን ሆኖ ሳለ እርሱ ግን ያንን ሰውን የማዳን ሥራ ወደ ጎን ትቶ የተራቡ ሕጻናትን ለአሞራ ሰጥቶ ለራሱ ክብር ዝና፣ ገንዘብ ሽልማት፣ ታዋቂነትን የሚያተርፍበትን መንገድ እንደተከተለ ሁሉ ዛሬ እኛም አገልግሎታችንን ለሌሎች ጥቅም መስጠት ትተን ለራሳችን ክብርና ዝና የምንኖር እንዳይሆን መጠንቀቅ እንዳለብን የሚያሳስበንን መልእክት ሐዋሪያው ጳውሎስ ከኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ከተናገረው አሳብ እንመለከታለን፡፡
ሐዋሪያው ጳውሎስ በመልእክቱ መግቢያ ላይ እንዲህ ይላል፡፡
ከሚሊጢንም ወደ ኤፌሶን ልኮ የቤተክርስቲያንን ሽማግሌዎች አስጠራቸው፤ ወደ እርሱም በመጡ ጊዜ እንዲህ አላቸው፦ ወደ እስያ ከገባሁበት ከመጀመሪያ ቀን ጀምሮ፥ በትሕትና ሁሉና በእንባ ከአይሁድም ሴራ በደረሰብኝ ፈተና ለጌታ እየተገዛሁ ዘመኑን ሁሉ ከእናንተ ጋር እንዴት እንደ ኖርሁ እናንተው ታውቃላችሁ፤ ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ንስሐንና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች እየመሰከርሁ በጉባኤም በየቤታችሁም አወራሁላችሁና አስተማርኋችሁ እንጂ፥ ከሚጠቅማችሁ ነገር አንዳች ስንኳ አላስቀረሁባችሁም።
ጳውሎስ ሌሎችን የመጥቀሙን አገልግሎት በኤፌሶን ላሉት አማኞች በትክክል አስመስከሯል፡፡ እንዲያውም እርሱ በዚያ ሲያገለግል ሁለት ዓይነት ሰዎች እንደነበሩ ከክፍሉ አጠቃላይ አሳብ እንረዳለን፡፡ አንደኛዎቹ የሐሰት ትምህርት አስተማሪዎች ናቸው፡፡ ጳውሎስ ስለ እነርሱ ሲገልጽ ከተኩላ ጋር ይመስላቸዋል፡፡ ከአውሬዎች ጋር ይመስላቸዋል፡፡ ነጣቂዎች ናቸው ይላቸዋል፡፡ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች ይላቸዋል፡፡ ደቀመዛሙርትን ወደ ኋላ  የሚስቡ፣ ጠማማ ነገርን የሚናገሩ እንደሆኑ ያሳስባል( ቁ 29-30)፡፡ አገልጋዮች ናቸው፣ የወንጌል አገልጋዮች፣ ሰባኪዎች ናቸው ግን በመንጋው ላይ የሚጨክኑ ፣ የአውሬነትና የተኩላነት ልብ ያላቸው፣ የሚነጥቁና የሚያጣምሙ መሆናቸው በጣም የሚያስገርም ነው፡፡ አንድ ሰው ወደ አገልግሎት ሲገባ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ልጥቀም ብሎ ካልሆነ የራሱን የሚመግብ ጨካኝና ነጣቂ ነው የሚሆነው፡፡ ያ ደግሞ መጥፎ መርገም ነው፡፡ ልክ ኬቪን ልጅቷ አዳንካት ወይ የሚል ጥያቄ ሲቀርብለት ግራ እንደተጋባና ራሱን ከሥፍራው እንዳገለለ ሁሉ አገልጋዮች አንድ ቀን መጠየቃችን አይቀርም፡፡
ሁለተኛው ጳውሎስ ራሱ ሲሆን የኖረው ለአማኞች ጥቅም ሲል እንደሆነ ይናገራል፡፡ በእስያ  ለሦስት ዓመታት ኖሯል፡፡ በዚያን ጊዜ ጢራኖስ በሚባል የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ቤት እያስተማረ ለሁለት ዓመታት መኖሩን በሐዋሪያት ሥራ ምዕራፍ 20 ላይ እናገኛለን፡፡ ከዚያም በላይ ዘመናትን ኖሮ ሊሆን ይችላል ግን በኖረባቸው ጊዜያቶች ሁሉ ለቅዱሳን የሚጠቅመውን አድርጓል፡፡ ከሽማግሌዎች ጋር ሆኖ የሦስት ዓመት አገልግሎቱን ሲገግምና ሲከልስ የእግዚአብሔርን ሰዎች ከሚጠቅማቸው ነገር አንዱንም እንዳላስቀረ በልበ ሙሉነት ይናገራል፡፡
በዚህ ክፍል ሐዋሪያው ርግጠኛ ሆኖ የሚናገረው ከቤተ ክርሰቲያን ሕዝብ ከሚጠቅማቸው ነገር አንድ እንኳ እንዳላስቀረባቸው ነው፡፡ የሚያደርጋቸውን ሁሉ ነገሮች ያደረገው ለአማኖቹ እንድጠቅማቸው ብሎ ነው፡፡ የእውነተኛ አገልጋይነት ሕይወትም እኮ እ ሌላውን በመጥቀም ነው፡፡ ወንጌላችን ራሱ ሌሎችን መጥቀም ነው፡፡ ጳውሎስ በሌላም ሥፍራ ሰዎችን ለመጥቀም ራሱን እንደሰጠ ሲናር እንዲህ አለ፡፡
ከሰው ሁሉ አርነት የወጣሁ ስሆን የሚበልጡትን እንድጠቅም እንደ ባሪያ ራሴን ለሁሉ አስገዛለሁ። አይሁድንእጠቅም ዘንድ ከአይሁድ ጋር እንደ አይሁዳዊ ሆንሁ፤ ከሕግ በታች ያሉትን እጠቅም ዘንድ፥ እኔ ራሴ ከሕግ በታች ሳልሆን፥ ከሕግ በታች ላሉት ከሕግ በታች እንዳለሁ ሆንሁ፤ ሕግ የሌላቸውን እጠቅም ዘንድ፥ ያለ እግዚአብሔር ህግ ሳልኖር ነገር ግን በክርስቶስ ሕግ በታች ሳለሁ፥ ሕግ ለሌላቸው ሕግ እንደ ሌለኝ ሆንሁ፤ ደካሞችን እጠቅም ዘንድ ለደካሞች እንደ ደካማ ሆንሁ፤ በሁሉ መንገድ አንዳንዶችን አድን ዘንድ፥ ከሁሉ ጋር በሁሉ ነገር እንደ እነርሱ ሆንሁ(1 ቆሮ 9፡19-22)።
ጳውሎስ ለተለያዩ ሰዎች ወንጌልን ሰብኮ እነርሱ ደህነነትን የሚያገኙበት መንገድ ሲናገር እነርሱን መጥቀም ይለዋል፡፡ በሌላም ሥፍራ ለፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን አማኞች ስናገር በምድር መኖሩ ራሱ ለራሱ ጥቅም ሳይሆን ለአማኞች ጥቅም እንደሆነ ይናገራል፡፡ ለእርሱ ወደ ክርስቶስ መሄድ እጅግ የተሻለና የበለጠ ነገር እንደሆነ ቢያምንም በሥጋ ከእነርሱ ጋር መኖር ግን ከእርሱ ይልቅ ለእነርሱ/ ለአማኞቹ/ ጥቅም እንደሆነ ያስረዳል፡፡ እንዲህም ሲል፡
ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ፥ ሞትም ጥቅም ነውና። ነገር ግን በስጋ መኖር ለእኔ የሥራ ፍሬ ቢሆን፥ ምን እንድመርጥ ኣላስታውቅም። በእነዚህም በሁለቱ እጨነቃለሁ፤ ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፥ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና፤ ነገር ግን በሥጋ መኖሬ ስለ እናንተ እጅግ የሚያስፈልግ ነው( ፊልጵስዩስ 1፡19-23)።
እኛስ ዛሬ ራሳችንን ስንፈትሽ  እግዚአብሔር በሰጠን ዘመን ባገለገልንባቸው ሥፍራዎች ሁሉ የእግዚአብሔርን ሕዝብ የሚጠቅም አገልግሎት እንደሰጠን እርግጠኞች ነንን? ለእግዚአብሔር ሕዝብ የምንጠቅም አገልጋዮች እንድንሆን እግዚአብሔር ይፈልጋል፡፡ በእውነት በዚህ ዘመን እግዚአብሔር ይርዳን፡፡ ሐዋሪያው ጳውሎስ ለኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ካስተማረው ትምህርት በአገልገሎታችን እንዴት ቅዱሳንን መጥቀም እንደምንችል አራት መሠረታዊ ነጥቦችን እንመለከታለን፡፡ በአገልግሎታችን ሌሎችን መጥቀም የምንችለው እንዴት ነው?
1.    ለአገልጋይነት የሚገባ ባሕሪይ /An aproprate character/ ሲኖረን ነው፡፡

ወደ እስያ ከገባሁበት ከመጀመሪያ ቀን ጀምሮ፥ በትሕትና ሁሉና በእንባ ከአይሁድም ሴራ በደረሰብኝ ፈተና ለጌታ እየተገዛሁ ዘመኑን ሁሉ ከእናንተ ጋር እንዴት እንደ ኖርሁ እናንተው ታውቃላችሁ፤ ጳውሎስ በዚህ ሥፍራ ወደ ሌሎች አሳቦች ሁሉ ከመግባቱ በፊት ስለ ራሱ የአገልጋይነት ባሕሪይ አጠንክሮ ይናገራል፡፡ በአማኞች መካከል በተመላለሰባቸው ጊዜያቶች ሁሉ 3 ዋና ዋና የአገልጋይ ባሕሪያትን ማሳየቱን በልበ ሙሉነት ይገልጻል፡፡ 1. ትሁት ነው፡፡ 2. የእምባ ሰው ነው፡፡ 3. ለጌታ የተገዛ ሰው ነው፡፡ ትህትና የሌለው ሰው በእግዚአብሔር አገልግሎት ቢሰማራም ቅዱሳንን ሊጠቅም አይችልም፡፡ እንዲያውም የእርሱ አገልጋይነት ለቤተ ክርስቲያን ሸክምና ፈተና ነው፡፡ ትህትና የትዕቢት ተቃራኒ ሲሆን በምድር ላይ እጅግ አስቸጋሪ ኃጢአት ቢኖር ትዕቢት ነው፡፡ ትዕቢተኛ ሰው መንፈሳዊ ፍሬ ሊያፈራ አይችልም፡፡ ቅዱሳንን ይጎዳል፣ አገልግሎትንም ያበላሻል፡፡  ትሁታን ባሉበት ግን ፍሬ አለ፣ ነጻነት አለ፣ ሰላምም አለ፣ ሁም በደስታ ጌታን ያልካል ያገለግላልም፡፡ ጳውሎስ በዚህ ሕይወቱ የተመላለሰ አገልጋይ ነበር፡፡ እርሱ ትሁት ብቻ ሳይሆን የእምባ ሰው ነው፡፡ ስለ አማኞች በእግዚአብሕር ፊት የሚያነባ ሰው ነው፡፡ አማኞችን ሲያስተምራቸውና ሲገስጻቸውም ሁሉ በእምባ ነበር (ስለዚህ ሦስት ዓመት ሌሊትና ቀን በእንባ እያንዳንዳችሁን ከመገሠጽ እንዳላቋረጥሁ እያሰባችሁ ትጉ ቁ 31)፡፡ የምናገለግለው አገልግሎት ከእውቀት ፣ ከትምህርት፣ ከልምድ ሁሉ በላይ እምባን የሚጠይቅ ነው፡፡ ከዚህም ጋር ጨምሮ በዘመኑ ሁሉ ለጌታ የተገዛ ሰው መሆን ይገባል፡፡ ጳውሎስ ከአይሁዶች ሴራና ዛቻ ቢደርስበትም እንኳ በሕይወቱ አንድም ቀን የትዕቢት ነገር አልታየበትም፡፡ይልቁንም ከእምባ ጋር ለጌታ እየተገዛ ዘመመኑን ሊኖር የቻለ ሰው ነው፡፡ የጌታ ባሪያ ጳውሎስ እነዚህ ሦስት ዋና ዋና መልካም ባሕሪያት የታየበት ድንቅ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነው፡፡
በዛሬዋ ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ ግምት የሚሰጠው አንድ ሰው የአገልግሎት ስጦታ መኖሩን ብቻ ነው፡፡ ሰባኪ፣ ዘማሪ፣ የፈውስ አገልጋይ፣ ተአምራት የሚያደርግ መሆኑን ብቻ ነው፡፡ እኛም አገልጋዮች የሆንነው የምናተኩረው በዚያ ላይ ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የሚባርከን በእኛ አገልግሎትም ሌሎችን የሚባርካቸው ባለን መንፈሳዊ ሕይወት ለውጥና ባሕሪይ(Charactor) መሰረት ነው፡፡ ይህ በጣም መሠረታዊ ነገር ነው፡፡  ጳውሎስ በምዕመናን መካካል ሲመላለስ እነዚህን ቁልፍ ባሕሪያትና ያሳየው ለአንድ ጊዜ ቆይታ ብቻ ወይም የሆነ ነገር ሲፈልግ ፣ ወይም አንድ ነገር እንዲሆንለት ሰዎችን ሊያማልል ያደረገው የግብዝነት ነገር አልነበረም፡፡ ነገር ግን የሁል ጊዜ የሕይወቱ ተሞክሮ እንደሆነ ሲገልጽ ወደ እስያ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ እነዚህ ባሕሪያት የታዩበት እንደነበረ ይናገራል፡፡ ስለዚህ በአጥቢያ ቤተ ክርስቲያንም ሆነ በሌሎች የአገልግሎት  ክፍሎች ተሰማርተን ስናገለገል በእውነት ሌሎችን እንጥቀማቸው ካልን ወደ መሠረቱ መመለስ ይኖርባናል፡፡ ያውም ከተሰጡን የጸጋ ሥጦታዎች በላይ በእግዚአብሔርና በሕዝቡፊት ያለን የሕይወት ለውጥ ምን እንደምመስል መገምገምና መረዳት ያስፈልገናል፡፡

2.   አገልግሎታችን ሥልታዊነት Strategy ያለው ሲሆን ነው፡፡

 የምንሰጠውን አገልግሎት የትና እንዴት እንደምንሰጥ በትክክል ማወቅ ቅዱሳንን ለመርዳት የሚያግዘን አንዱ መንገድ ነው፡፡ ሐዋሪያው የአገልግሎቱ ሽፋን( a ministerial scope) ለማን፣ ለምንና   እንደሆና ከየት እስከ የትም መሆን እንዳለበት የተረዳ ሰው መሆኑን በዚህ ክፍል ያሳየናል፡፡ (ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ንስሐንና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች እየመሰከርሁ በጉባኤም በየቤታችሁም አወራሁላችሁና አስተማርኋችሁ፣ቁ.20-21)፡፡ ጳውሎስ በዚህ አሳቡ ማንን እንደሚጠቅም ያውቅ ነበር፣ የት እንደሚጠቅማቸውም ያውቅ ነበር፡፡ በእርሱ አገልግሎት የሚጠቀሙት ሰዎች ሁሉ ማለትም አይሁድም አሕዛብም ናቸው፡፡ በዚያ ጊዜ የዓለም ሕዝብ አይሁድና አሕዛብ ተብሎ በሁለት ጎራዎች የተከፈሉ ቢሆንም የጳውሎስ አገልግሎት ግን  ለሁሉም ነበረ፡፡  እርሱ ራሱ ሁሉንም የሚጠቅም አገልጋይ ነበረ፡፡ ሁሉንም ማገልገሉና መጥቀሙ የሕይወቱ መመሪያ ስለነበረ ለፊልጵስዪስ ሰዎች ሲጽፍ ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ወይም በከንቱ ውዳሴ ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ፥ ነገር ግን እያንዳንዱ ባልንጀራው ከራሱ ይልቅ እንዲሻል በትሕትና ይቍጠር፤እያንዳንዱ ለራሱ የሚጠቅመውን አይመልከት፥ ለባልንጀራው ደግሞ እንጂ(ፊልጵ 2፡4) በማለት ጠንካራ መመሪያ ሰጥቶ አለፈ፡፡  የጳውሎስ ሥረ- መሠረቱ አይሁዳዊ ቢሆንም እርሱ ግን አህዛብ የሆኑ ግሪኮችንም ይጠቅማቸው ነበር፡፡ ደካሞችን ይጠቅማቸው ነበር፡፡ የተጠቁትን፣ የተጣሉትን፣ የተገለሉትን፣ አምላክ የላቸውም የተባሉትን፣ አገርም የሌላቸው የተባሉትን፣ ያልተገረዙ የተባሉትን ሁሉ ለመጥቀም ያገለግል ነበረ፡፡ በጳውሎስ አገልግሎት ውስጥ ልዩነት የሚባል ነገር ስላልነበረ እርሱ ለሁሉም የሚጠቅም አገልጋይ ሆነ፡፡
ጳውሎስ  የአገልግሎቱን ተደራሲያን ብቻ ሳይሆን የት ማገልገል እንዳለበትም የተረዳ ሰው ነበረ፡፡  አገልግሎቱ ጉባኤም በየቤታቸውም  ሁሉ ነበር፡፡ የሐሰት አስተማሪዎች ትልቁ ትኩረታቸው ቤት ለቤት እየዞሩ የቅዱሳንን ቤት መብላት፣ በእምነታቸው ያልበረቱትና አንዳንድ ቅምጥል ሰዎችን ማሳት ነው፡፡ በኢየሱስም ጊዜ የፈሪሳውያን ትልቅ ስህተት ከነበረው አንዱ ቤት ለቤት እየዞሩ የመበለቶችን ቤት መብላት ነው፡፡ በአንጻሩም ደግሞ እውነተኞች አገልጋዮች እውነተኛና ጤናማ የሆነ አገልግሎት ይዘው ወደ የቤቱ ሄደዋል፡፡ ኢየሱስም ወደ የቤቱ ሁሉ ሂዱ ስትሄዱም ሰላም ለዚህ ቤት ይሁን በሉ፣ ያቀረቡላችሁንም ብሉ ያለው አገልጋዮች ወንጌልን ለመስበክም ሆነ አማኞችን በእምነታቸው ለማጽናት የቤት ቤት አገልግሎት በጣም ተፈላጊ ስለነበረ ነው፡፡ አሁንም ይህ ሊተኮርበት ይገባል፡፡ ዛሬ በኢትዮጵያ በአገልጋይነት ስም  ብዙ ሰዎች ቤት ለቤት እየተዘዋወሩ የቅዱሳንን እምነት እየሸረሸሩ እንደሆነ በግልጽ የሚታይነው፡፡ አንዳንዶች ደግሞ ቤት ለቤት አገልግሎትን እያስቀሩ ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ፣ በቤተ ክርስቲያን የሚደረገው የፈውስ አገልሎት መልካም ቢሆንም አስተምሮአዊ መርሆ ግን ሙሉ በሙሉ እየተረሳ ነው፡፡ በያዕብ 1፡16 ላይ ማንም የታመመ ቢኖር የቤተ ክርስቲያንን ሽማግሌዎች ወደ ራሱ ይጥራ እነርሱም በጌታ ስም ዘይት ቀብተው ይጸልዩ ይላል፡፡ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮን ለመጣሷ ይህ ምሳሌ ነው፡፡ ሰዎች በአደባባይ ግሩም ክርስቲያኖች ቢመስሉም እቤታቸው የሚኖሩበት ሕይወት መታየት ይኖርበታል፡፡ በቤታቸው መከራን የሚቀበሉ፣ ሕይወት የተበላሸባቸው፣ የቅዱሳንን ድጋፍና ምክር የሚፈልጉ ሲኖሩ በጉባኤ አገልግሎት ብቻ መፍትሔ ልናስገኝላቸውና ልንጠቅማቸው አንችልም፡፡ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ወደ እነዚያ ሰዎች በማቅናት ባሉበት ሁኔታ ሲገለግሉአቸው ይገባል፡፡ በተለይም የቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ከጌታ የተሰጣቸውን መንፈሳዊ ሥልጣን ከሚገልጹባቸው መንገዶች አንዱ ወደታመሙ ሰዎች ቤት በመሄድ ቃሉን ማስተማር ፣ አስፈላጊውን ምክር በመስጠት ፣በጌታ ስም ዘይት ቀብተው በመፀለይ ድዊውን የመፈወስአገልግሎት ነው፡፡ በቤተክርስቲያን ጉባኤ ላይ የሚደረገው የፈውስ አገልግሎት ለወንጌል ሥርጭት ጠቃሚ ነው፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔር ቃል በግልጽ የሚያስተምረን ግን ማንም የታመመ ቢኖር የቤተ ክርስያንን ሽማግሌዎች ወደ ቤቱ እንዲጠራና አገልግሎቱን እንዲካፈል ነው፡፡ የቤት ለቤት አገልግሎት ቃሉን ለማስተማር፣ መንፈሳዊ ምክርንም ለመስጠት ፣ የቅዱሳንን የእርስ በርስ ህብረት ለማጠናከርና የስተት ትምህርቶች ለመከላከል የሚረዳበመሆኑ በአደባባይ ያለውን አገልግሎት ከማካሄድ ጎን ይህኛውንም ማጠናከር ተገቢ ነው፡፡ ከመድረክ አገልግሎት ይልቅ ቤት ለቤት ተዘዋውሮ ማገልገል በጣም አድካሚ ነው፣ታዋቂም አያስብልም፡፡ ስለዚህ ብዙዎች አይሞክሩትም፣ አይፈልጉትምም፡፡ በተለይም መድረክ ተኮር መጋቢዎች መዕመናን ወደ እነርሱ እንዲመጡ እንጂ ወደ መዕመናን ወርደው በቤታቸው ማገልገል አያስቡትም፡፡ ቅዱሳንን በመንፈሳዊ ሕይወታቸው የሚጠቅም የእረኝነት  ልብ ያላቸው መጋቢያን ግን የኢየሱስንና የጳውሎስን ፈለግ ተከትለው የሚያለግሉአቸውን ምዕመናን በቤትም በጉባኤም ያለግሉአቸዋል፡፡
ከጳውሎስ አገልግሎትየምንማረውሌላው ቁም ነገር የሚያገለግላቸውን ሰዎችና ቦታን ለይቶ ማወቅ ብቻ ሳይሆን እንዴት እንደሚያገለግልም ያውቅ ነበር፡፡ እርሱ በበጉባኤም ሆነ  በቤትም ያደረገው ምንድነው; ሦስቱ የአገልግሎቱ ስልቶች ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ እነርሱም ማስተማር፣ በስበክ( እየመሰከርኩ አወራሁላችሁላችሁ ይላል እርሱ)ቁ 20፣ መገሰጽ( ቁ.31) ናቸው፡፡ ሐዋሪያት ፣ ነቢያት፣ አስተማሪዎች፣ የወንጌል ሰባኪዎችና እረኞች ሽማግሌዎች አሁን በእጃቸው የለውን ሕዝብ ቤቤቱ እየገቡ ቢያስተምሩ፣ ቢሰብኩ፣ በድካማሙም አባታዊና መጋቢያዊ ግሳጼ እየሰጡ ማገልገል ከቻሉ በእውነት ጠቅመዋል ማለት ነው፡፡ በዛሬው ጊዜ ወደ ሰዎች ቤት የሚሄዱ አገልጋዮች አሉ፡፡ መነሳት ያለበት ጥያቄ ግን የሚሄዱት እነማን ናቸው፣ ማንስ ጋ ይሄዳሉ፣ ሄደውስ ምን ያድርጋሉ የሚለው ነው፡፡ ይህ በትክክል መለስ ማግኘት ይኖርበታል፡፡ ወደ ሰዎች ቤት መሄድ ያለባት ቤተክርስቲያን ናት፣ ወይም ደግሞ ቤተክርስቲያን የወከለቻቸው አገልጋዮች በዓላማና በመርሀ ግብር ፣ ያለምንም ልዩነት ወደ እያንዳዱ ምዕመን በመግባት ሕይወታቸውን ማደስ ማስተማር፣ መምከር፣መገሰጽ ይኖርቸዋል፡፡ ካልሆነ ግን ሀሰተኞች ተኩላዎች መንጋውን ይበሉባቸዋል፡፡    
         

3.   አገልግሎታችን ቁም ነገርና ይዘት /substance and content/ ያለው ሲሆን ነው፡፡

ሰዎችን በአገልግሎታችን የምንጠቅመው በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዲጠናከሩ የሚያደርገውን ነገር ሁሉ በመስጠት ነው ፡፡  ጳውሎስ እንዲህ ይላል፡፡ ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ንስሐንና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች እየመሰከርሁ በጉባኤም በየቤታችሁም አወራሁላችሁና አስተማርኋችሁ እንጂ፥ ከሚጠቅማችሁ ነገር አንዳች ስንኳ አላስቀረሁባችሁም(20-21)። አሁንም፥ እነሆ፥ እኔ የእግዚአብሔርን መንግሥት እየሰበክሁ በመካከላችሁ የዞርሁ ሁላችሁ ከእንግዲህ ወዲህ ፊቴን እንዳትዩ አውቃለሁ( ቁ.25)። የእግዚአብሔርን ምክር ሁሉ ነግሬአችኋለሁና፥ ምንም አላስቀረሁባችሁም(ቁ 27)። ጳውሎስ እንደሚነግረን እርሱ ወደየቤቱም በየጉባኤ ምን ያደርግ ነበር  የሚለው ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ወደ ሰዎች ቤት መሄድ ወይም በጉባኤ ፊት መቆም ብቻ ሳይሆን ምን አደረጉ የሚለው ነው መታየት ያለበት፡፡ ጳውሎስ አስተማረ፣አወራላቸው( ሰበከላቸው) ፣ በቁጥር 31 ላይ እንደምንመለከተው ያለማቋረጥ ሌሊትና ቀን ያውም በእምባ ሆኖ ይገስጻቸው ነበር፡፡ ሲሰብክና ሲያስተምርም መንፈሳዊ ቁም ነገር ያለበትን ስብከትና ትምህርት ያስተላልፍ እንደ ነበርከፍ ብሎ አይተናል፡፡ የመልእክቱ ይዘትስ ምን እንደነበር መረዳት በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ሰዎች ወደ ሰዎች ቤት መሄዳቸው ወይም ለአገልግሎትመድረክ ላይ መውጣታችን ብቻ ሳይሆን የምንለው ምንድነው የሚለው ደግሞ ሌላው ወሳኝ አሳብ ነው፡፡ ባለፈው ሁለት ዓመት አካባቢ ወደ ጌታ የሰበበሱቡት  ተወዳጁ የቅዱሳት መጻሕፍት አቀንቃኝ፣ አስተማሪና ሰባኪ የነበሩ ዶር ጆን ስቶት በአንድ ስብከታቸው ላይ እንዲህ ብለው ነበር፡፡ “ኢየሱስ ካልተዘመረ ዘማሪው መዝሙሩን አልዘመረውም፣ ኢየሱስ ካልተሰበከ ሰባኪው ስብከቱን አልሰባከውም፣የኢየሱስ ሥልጣን ካልታከለበት ጸሎቱም አልተጸለየም”፡፡ ይህ የቀድሞ ሐዋሪያት ያደረጉት  አባቶቻችንም የተከተሉት ሲሆን እኛም ጠንክረን ሊናደርገው የሚገባ ተግባር ነው፡፡ ሓዋሪያው ጳውሎስ መልእክቱም ለሰዎች ያስተላፈው ስለ ንስሐና በኢየሱስ ክርስቶስ ስለማመን(ቁ 20-21)፣ እና  ስለ እግዚአብሔር መንግሥት(ቁ.25) ይስብክና ያስተምር ነበር፡፡ እንደዚህ ዓነቱን አገልግሎት ስንሰጥ ሰዎች ይጠቀማሉ፣ይጠነክራሉ፡፡ ጳውሎስ ለራሱ ጥቅምና ዝና የሆነውን ስብከት አይሰብከም፣ እንደዚያ ያለውንም ትምህርት አያስተምርም፡፡ ራሱን አያወድስም ይልቁንስ ኢየሱስን ነው ያሳየው፡፡ ያ አገልግሎቱ እስከ ዛሬ ድረስ ወደ እኛ ዘለቀ፡፡ ዛሬ በየመድረኩ የሚሰበኩትና የሚተላለፉት ስብከቶችና ትምህርቶች ምን ይዘት አላቸው የሚለው አሳሳቢ እየሆነ በመጣበት ዘመን ላይ ነን፡፡ ሰውን ለማስደሰት ተብሎ በሚደረጉ ውድድሮች ከቁም ነገሩ ይልቅ ገለባው እየበዛ ነው፡፡ ከሰማያዊው ትምህርት ይልቅ ምድራዊ ብልጽግና ፣ ስኬት፣ የመሳሰሉት ይተኮርበታል፡፡ ካልሆነም ደግሞ የግለሰቦች ማንነት የኢየሱስን አዳኝነትና ክብር እስክሸፍን ድረስ አየተወራና እየተነገረ ነው፡፡ ይህንን ትምህርት እያዘጋጀሁ ሳለ ወደ አገር ቤት ሲደውልና ስለ አንዳንድ መንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ሲጠይቅ የአንድ ዕድሜ ጠገብ  ስለሆኑ አባት ይነግሩኝ ነበር፡፡ እኒህ ሰው አቶ ባንጫ በመባል የሚታወቁ ሲሆን ዶር ላምቤ ወደ ወላይታ ገብተው ወንጌል ሲሰብኩ የዶክተሩን በቅሎ በመጎተት ከረዱአቸው ወጣቶች አንዱ ሲሆኑ በወላይታ ውስጥ ወንጌልን በማሰራጭትና ቤተ ክርስቲያንንም በመምራት ትልቅ ዋጋ የከፈሉ ሰው ናቸው፡፡ እኒህ ሰው ጓደኞቻቸው ሁሉ ወደ ጌታ ተሰብስበው እርሳቸው ብቻ በሕይወት ያሉ ናቸው፡፡ ሰዎች ስለእሳቸው አገልግሎትና ታሪክ ለመጻፍ ፈልገው ሲጠይቋቸው የመለሱላቸው መልስ የሚገርም ነው፡፡ እኔ በሕይወት እያሁ የእኔን ታሪክ አትጻፉ፣ መጻፍ ከፈለጋችሁም የኢየሱስን ሥራና ታሪክ ጻፉ እንጂ የእኔን እንድትጽፉ አልፈልግም በማለት ነው፡፡ ይህ አስገርሞኛል፡፡ ሰው ራሱን ለማሳየት፣ ዝናውን ለማግኘት፣ ክብርንም ለማግኘት ብዙ ነገሮችን በሚያደርግበት ወቅት የእኔ ታሪክ አይጻፍም ማለት፣ ያውም የተሠራ የሚታይ ታሪክ እያለ አለመፍቀድ እንዴት ያለ አስደናቂ ጉዳይ ነው፡፡  በአገልግሎታችን ሰዎችን መጥቀም  የምንችለው መንፈሳዊ ቁም ነገርና ይዘት ያለበትን መልእክት ፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ የሆነውን እውነት፣ ሥነ-መለኮታዊና አስተምህሮአዊ የሆነውን በታማኝነት ያቀረብንላቸው እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ያስተማርናቸው፣ የሰበክናቸው፣ እና በትጋት የገሠጽናቸው እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ያለዚያ እያሳሳትናቸውና እየበደልናቸው መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ እግዚአብሔር ግን ቅዱሳንን እንድንጠቅም ስለሚፈልግ ከሰጠን መንገድ አንዱ ቁም ነገርን መናር፣ ቁም ነገርን ማስተማር፣ ቁምነገርን ማድረግም ነው፡፡   

4.   በአገልግሎታችን የቁርጠኝነት ሕይወት/ Determination/  ሲኖረን ነው፡፡

አሁንም፥ እነሆ፥ እኔ በመንፈስ ታስሬ ወደ ኢየሩሳሌም እሄዳለሁ፥ በዚያም የሚያገኘኝ ምን እንደ ሆነ አላውቅም፤ ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ እስራትና መከራ ይቆይሃል ብሎ በየከተማው ሁሉ ይመሰክርልኛል። ነገር ግን ሩጫዬንና ከጌታ ከኢየሱስ የተቀበልሁትን አገልግሎት እርሱም የእግዚአብሔርን ጸጋ ወንጌልን መመስከር እፈጽም ዘንድ ነፍሴን በእኔ ዘንድ እንደማትከብር እንደ ከንቱ ነገር እቆጥራለሁ (ቁ.22-24) ።


አሁን ጳውሎስ ወደ ኢየሩሳሌም እየሄደ ነው፡፡ በዚያ ምን እንደሚገጥመው አያውቅም ግን መከራ እንደሚደርስበት ከመንፈስ ቅዱስ ተረድቷል፡፡ ቢሆንም ግን መከራ ተቀብሎም ቢሆን በኢየሩሳሌም ያሉ ቅዱሳንን በወንጌል ለመጥቀም ቆረጠ፡፡ እንዲሁም ሰዎች መከራ መኖሩን ተረድተው ወደ ኢየሩሳሌም እንዳይሄድ አጥብቀው ቢለምኑትም በኢየሩሳሌም ለመሞትም እንኳ ዝግጁ መሆኑን በቁርጠኝነት ተናገረ፡፡  ሰዎች ከሚናገሩት ይልቅ ጳውሎስን ይገዛው የነበረው እርሱ የተቀበለው የእግዚአብሔር መንፈስ ነው፡፡ ወደ ወንጌል አገልግሎት የሚሄደው በእግዚአብሔር መንፈስ ቁጥጥር ሥር ሆኖ ነው፡፡ እርሱን የሚመራው የእግዚአብሔር መንፈስ ስለሆነ ምንም እንኳ  ወደ ኢየሩሳሌም ሲደርስ የሚጠብቀው መከራና ስደት ቢሆንም በእግዚአብሔር መንፈስ ተሥሮ ወደዚያ ሥፍራ እንደሚጓዝ በግልጽ ተናራቸው፡፡  ጳውሎስ በኢየሩሳሌም የሚጠብቀው መከራ ወንጌልን በመስበኩ ምክንያት ከአይሁዶች የሚደርስት ስደት ሊሆን ይችላል፡፡ ቢሆንም ግን እርሱ ወደ ኢየሩሳሌም የሚሄደው በመንፈስ ታሥሮ መሆኑን ግልጽ አደረገላቸው፡፡ በወንጌል አገልገሎት ውስጥ  ይህን የሚመስል ዋጋ መክፈል የሚስፈልገው ለምንድነው? መስዋዕትነት  ከፍሎ ማገለገል የሚያስፈልግበት ምክንያትማ የተሰጠው አገልግሎት  ስለነበረው ነው፡፡ እንዲሮጥ የተሰጠው ሩጫ ስላለ ነው፡፡ከኢየሱስ የተቀበለው አገልግሎት መፈጸም ስላለበት ነው፡፡ ይህን ሩጫ ማጠናቀቅና አገልግሎትን መፈጸም ሲባል መከራና ስደት መኖሩ በግልጽ እየተነገረም ቢሆን ወደ አገልሎቱ እንዲንገሰግሥ ያስገድደናል፡፡ ነፍሴ በእኔ ዘንድ እንደማትከብር እንደ ከንቱ ነገር እቆጣራታለሁ ያለው ለዚህ ነው፡፡ ይህ ሐዋሪያው ጳውሎስ ለወንጌል አገልግሎትና በወንጌል ሌሎችን ለመጥቀም ምን ያልህ እንደተሰጠ የሚመለክት ነው፡፡ እርሱ ገና በኤፌሶን ከተማ ወንጌልን መስበክ በጀመረበት ወቅት መከራና ስዴት አንዲሁም በሚሰብከው ወንጌል እውነት ምክንያት በከተማው ውስጥ ሁከት ከተነሳት ጊዜ ጀምሮ ወንጌልን በመከራ መስበክን ተለማምዷል፡፡በገና በደማስቆመንገድ ሲጠራ በጌታ ስም መከራን የሚቀበል አገልጋይ እን ደሚሆን በጌታ የተነገረለት ሰው ስለነበርና ያንን ሁሉ አልፌ እዚያጋ ስለደረሰ በኢየሩሳሌም ሰለሚጠብቀው  መከራ የሚፈራበት ምክንያት አልነበረውም፡፡   ለእግዚአብሔር አገልሎት ታማኝ የሆኑ አገልጋዮች በመከራም ውስጥ ሆነው ጌታን ያገለግሉታል፡፡ እኛ ሁላችንም እኮ ከእኛ በፊት የሄዱ ሰዎች የከፈሉበት ዋጋ ውጤቶች ነን፡፡ የቀደሙት አባቶቻችን እኛ ከዳንን ይበቃናል ብለው አልተቀመጡም፡፡ ወንጌልን በብዙ መስዋዕትነት ለእኛ ሰበኩልን፡፡ እግዚአብሔር በመስዋዕትነት የምናለግለውን አገልግሎት እጅግ በጣም አድርጎ ያከብረዋል፡፡ ቁርጠኝነት ካላቸው አገልጋዮች ጋር እግዚአብሔር ይቆማል፡፡ ስለዚህ  ከጌታየተቀበልነውን አገልግሎትና ሩጫ በመፈጸም የእግዚአብሔርን መንጋ ለመጥቀም እንድንችል እግዚአብሔር ይርዳን፡፡  

Thursday, February 9, 2017

ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካ ባትሳተፍስ?

ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካ ባትሳተፍስ?
ከመጋቢ ሳሙኤል ሾንጋ

 የፖለቲካ ጉዳይ ከነባሕሪዩ አስቸጋሪ፣ ለመተንተን አደጋች፣  በተለይም እንደ እኔ ላለ ፖለቲካ ላልቀመሰ ሰው ደግሞ የባሰ አደናጋሪ ነው፡፡ ለነገሩ ምሁራኑም ቢሆን ፖለቲካን እንደ ቀላል አያዩትም፡፡ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካ መሳተፍ የለባትም እያልን ከጎኑ ደግሞ ባለመሳተፏ የሚመጣባት  የጎንዮሽ ጉዳት ሳያስጨንቀን አልቀረም፡፡ በፖለቲካ ካለመሳተፍና ከመሳተፍ መቼም ቢሆን ከሁለት አንዱ የተሻለ መሆኑ ግድ ነው፡፡ ለማንኛውም ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው ባትሳተፍ የምትቸገርባቸው አቅጣጫዎች እነሆ
1.          አገዛዙ ዓለማዊ መሆን፡
ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው ባትሳተፍ የፖለቲካውና የመንግሥት አመራር ሙሉ በሙሉ በዓለማውያን እጅ ይገባል፡፡ የመንግሥትን አመራር እግዚአብሔርን የማያውቁ፣ ፈርሃ እግዚአብሔር የሌላቸው ሰዎች ከተቆጣጠሩት  በምድር ላይ የከፋ አመጽ ይከተላል፡፡ ቤተ ክርስቲያንና አማኞች ከለሉበት የአገር ፓርላማ ያለአንዳች ተከላካይ ቢያንስ የልዩነት አሳብ የሚያቀርብ እንኳ ሳይኖር  በሙሉ ኃይሉና አቅሙ ለቤተክርስቲያን እንቅስቃሴ እንቅፋት የሚሆን ውሳኔ ሊያስተላልፍ ይችላል፡፡ አማኞችም እንደ አናሳ ቡድን (Minority group) ስለሚታሰቡ አስፍተው መራመድ ፣ በአደባባይ መናገር፣ ሁሉ እየቀረ ይመጣል ማለት ነው፡፡ በኢትዮጵያ ፓርላማ በርከት ያሉ ጠንካራ አማኞች ስላልነበሩና ቤተክርስቲያን በዚያ ቦታ በብቃት መሳተፍ ባለመቻሏ የወታደራዊ መንግሥት ሙሉ በሙሉ ስለተቆጣጠረው ፓርላማው የሚያወጣው አዋጅና መመሪያ ጸረ እግዚአብሔር፣ ፀረ -ክርስትና ሆኖ ለ17 ዓመት ዘለቀ፡፡  በዚያን ወቅት ጥቂት ክርስቲያኖች መንቀሳቀሳ ሲጀምሩ ብዙም ሳይራመዱ ወጥመድ ይበዛባቸው ጀመረ፡፡ በቤተ ክርስቲያንም አጠቃላይ እንቅቃሴና እምነት ላይ አደጋዎች እየተበራከቱ መጡ፡፡ ያነ ግን አማኞች( ፍርሃ እግዚአብሔርና የክርስትና ልብ ያላቸውን ማለቴ ነው) በርከት ብለው በፓርላማውና በመንግስት ምክር ቤት ተገኝተው ቢሆን ኖሮ ያ ሁሉ ጥፋት አቅም ባላገኘና በእዚያ የነበሩ ጥቂት ወገኖችም አፍ ባላጡ ነበር፡፡ የአሥራ ሰባት ዓመቱ የኮሚዩኑዝም ሥርዓት በአገራችን አደባባዮች እግዚአብሔርንም አምላኪዎቹንም ባለ በሌለ ኃይሉ ይዳሰብ የነበረው  ፖለቲካው ሙሉ በሙሉ  በከሃዲዎች እጅ ስለገባ ነበር ማለት ይቻላል፡፡ የአሁኑዋም ቤተ ክርስቲያን ከዚያ ልምድ በመውሰድ በተለይም ከአሁን በኋላ በሚመጡ መንግሥታትና በዘመናቸው የባለፈው ዓይነት ቀውስ እንዳይከሰት ራሷን ማዘጋጀት ይኖርባታል፡፡
2.   የመብት መገደብ፡
አማኞች ወይም ቤተ ክርስቲያን ከፖለቲካው ከራቁ  የቤተ ክርስቲያን እና የክርስትና መብት ይገደባል፡፡ የማምለክ መብት፣ ወንጌልን በአደባባይ የመስበክ መብት፣ ነጻነታችን ሁሉ ይገደባል፡፡ በግል ክርስቶስን መከተል ባይከለከልም እንደ ቤተክርስቲያን በጋራ አዳራሽ ሞልተን አደባባይ አጣብበን ማምለክ፣ መዘመርና ማእለል ሁሉ ይገደባል፡፡ ቤተ ክርስቲያንና ሚኒስትሪ መክፈት፣ በየቀበለው ከፍተኛ የድምፅ ማጉያ  ተክለን ስብከታችንንም ሆነ ምስጥራዊ ሊሆኑ የሚገባቸውን ጸሎቶቻችንን ሁሉ ጭምር ለአቅራቢያው እስክናሰማ ድረስ የምናደርገው አካሄድ እያጠረ ፣ ቀስ በቀስ አንዳንዴ በፍጥነትም ሁሉም እየተሰፈረ መሰጠት ይጀምራል፡፡ የአምልኮ ቦታ በሕጋዊ መንገድ የመጠየቅ መብት እንደበፊቱ በነጻነት አይሆንም፣ ገመዱ እያጠረ ይሄዳል፡፡ አሁን አስፍተን የምያናቸውን ሁሉ በቀዳዳ በኩል  በአንድ ዓይን እንድናያቸው የሚያደርግ ጫና ሊደረብን ይችላል፡፡ ከዚህ ጋር በተያያዘ መንግሥት በሓይማኖት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም፣ ሃይማኖትም በመንግሥት ጉዳይ ጣልቃ አይገባም የሚለውን መርህ  አየት ማድረጉ አይከፋም፡፡ ይህ ለብዙዎቻችን በጣም ተራማጅና መልካም አሳብ ይመስለናል፡፡ መንግሥት ቤተ ክርስቲያንን እንደዚህ አድርገሽ ስበኪ ወይም አስተምሪ ፣ የጸሎትሽም ይዘት እንደዚህ ይሁን እንጂ ሌላ አልፈልግም እያለ ማድረግ ያለባትን እየመዘነ አይሰጥም ማለት ብቻ ይመስለናል፡፡ ግን ከዚያም ያለፈ ጣጣም አለው፡፡ መንግሥትና ሃይማኖት ተለያዩ ማለት ማንም ሰው የፈለገውን እምነት የመከተል መብት እንዲኖረውና ቤተ እምነቶችም በሚከተሉአቸው የእምነት አቋማቸው ላይ መንግሥት እጁን አያስገባም ማለት ቢሆንም በአንጻሩ ደግሞ  ማንም ሌላውን ሰው ይህንን እምነት ተከተል ይህንን ደግሞ አትከተል ማለት  እንደማይችልም የሚደነግግም ነው፡፡ በሌላ አባባል ወንጌል በመስበክ የሰዎችን ሃይማኖት ማስቀየር ሊያስከስስ ይችላል እንደማለትም ነው፡፡ ኢየሱስ ያድናለና ጌታን ተቀበል ማለት ሊያስወነጅል የሚችል ይሆና እደማለት ነው፡፡ የመንግሥትና የሃይማኖት ልዩነትን ፍልስፍና ከመጀመሪያውም የጠነሰሱት  የአሜሪካን የመብት አንቀጽ አርቃቂ የነበሩ እንደ ጃምስ ማዲሴን ያሉ ሲሆኑ አሳባቸው ቤተ ክርስቲያን ወይም ሃይማኖት ከማህበረሰቡ ሥልጣን ውጭ ብትሆንም የአንድ አገር ሕጋዊ ሥልጣን እንደሚመለከታት አልሸሸጉም፡፡ እንደ ማዲሴን አባባል መንግሥትና ሃይማኖት መለያየት ሁለቱም በሚያደርጉት ውሳኔ የሌላ እጅ ጣልቃ የማይገባበትና የመንግሥትም ሆነ የሃይማኖት ንጽሕና እንዲጠበቅ ያስችላል፡፡ ስለዚህ ይህ ጉዳይ በተለያዩ ጊዜያቶች ተተችቶበት ለ25 ጊዜ ያህል ወደ ከፍተኛ ፍርድ ቤት ቀርቦ ነው ውሳኔን ያገኘው፡፡  መንግሥት በሃይማኖት ጣልቃ አይገባም ፣ ሃይማኖትም በመንግሥት ጣልቃ አይገባም የሚለውን መርሀ ቃል በራሳቸው መንገድ የተረጎሙ እንደ ሞርሞን፣የይሖዋ ምስክሮች፣አሚሾችና ሌሎች የመሳሰሉትም ኢየሱስ በዮሐንስ ወንጌል ምዕራፍ 18፡36 ላይ “የእኔ መንግሥት ከዚህ ዓለም አይደለችም፣ መንግሥቴ ከዚህ ዓለም ቢሆን ኖሮ ሠራዊቶቼ ይዋጉልኝ ነበረ” ያለውን አሳብ አክለውበት የእኛ መንግሥት ከዚህ ዓለም ስላይደለ የዚህ ምድር መንግሥት በሚያደርገው ሁሉ አንሳተፍም የሚል አቋም ያዙ፡፡ ይህ ማለት መንግሥትን አንደግፍም፣ አገርን አንከላከልም፣ ግብር አንከፍልም ወዘተ የሚል ጥግ ይዘው ተገኙ ማለት ነው፡፡  ነገር ግን የካቶሊክ ቤተ ክርሰቲያን ማንም ሰው እንደፈለገው የሃይማኖት ነጻነት ሊኖረው ይገባል ግን ያ የሃይማኖት ነጻነት በአገሪቱ ሕገ መንግሥት እውቅናን ማግኘት ይኖርበታል የሚል አቋም ያዙ፡፡ ከዚህም ጋራ በመጨመር የካቶሊክ ቤተክርስቲያን የሃይማኖትና የመንግሥት መለያየት ስለማይዋጥላት  መንግስት የሚወስዳቸው ውሳኔዎች ሚዛን እንዲጠብቁ ለማድረግ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው በቂ ሚና መጫወት ይኖርባታል የሚለውን መርህ አጠንክራ ያዘች፡፡ የሆነ ሆኖ መንግሥትና ሃይማኖት የመለያየታቸው ጉዳይ የፍርድ ቤት ውሳኔ ካገኘ በኋላ ክርስቲያኖች ከአምልኮ ሥፍራ ውጪ የሚያደርጉአቸው መንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ገደብ ይበጅላቸው ጀመር፡፡ በመንግሥት ትምህርት ቤቶችና በሠራተኞች መሰብሰቢያ ቦታዎች ላይ የተሰቀሉ አሥርቱ ትዕዛዛትን የያዙ ጽሑፎች እንዲወርዱ ተጠየቀ፣ወረዱም፡፡ በግልም ሆነ በመንግሥት ትምህርት ቤቶች ትምህርት ከመጀመሩ በፊት የሚደረገው ጸሎት እንዲቀር ተጠየቀ፣ ቀረም፡፡ በየትኛው ከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ክፍል ውስጥ የቡድን መጽኸፍ ቅዱስ ጥናት እንዳይደረግ፣ በግል ትምህርት ቤቶችም ቢሆን የመጽሐፍ ቅዱስ ነክ ትምህርት እንዳይሰጥ ክልከላ እየተደረገ መጣ ፡፡ በአገራችንም መንግሥት በሃይማኖት፣ ሃይማኖትም በመንግስት ጉዳይ ጣልቃ አይገቡም እና በቤተክርስቲያን ትምህርት ቤቶች ውስጥ ለተማሪዎች መንፈሳዊ ትምህርት ማድረግ ፣ ወንጌልን መስበክ፣ መጽሐፍ ቅዱስን እንደ አንድ ትምህርት መስጠት የማይቻል እየሆነ መጣ፡፡ ይህም በመሆኑ መንግሥት በሃይማኖት ጉዳይ ፣ ሃይማኖትም በመንግሥት ጉዳዮች ጣልቃ አይገባም የሚለው መርህ ቤተ ክርሰቲያን መንግሥት በሚያደርገው ጥፋት ድምጽ እንዳታሰማ ሊከለክል የሚችል ነው፡፡ ምክንያቱም ሃይማኖት በመንግሥት ጉዳይ ጣልቃ አይገባምና፡፡    
3.   ፍትህ መጉደል፡
አማኞች እና ቤተ ክርስቲያን አማኝ ባልሆኑና በሌሎች ድርጅቶ የታቀደ ጥቃት ሊደርስባቸው ሰሚ ዳኛ ሊያጡ ይችላሉ፡፡ በተለይም የመንግሥት ባለሥልጣናት ክርስትናን የሚቃወሙና የሚጠሉ ከሆነ በየሰበቡ ክርስቲያኖች ይጠቃሉ፡፡ ከቀበሌ እስከ ሚኒስትሮች ምክር ቤት ባሉ የሥልጣን እርከኖችና መምሪያዎች አማኞች የሉም ማለት በቤተ ክርስቲያን ላይ ሁኔታዎች ከበድ ያለ መሆኑን ያሳያል፡፡ የቀበሌ ሊቀመንበር፣ የወረዳው ባለሥልጣናት፣ የፖሊስ አዘዦች፣ የማዘጋጃ ቤት ሹሞችና የመምሪያ ኃላፊች( DEPERETMENTS HEADS ) የክልል ርዕሰ መስተዳድሮች ፣ ሚኒስትሮች ፣ ዴኤታዎች ፣ ከስራቸውም ያሉ የመምሪያ ኃላፊዎች እግዚአብሔርን የማይፈሩና የቤተ ክርስቲያንን መኖር የማይፈልጉ ከሆነ ቤተ ክርስቲያን የሚደርስባትን ጥቃት ለመቃወምና መብቷን ለማስከበር አቤት የምትልበት ሥፍራ ታጣለች፡፡  የተቀበረውን ሬሳ ከጉድጓድ አውጥተው ሜዳ ላይ ሲጥሉ ወይም እንጨት ላይ ሲያንጠለጥሉ የሟች ቤተሰብ  የሚደርስበትን በደል ለማን እንደሚናገር መላ የሚጠፋው አስተዳደሩ ፀረ ክርስትና  ሲሆን ነው፡፡ የድርጊቱ ተዋኒያንን የሚሸፍን መሪ ባለስልጣን ባለበት አካባቢ ይህ ሲሆን አይተናል፣ ይኸውም ዴሞክራሲ አለ በሚባል አገር!  ባለፈው ሳምንት በናይጄሪያ አምላካቸውን እያመለኩ ባሉ ክርስቲያኖች ላይ ሌላ እምነት  ተከታዮች ከፍተኛ ጥቃት አደረሱ፡፡ በቤተ ክርስቲያኑ ግቢ የነበሩ የቅዱሳንን  መኪናዎች አንድ በአንድ በእሳት ካያያዙት በኋላ ወደ ቤተ ክርስቲያን ውስጥም ዘልቀው በመግባት አማኞች መደብደብና መግደል ጀመሩ፡፡ ያ የሆነበት ምክንያት ሴሌጃ በሚባል በዚያ ግዛት ውስጥ ከሙስሊሞች በስተቀር ሌላ እምነት፣ ከዓርብ በቀር ሌላ የአምልኮ ቀን መኖር የለበትም በሚል ነው፡፡ ይህ ሲሆን ክርስቲያኖች የጸጥታ አካል ወደሆነው ክፍል ቢደውል ፖሊስ የተላከው ሁሉም ነገር ከወደመ በኋላ ነበር፡፡ የናይጄሪያው ክርስቲያን ህብረት ዋና ዳይሬክተር ቄስ ሙሳ አስኬ የመንግሥትን ቸልተኝነት አስመልክተው ሲናገሩ : “መንግሥት ራሱ ክርስቲያኖችን ከዚህ አገር ለማጥፋት ይፈልጋል፡፡ ለሌሎች ሃይማኖቶች ያደላል፡፡ እኛ በዚህ አገር እንደ ሁለተኛ ዜጋ እንታያለን፡፡ በዚህ አገር ያሉ የጸጥታና የዋስትና ኤጄንቶች ሁሉ በሰሜኑ ሰዎች እጅ ሥር ናቸው፣ በሰሜን የአገሪቱ ክፍሎችስ ክርስቲያኖች የሉንምን ? አሁን ክርስቲያኖች ተገልለናል ግፍም እየደረሰብን ነው፡፡ እኛ ጥቃት እየሰድረብን እያለ መንግስት ለሌሎች ሃይማኖቶች ስለሚያደላ እኛ እንደ ሁለተኛ ዜጋ ተቆጥረናል፣ ግድ የለም አምላካችን ግን አልተኛም” በማለት ሆድ የሚያብስ ነገር ተናገረ፡፡ እንደ ኢትዮጵያ አቆጣጠር በክረምት ወር 1984 ዓ.ም በአዲሰ አባባ ዩኒቨርሲቲ በተካሄደው የአብያተ ክርስቲያናት መሪዎች ኮንፍራንስ ላይ ዶር አዲዬሞ ቱኩንቦ የተናገረውም ይህንን የሚመስል ነገር ነው፡፡ ዶር ቱኩምቦ ቤተ ክርስቲያን በናይጄሪያ በየጊዜው የሚደርስባትን ጥቃት አስመልክቶ ሰፊ ምስክርነት ከሰጡ በኋላ በኢትዮጵያም ሆነ በሌሎች አገሮች ያሉ ክርስቲያኖች ከሌሎች ጥቃት ሲደርስባቸው መንግሥት ዋስትና ካልሰጠ ራሳቸውን ለማዳን ድምጻቸውን ማሰማት መቻል አለባቸው ይል ነበር፡፡ ካቀረባቸው መብትሔ አሳቦች አንዱ ሰላማዊ ሰልፍ ማድረግ የሚል ይገኝበታል፡፡ ይህ እንግዲህ ከ25 ዓመት በፊት ነው፡፡ ዶር ቱኩምቦ እንደተናገሩት አስቀድመው ክርስቲያኖች በእጃቸውን ያለውን ሥልጣንና መብት ቸል በማለታቸው  ሌሎች ስለተጠቀሙበት ያ ሁሉ ችግር ደረሰባቸው፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያኖችም ፖለቲካን በሩቁ ካሉና ምንም እንቅስቃሴ ካላደረጉ በቆይታ ወይ ከመንግሥት ወይ ከሀይማኖት አካላት ተመሳሳይ ችግር ሊደርስባት ይችላል፡፡ ክርስቲያኖች በፖለቲካው ጉዳይ ቸል ካሉ በእነርሱ ላይ ጥቃት ሲደርስባቸው ቸል የሚል መንግስት በአገር ላይ እንዲሾም እየፈቀዱ ናቸው፡፡
እንግዲህ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካ መሳተፍ የለባትም በፖለቲካ ባትሳተፍም ችግር ይገጥማታል ካልን የቱጋ እንሆናለን የትኛው ነው የሚያስፈልጋት የሚለውን መፍታት ይኖርብናል፡፡ 
ከአገርና ከፖለቲካ ውጥረቱ አንጸር ቤተ ክርሰቲያን ምን ታድርግ;
 እስከ አሁን ቤተ ክርሰቲያን በፖለቲካ መሳተፍ አለባት የለባትም በሚለው አሳብ ላይ ብዙ ስናወጋ እዚህ ደርሰናል፡፡ እኔ በበኩሌ ቤተ ክርስቲያናችን በፖለቲካ ከመሳተፍዋ በፊት ተሰጣትን ሥራ ትጨርስ እንጂ ፖለቲካ ውስጥ ካልገባች ብለን ያልተሰጣትን እንድትሠራ አናስገድዳት እያልኩ ቆየሁ፡፡ አሁንም እንደዚያው ነኝ፡፡ በፖለቲካው ባትሳተፍ ግን የሚገጥማት ተግዳሮት መኖሩንም ደግሞ እንደ አቅሜ አስቀምጫለሁ፡፡ ይህንን ስል  ቤተ ክርስቲያን በአገር ጉዳይ ምንም አያገባትም እያልኩ እንዳልሆነ አስምሬበት አልፌአለሁ፡፡ በዛሬው ጽሑፌ የማሳየው ቤተ ክርሰቲያን እንደ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው ተሳታፊ ሆና፣ ወንበርም ተዘጋጅቶላት በፓርላማ ስተቀመጥ ብናይ ሞቅ ሊለን ይችል ይሆናል ፣ ግን ያ ብቻውን የሚሰጠን ረብ ሊኖረው አይችልም፡፡   ሁላችንም እንደምናምነው ቤተ ክርስቲያን የአገር ፍቅር ፣ የአገር ኃላፊነት፣ የሕዝቦች ሸክም ሊሰማት ይገባታል፡፡ በተለይም ደግሞ የወንጌላውያን አማኞች ያለ ምንም ልዩነት የዓለምን ሕዝቦች መውደድ ይኖርባቸዋል፡፡ የእግዚአብሔር ቃል እንደሚያስተምረው  በማድረግ የሕዝቦችን ችግር ማቅለል የምትችለው ቤተ ክርስቲያን ነች፡፡ እኛ በርዕሰ ጉዳያችን የምንናገረው ስለ ፖለቲካው ስለሆነ ነው እንጂ የቤተክርስቲያን ኃላፊነት በሁሉም አንጸር ነው፡፡  መንግሥት ተፈጥሮን በቁጥጥራችን ሥር እናደርጋለን ቢልም ዝናብ ሲጠፋ ፣ ሰዎችና እንስሳት ከውሃ እጥረት የተነሳ ሲያልቁ ተፈጥሮን በቁጥጥር ሥር እናደርጋለን የሚለው ሁሉ ፉከራ ሳይሥራ ቀርቶ  አይተናል፡፡ ታዲያ ቤተ ክርስቲያን ምን ታድርግ ለሚለው የሚታየኝ ከዚህ በታች ባሉ አምስት አቅጣጫዎች Aspects  ማትኮር ይገባታል ባይ ነኝ፡፡ ከዚየ ቦኃላ ራሷ በቀጥታም ሆነ በተዘዋሪ መንገድ አባላት እንዲሳተፉ በማዘጋት ኃላፊነቷን መወጣት ትችላለች፡፡ ቤተ ክርሰቲያን በፖለቲካ ከምትሳተፍ አማኞች እንደ ግለሰብ ቢሳተፉና ጠንክረው ቢታገሉ የተሻለ ነው፡፡ ቤተ ክርስቲያ እንደ ድርጅት ሰትካፈልና አማኞች ሲሳተፉት አንድ አይደለም፡፡ ልዩነቱን መተንተን የሚያስፈልው አይመስለኝም ግን ከአምስቱ አቅጣጫዎች ለዛሬ ሦስቱ እነሆ፡

1.      መንፈሳዊ አቅጣጫዎች Spiritual Aspects :

ቤተ ክርስቲያን መንግሥትን  ወይም ደግሞ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲ አባላትን እንድትቋቋመው የሚፈልጉ ወገኖች ሁሉ አስቀድመው የቤተ ክርስቲያንን ተልዕኮ ማሰብ ይኖርባቸዋል ባይ ነኝ፡፡  ጌታ እግዚአብሔር ፣ ኃያሉ አምላክ በልጁ ደም የዋጃት ቤተክርቲያኑ ክብርትና ንጽሕት እንዲትሆን ይፈልጋል፡፡ ለዓለም ሕዝቦች ሁሉ ክርስቶስን የምትገልጽ የእርሱ አምባሳደር እንድትሆን ይጠበቅባታል፡፡ ይህ ለቤተ ክርስቲያን የማንነቷ ጉዳይ ፣ ከምንም ጋር የማታወዳድረው ሀብቷ የምንጊዜም መታወቂያዋ ነው፡፡ ሞገስዋና ጉልበቷ (መንፈሳዊ አቅሟ ማለቴ እንደሆነ ይሰመርልኝ) ያለው እዚህ ውስጥ ነው፡፡ በምድር ላይ ያለቺው ቤተ ክርስቲያ የቱንም ያህል መንግሥትን ብትቃውም ወይም ብትደግፍ ክብሯንና ንጽሕናዋን ፣ የተፈጠረችብትንም ማንነት የጣለችና ያጣች እንደሆነ በምታደርገው ሁሉ አንድ የፖለቲካ ድርጅት ከሚያደርገው በላይ የከበደ ነገር ሊኖራት አይችልም፡፡ ሐዋሪያት የኢየሩሳሌምን ከተማ እና በአካባቢው ያለውን ግዛት ያነቃነቁት መንፈሳዊ ማንነታቸውን ጠብቀው ስለቆሙ ነው፡፡ ከአሁኑዋም ቤተ ክርስቲያን የተሰጣት አምላካዊ ተልእኮ አለ፡፡ ያውም ወንጌልን ለሰው ልጆች ሁሉ መስበክ፣ ያመኑትን ደቀ መዛሙርት ማድረግ፣ እግዚአብሔር በእውነትና በመንፈስ እንዲመለክ ቅዱሳን ማነሳሳትና ማገዝ ነው፡፡ የምድሩም ጉዳይ ስለሚያገባት አጥብቃ መጸለይ የተሰጣት ተልዕኮ መሆኑን ብሉይም ሆነ አዲስ ኪዳናት የሚያስስቧት ነው( 2ዜና 7፡14፣ 1 ጢሞቴዎስ 2፡1-5)፡፡ መንግሥት ጨካኝና አሬሜአዊ እንኳ ቢሆን የተሰጣት ሃላፊነት መጸለይ ነው፡፡  ሐዋሪያው ጳውሎስ ልመናና ጸሎት ምልጃና  ምስጋናም ስለ ሰዎች ሁሉ ስለ ነገሥታትም ስለ መኳንንትም ሁሉ እንዲደረግ ከሁሉ በፊት እመክራለሁ ሲል ነገሥታትና መኳንንት እኮ እንደነ ኔሮ ያሉ ጨካኞችና አብረው ያሉት አይደሉምን? ናቸው እንጂ! በጸሎትና በጸሎት ኃይል እናምናለን እያልን የመንግሥት አቋም አልዋጥ ብሎን በሚጎመዝዘን ሰዓት የተቃውሞ ሰልፍ ማስተባበርና የአቋም መግለጫ ማውጣት ቤተ ክርስቲያን ከተሰጣት ተልዕኮ ጋር አይገጥምም፡፡ ቤተ ክርስቲያን ወንጌልን ከመስበክና ጸሎት ከማድረጉ ጎን ለራሷ ቅድስትና ንጽሐት መሆኗን ማረጋገጥ ይኖርባታል፡፡ ስለ ቅድስና መስበክ የሚያስፈራን ለምንድነው? እግዚአብሔርን ስለመፍራት ማስተማር እንደጦር የሚያስጋን ምን ብንሆን ነው? ነገራችን እየባሰበት መጥቶ  ፊቺ፣ ዘረኝነት፣ ስርቆት ፣ ዝሙት፣ አመንዝራነት እና የእርስ በርስ መካሰስ ዙፋናቸውን ዘርግተውብን የሚነካቸውም ሆነ የሚደረፍራቸው የታጠው ለምንድነው ማለት አያስፈልግምን? ከዚህ አንጸር ቤተ ክርሰቲያን ሥር ነቀል ተሀዲሶ የሚያስፈልጋት ናት እንጂ መንግሥትን ለመቃወም የሚያስችል ማንነትና መንፈሳዊ ሥልጣን አላት ማለት የሚቻል አይደለም፡፡ እኔ መንግሥትን የሚሾመው እግዚአብሔር እንደሆነና ሰው ሁሉ ለተሸመው ሥልጣን ማስገዛት እንዳበት( ሮሜ 13፡1-) አምናለሁ፡፡ ስልጣን ስንል የመንግሥት ሥልጣን ብቻ ሳይሆን የቤተሰብንም የቤተ ክርስቲያንንም፣ የድርጅትንም ሥልጣን ሁሉ የሚያካትት እንደሆነ መካድ አልፈልግም፡፡ መንግሥት ከእግዚአብሔር የተሰጠውን ሥልጣን ያለቦታው ሲጠቀምና በሕዝብ ላይ በደል ሲያደርስ ቤተ ክርስቲያን የእኔ ሥራ መጸለይና መስበክ ነውና በሚል በሯን ዘግታ፣ ጭንቅላቷንም አሸዋ ውስጥ ቀብራ አላየሁም፣ አልሰማሁም  ትበል የሚል አቋም የለኝም፡፡ የጨለማውን ሥራ ሁሉ መግለጥ፣ አፍ ላጡ አፍ፣ ድምጽ ላጡ ድምጽ መሆን ይጠበቅባታል፡፡ ያንን ከማድረግ በፊት አስቀድማ ግን የጣለቸውን ማንሳት፣ የለበሰቺውን ድሪቶ ማውለቅ፣ ቤቷንና ጓዳዋን ከቆሻሻ ማጽዳት ይኖርባታል፡፡  እንደገና ጌታንና ከእግዚአብሔር የሚሰጣትን መንፈሳዊና መለኮታዊ ሥልጣን መልበስ ይኖርባታል፡፡ ያኔ መንግሥትም በውስጧ ለተቀመጠው ሥልጣን ቀኝ እጁን ይሰጣል ባይሰጥ ከቤተ ክርሰቲያን ጋር ያለውን የእግዚአብሔርን መኖር ይለማመደዋል ማለት ነው፡፡ 
     
2.     ኢኮኖሚያዊ አቅጣጫ Economical Aspect

 ገንዘብ የማይገባበት ሥፍራ የለም፡፡ ስልጣንና ገንዘብ አብረው የሚሄዱ ናቸው፡፡ ቤተ ክርስቲያን ደግሞ ስለ ገንዘብ ያላት አመለካከት ራሱ በብዙ አንጻር  ተሃዲሶ የሚያስፈልገው ነው፡፡ አንዳንዶች በባሕታዊነት የሚያምኑ ሲሆን ሌሎች ደግሞ የብልጽግና ወንጌልን መስበክ ያስደስታቸዋል፡፡ ባህታዊነትና የገዳምን ሕይወት የሚያምኑ አገልጋዮቻቸው ገና ወደ ገዳም ሳይገቡ የባህታዊነትን ሕይወት እንዲኖሩ የሚፈልጉ፣ ያንኑንም የጽድቅ መንገድ አድርገው የሚወስዱ ናቸው፡፡ በኢትዮጵያ ሳገለግል ከጓደኛዬ ጋር ምሳ ከበላን በኋላ በአንድ ካፍቴሪያ ሻይ እየጠጣን ሳለ ኬክም አዝዘን ስንበላ እግር ጥሎአቸው ወደነበርንበት ካፍቴሪያ የመጡ አንድ የቤተ ክርስቲያን መሪ ተቆጡን ፣ ወንጌላውያን ሆናችሁ እንዴት ኬክ ትበላላችሁ በሚል፡፡ እውነት ለመናገር እኛ በጊዜው ኬክ ምንበላው በሁለት ወር አንዴ ያውም አንዱን ኬክ ለሁለት ነበር( አጋጭተን ማለት ነው)፡፡ ያንኑንም ባንበላ ኬክ ቀርቶብን እንደምንጎዳ አንቆጥርም ነበር፡፡  ጊዜያትን ቆጥረን ለሁለት አጋጭተን በበላንባት ቀንም ቢሆን እኒያ አባታችን ወደዚያ ካፍተሪያ ገቡና አዩብን፡፡ ሲቆጡ እውነት አድርገን አልወሰድንም፣ የሚቀልዱ መስሎን እኛም ሳቅ ሳቅ ማለታችን በበለጠ አስቆጣቸው፡፡ የምራቸው መሆኑ ሲገባን ስሜታችን ልውጥውጥ ስልብን ጊዜ ክርስትናችን እንዳይከዳን ብለን እንደምንም ያቺን ደቂቃ ችልን ማለፋችንን አስታውሳለሁ፡፡ ወንጌላዊ ኬክ መብላት መሪውን እስክያስቆጣ ድረስ ወንጀል የሆነበት ምክንያት እስከ አሁንም አልገባኝም፣ ሊገባኝም አይችልም፡፡ በእሳቸውና በብጤዎቻቸው አስተያየት ኬክ መብላት ለወንጌላዊ የተከለከለ፣ የበላ እንደሆነ  በኃጢአት እንደሚወድቅ ፣ እሳቸው ልጆቻቸውና ሌሎች አይደለም ኬክ ሌላም አልፈው ቢበሉ ግን የፈቀደ ነው፡፡ ለማንኛውም ቤተ ክርስቲያን ስለ ባሕታዊነትም ሆነ ስለ ብልጽግና ብትሰብክ ስለ ገንዘብ ያላት አቋሟ መጽሐፍ ቅዱሳዊ መሆን አለበት፡፡ የኢትዮጵያ ቤተ ክርስቲያን ስለ ገንዘብ የምትሰብከው ምዕመናን አሥራታቸውን በጊዜ እንዲሰጡ፣ ለሕንጻ ግንባታ ገንዘብ ማሰባሰቢያ ጊዜ ዳጎስ ያለ ገንዘብ፣ ወርቅና  ሌላም ንብረት በመስጠት ውድድር እንዲሽቀዳደሙ ነው፡፡ የስብከቱም ርዕስ ስጡ ይሰጣችኃል፣ ስጡ ትባረካላችሁ ወዘተ ነው፡፡ በገንዘብ ማሰባሰቢያ ፕሮግራም ሊሰብኩ መጥተው የእኔ ሥራ በየሄድኩበት ኪስ ማስወለቅ ነው ብለው ያለምንም እፍረት የሚናሩ ሰባኪዎች አሉ፡፡ አሁን የምስተዋለው የቤተ ክርስያናት የገንዘብ አመለካከትና ገንዘብን የማግኛ ዓላማና መንገድ ከላይ ካየናቸው እውነታ ብዙም የዘለሉ አይደሉም፡፡ ይሁን እንጂ የእግዚአብሔር ቃል ስለ ገንዘብ የሚለው ተዝቆ የማያልቅ ትምህርት አለ፡፡ ገንዘብን በጽድቅ ስለ ማግኘትና በጽድቅ ስለ ማውጣት፣ በገንዘብ ቤተ ክርስቲያንን ስለማገልገልና ስለ መስጠት ቃሉ በጥልቀት ያስተምራል፡፡ ገንዘብና አማኞች ሊኖራቸው ስለሚገባቸው መሠረታዊ እውነት ትልቅ ነገረ መለኮት ሊበጅለት ይችላል፡፡ በንግድ ሥራ ላይ የተሰማሩ አባሎቻችን ንግዳቸው በትምህርትና በእውቀት የተደገፈ እንዲሆን በማሰልጠን በተሰማሩበት ሙያ እድገት እያሳዩ ለራሳቸውም ለቤተክርስቲያንም ሆነ ለምድሩ በረከት እንዲሆኑ የማዘጋጀት ሥራ መሥራት የቤተ ክርስያን ኃላፊነት ነው፡፡ አማኞች የገንዘቡን ቁልፍ ቦታ እንዲይዙ፣ እንዲያድጉ፣ ከማጭበርበር ነጻ በሆነ መንገድ እየነገዱ በአገሪቱ ምጣኔ ሀብት ተወዳዳሪነታቸውን ማሳየት እንዲችሉ ለማድረግ ቤተ ክርስቲያን በእጇ ያሉትን ሰዎች በትጋት ማሰልጠን፣ ማስታጠቅ፣ በሀብታቸው እንዲያድጉ ማበረታታት ይኖርባታል፡፡ ስጡ ይሰጣችኋል፣ ትባረካላችሁ የሚለው ትምህርት ኪስ ለማውለቅ ብቻ የሚደረግ የመድረክ መታለያ ከመመስል ማለፍ ይኖርበታል፡፡ ፖለቲከኞች ገንዘብ ላላቸው እንደ ቅቤ ይቀልጣሉ አሊያም በሰበብ በአስባቡ ይጠፉአቸዋል፡፡ ምክንያቱም እንደ ኢትዮጵያ ባሉ ደሀ አገር የፖለቲካው ጨዋታም ቢሆን የሚሰምረው ከገንዘብ ጋር ነው፡፡ ገንዘብ ከእውቀት በላይ ይጮሃል፣ ይሰማልም፡፡ ከመሸታ ቤት ወጥቶ ወደ ቤተ መንግሥት ሲገባ ፈቃድ አይጠይቅም ሰተት ብሎ በፓርላማ ይቀመጣል፡፡ ድምጹም ያስጋባል፡፡ ከዚያ ሲወጣ በሴትኛ አዳሪ ቤት አልፎ ወደ ቤተ መቅደስ ሲመጣ በእለቱ መርሀ ግብር ሴሌዳ ውስጥ ለብቻው ጊዜ ይመደብለታል፡፡ በሰማይ መንገድ እንዳለው ንጣፍ ዓለትን ያለ መሰርሰሪያ በስቶ የመግባት ችሎታ ባለቤት እንደሆነ የሚያምኑ ብዙ ናቸው፡፡ ስለዚህ ከልጅ እስከ አዋቂ ፣ ከምሁር እስከ አላዋቂ፣ ከመምህር እስከ ተማሪ፣ ከካህን እስከ ምዕመን ፣ ከአገር መሪ እስከ ቤተሰብ አስተዳዳሪ ድረስ ለገንዘብ ያልተንበረከከ፣ በገንዘብም ያልተፈተነና ያልተሸነፈ አለ ማለት ያስታዝባል፣ ዋሾም ያደርጋል፡፡  ለገንዘብ ሲል ሲሉ ባልገባቸው ፖለቲካ ውስጥ የሚንደፋደፉ፣ አገር ለቀው የኮበለሉ፣ እምነታቸውን የለወጡ ፣ ነቢያት ሳይሆኑ ነቢያት ነን ያሉ፣ ሐዋሪት ሳይሆኑ ሐዋሪያት ነን ያሉ ከቁጥር በላይ ናቸው፡፡ ከፈለገ እንደ አምላክ ሰውን ይገዛል፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያናችን በአገሪቱ ፖለቲካ ውስጥ መሳተፍ አለባት ካልን በአገሪቱ መዋዕለ ንዋይ ወይ ምጣኔ ሀብቱ ጉልህ ሚና የሚጫወቱ አባላትን የሚታዘጋጅበት ስልት መቀየስ ይኖርባታል፡፡ ስጡ ትባረካላችሁ፣ ከምትለው ትምህርቷ ባለፈ ገንዘብን የማግኘት መንገዱ ይህ ነው፣ በዚህ መንገድ ሂዱና በልጽጉ፣እደጉ፣ ከዚያ ቤተሰባችሁን ፣ ቤተ ክርስያናችሁንና አገራችሁን አገልግሉ የሚለውን ትምህርት አጥብቃ ማስተማር ይኖርባታል፡፡ የነጋዴዎችና የባለሙያዎች አገልግሎት መደራጀት አለበት፡፡ አገልገሎቱም እንዲያድግ በባለሙያዎች አማካይነት ተከታታይ ትምህርትና ሥልጠና እየተሰጠ ነጋዴዎች በንግዳቸው ክህሎትም ተግባራዊነትም እንዲኖራቸው ማድረግ ይገባል፡፡ እግዚአብሔርም እንዲባርካቸው መጸለይ ይገባል፡፡ ይህ ካልሆነ ግን ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው ዓለም ተጽእኖ ሊታመጣ አትችልም፡፡ መንግሥት ሙስናን እዋጋለሁ ሲል ቤተ ክርስቲያን  የጽድቅን አሠራር ይዛ ሥርቆት ኃጢአት ነው፣ ጉቦ ኃጢአት ነው፣ ማጭበርበር ኃጢአት ነው የምትልና ልሳኗ የሚሆኑ ንጹሐን ነጋዴችን ማሰማራት ከቻለች በፓርላማ ወንበር ባይኖራት እንኳ በፖለቲካው ለውጥ የሚያመጣ አንድ ርምጃ ፈቀቅ ብላለች ማለት ይቻላል፡፡ በገንዘብ ላይ ግልጽነትን ልማዷ መሆን አለበት፡፡ በየእሁዱ ሳምታዊ የገቢና የወጪ ሪፐርት በአጭሩ ለምዕመናን የሚያቀርቡ ቤተ ክርሰቲያናት ያሉ አይመስለኝም፡፡ ግን መለመድ ያበት ነው፡፡ በጥቅሉ ቤተ ክርሰቲያን በአገሪቱ ኢኮኖሚ ግንባታ ቀደም የሚሆኑ ሊኖሩ ይገባቸዋል፣ እርሷም በዘርፉ መሰለፍ ይኖርባታል፡፡ ይህ ከሆነ በፖለቲካው ላይ ለውጥ ማምጣት ትችላለች ባይ ነኝ፡፡ 
                
3.     የትምህርት አቅጣጫዎች Educational Aspect

ቤተ ክርቲያን በፖለቲካ ትሳተፍ የሚሉ ወገኖችን አልቃወማቸውም ግን መቼም ቢሆን ወደ ሥራ ሲገባ መሣሪያ ያስፈልጋል፡፡ ቤተ ክርስቲያንም ወደ ፖለቲካው ስትገባ ውጤታማ እንድትሆን የሚያደርጉ  መሣሪያዎች ( tools)ያስፈልጉአታል፡፡ ከመሣሪዎች አንዱ የትምህርት  ብቃት ነው፡፡ ፖለቲካ ራሱ እውቀትን የሚጠይቅ መሆኑ በማንም ሊካድ አይገባም፡፡ እግዚአብሔር የኢትዮጵያ ወንጌላውያ አብያተ ክርሰቲያናትን በተማሩ ሰዎች ባርኮአታል፡፡ ብዙ የህክምና ባለሙያዎችና የመረጃ ተክኖሎጂ አባላት አሉአት፡፡ ባለሙያዎቻችን አብዛኛዎቹ ሐኪሞች ወይም የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ፕሮፌሴሮች ናቸው፡፡ ሚሲዮናውያን ከዋሉልን ዉለታዎች አንዱ ብዙ የቤተ ክርስቲያን ሰዎች የሕክምና ሙያ እንዲሰለጥኑ በማድረጋቸው ወላጆች ልጆቻቸውን የሕክምና ዶክተሮች  እንዲሆኑ ማበረታታት የባህል ያህል ቦታ ያለው ነው፡፡ ከዚህ የተነሳ ከሌላው ሙያ ጋር ሲነጻጸር ዶክተሮች ብዙ ናቸው፡፡ በተቃራኒው ደግሞ ፖለቲካ እንደ ኃጢአት ስለተወደሰ በፖለቲካ ትምህርት የተካኑ አባላት አሉ ማለት ያስቸግራል፡፡ ፖለቲካዊ ሳይንስ(political science ) የሚማሩ ክርስቲያን ተማሪዎች ምን ያህል ናቸው፡፡ የአመራር ትምህርት ( leadership)በከፍተኛ ዲግሪ የሚማሩ ለዚህም ዝንባሌ ያላቸው አባላት እና የአባላት ልጆች አሉን ወይ;፣አገራዊ( national)፣አህጉራዊና (continental) ዓለም አቀፋዊ( global) ሕግ ጠበብት አሉን ወይ; ካሉን ደግሞ  ቤተ ክርስቲያን በገንዘብም ቢሆን ደግፋ ከፍተኛ ተወዳዳሪ እንዲሆኑ ለማስቻል የተንቀሳቀሰችበት አጋጣሚ አለ ወይ? የሚሉ መሰል ጥያቄች መልስ ማግኘት ያበት ይመስለኛል፡፡ የሥነ መለኮትን ትምህርት ( Theology) የሚማሩ አገልጋዮቿን ገንዘብ ከፍላ እንደምታስምር ሁሉ በፖለቲካና በሕግ እንዲሁም  አመራር አስተማማኝ አቅም ለመገንባት ገንዘቤተ ክርስቲያን  አውጥታ በመስኩ የሚማሩትን ሰዎች ማፍራት አለባት ባይ ነኝ ፡፡ ተሳሳትክ ትሉኝ ይሆን? የህክምና ባለሙያዎች በረከት ሆነውልናል፣ የሥነ መለኮት ተማሪዎችም የእግዚአብሔርን ቃል አስታጠቀውናል፡፡  ፖለቲካ ግን ሙያቸው ስላይደለ እነርሱን ከዚህ አንጻር  መጠበቅ የለብንም፡፡ ፖለቲከኛ መሆን ግን ሌላ ብቃትና ክህሎትን እውቀትንም የሚጠይቅ ስለሆነ በጉዳዩ ማሰብ ተገቢ ነው፡፡ ሥነ መለኮት ተቋማት በእነዚህ ዘርፎች ሰዎችን ማሰልጠን ቢችሉስ ኃጢአቱ  እምኑ ላይ ነው? በአመራር በኩል የተጀመረ አስደሳች ነገር አለ፡፡ ወንጌላውያን አብያ ክርስቲያናት ተባብረው የፖለቲካ ትምህርት ከፍተው አባሎቻቸውን በከፍተኛ ዲግሪ ቢያሰለጥኑና የአገሪቱን ፖለቲካ እንዲመሩ የሚያስችል ክህሎት ቢያስታጥቁአቸው ራዕይ የጣሉ ያስመስልባቸው ይሆን? እኔ ግን ይህ መሆን አለበት ባይ ነኝ፡፡  ክርስቲያን በፖለተካዊ ሳይንስ ብቻ ሳይሆን በሁሉም የትምህርት ዘርፍ ተጽዕኖ ፈጣሪ  አባላት እንዲኖሩአት መጸለይና መሥራት  ይኖርባታል፡፡ ያለዚያ ግን ወደ ፖሊቲካው ሜዳ ወጥታ ያለ በቂ መሣሪያ ወደ ጦር ሜዳ እንደሄደ ተዋጊ ሠራዊት ትሆናለች፡፡ 
ቤተክርስቲያን በዚህ ምድር ላይ የሕበረተሰቡ አካል እንደመሆኑዋ መጠን ሕብረተሰቡን የሚለከት ነገር ሁሉ እርሷን ወደ ጎን ስለማይተዋት በህብረተሰቡ እልተእለት ጉዳዮች ላይ መግባት አለባት የሚል ሙግት በብዙ ይደመጣል፡፡ ሕብረተሰቡ ከሚጋፈጣቸው እለትተእለት ጉዳዮች አንዱ ፖለቲካና ከፖለቲካ ጋር ተያይዞ የሚመጣ ነው፡፡  እኔ በበኩሌ ቤተ ክርስቲያን ሠርታ ልትጨርሰው የማትችለው በጣም ብዙ ሥራ ስላላት ያንኑን ትወጣው ፣ ፖለቲካውን ለፖለቲከኞች ትተውላቸው እያልኩ ግን እንዲያው የግድ በፖለቲካ መሳተፍ አለባት ካልን መወሰድ ስላለባቸው ቅድመ ሁኔታዎች አስቀምጫለሁ፡፡ ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው ውጤታማ እንዲትሆን ከፈለግን ተወዳዳሪነቷ ሊታሳይባቸው ከሚገባ ጠርዞች ሦስቱን ማለትም በመንፈሳዊ ሕይወት፣ በትምህርት፣ በኢኮኖሚ ተወዳዳሪ መሆን እንዳለባት ለማሳየት ሞክሬአለሁ፡፡ አሁን ደግሞ ትንታኔዬን ካቆምኩበት ልቀጥል፡፡ 
4
5.      የፖለቲካው አቅጣጫዎች Political Aspect

 ቤተክርስቲያን  የሕብረተሰቡ አካል እንደመሆኑዋ መጠን በህብረተሰቡ እለት ተእለት ጉዳዮች ላይ መግባት አለባት የሚል ሙግት በብዙ ይደመጣል፡፡ ሕብረተሰቡ ከሚጋፈጣቸው እለት ተእለት ጉዳዮች አንዱ ፖለቲካና ከፖለቲካ ጋር ተያይዞ የሚመጣ ነው፡፡  እኔ በበኩሌ ቤተ ክርስቲያን ሠርታ ያልጨረሰቺው በጣም ብዙ ሥራ ስላላት ያንኑን ትወጣው ፣ ፖለቲካውን ለፖለቲከኞች ትተውላቸው እያልኩ ግን እንዲያው የግድ በፖለቲካ መሳተፍ አለባት ካልን መወሰድ ስላለባቸው ቅድመ ሁኔታዎች አሳቤን አስቀምጫለሁ፡፡ እንደ እኔ  ቤተክርስቲያናችን መንግሥት ለምክርና ለጸሎት እስክፈልጋት ድረስ የከበደችና የተሞገሰች እንድትሆን እንናፍቃለን፡፡ መንግሥት  በከባባድ ጉዳዮቹ ላይ የቤተ ክርስቲያንን የጸሎት ርዳታ የሚሻበት እና በአገራዊ ጉዳይ መፍትሔ አመንጪና የችግሮችም ፈቺ እንደሆነች ተቀብሎ ራሱ ነይ ታስፈልጊናለሽ እያለ የሚያማክራት ቢሆን እንዴት በተደሰትን! ታላላቅ የአሜሪካን መሪዎች የተወደዱ አገልጋይ የሆኑ ዶር ቢሊ ግርሃምን እየጠሩ እንዲጸልዩላቸው ያደረጉበት ጊዜያቶች ብዙ ነበሩ፡፡ ለምሳሌ በጆርጅ ዴቭልዩ ቡሽ  ፕሬዝዳንታዊ በዓለ ስመቱን በጸሎት የመሩት ዶር ቢሊ ነበሩ፡፡ ቢሊ በአጭሩ እንደሚከተለው ጸልየው ፕሬዝዳንቱን ለሥራ አሠማሩ፡
 And now we come to a new era in our history. In Thy sovereignty Thou hast permitted George Bush to lead us at this momentous hour of our history for the next four years. As he today places his hand upon the Bible and solemnly swears before Thee to preserve, protect and defend the Constitution, give him the wisdom, integrity and courage to help this become a nation that is gentle and kind. Protect him from physical danger, and in the lonely moments of decision grant him Thy wisdom to know what is morally right and an uncompromising courage to do it. Give him a cool head and a warm heart. Give him a compassion for those in physical, moral and spiritual need. O God, we consecrate today George Herbert Walker Bush to the presidency of these United States with the assurance that from this hour on, as he and his family move into the White House, they will have the presence and power of the One who said, “I will never leave thee or forsake thee. [Hebrews 13:5(  የቢሊ ግርሃም ልጅ ፍራንክሊን ግርሃም ከጻፈው የኢሜይል መልእክት የተወሰደ)፡፡

 የኢትዮጵያ መንግሥትም ፕሬዝዳንቱንና ጠቅላይ ሚኒስትሩን ሲሰይም እጃቸውን ጭነው ተሽዋሚውንና አገሩን በጸሎት ለእግዚአብሔር አሳልፈው የሚሰጡ መሪዎች እንዲኖሩን ብንጸልይና ብንሠራበትስ! በአገራችን ላይ የእግዚአብሔር ሉዓላዊ አመራር እንዲሰፍን  ብንቃትትስ? ፓርላማው ስብሰባውን ከመጀመሩ በፊት የቤተ ክርስቲያን ቡራኬና ጸሎት የሚያስቀድምበት ሥርዓት እንዲኖር ለማድረግ መንፈሳዊ ጦርነት ብንዋጋስ? ሌላውን ሁሉ ትተን በዚህ በኩል ብንተጋ የበለጠ መልካም ይመስለኛል፡፡
ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካው መሳተፍ ግድ ነው ካልንና በመስኩ  ውጤታማ እንዲትሆን ከፈለግን ተወዳዳሪነቷን ሊታሳይባቸው ከሚገባ ጠርዞች ሦስቱን ማለትም በመንፈሳዊ ሕይወት፣ በትምህርት፣ በኢኮኖሚ ተወዳዳሪ መሆን እንዳለባት ለማሳየት ሞክሬአለሁ፡፡ አሁን ደግሞ ትንታኔዬን ካቆምኩበት ልቀጥል፡፡ 
በፖለቲካ ውጤታማ መሆን እንዴት እንደሚቻል ከእኔ ይልቅ የዚያ ዘርፍ ባለሙያዎች ቢናገሩ የበለጠ ክብደት ይኖረዋል፣ ሰሚውም ጆሮውን የሚሰጠው ያኔ ነው፡፡ ይሁን እንጂ ከአጠቃላይ ምልኬታዬ ተነስቼ የሚከተሉት ነጥቦች ትኩረት ሊሰጣቸው ይገባል ባይ ነኝ፡፡   የፖለቲካውን ሳይንስ መማር አስፈላጊ ቢሆንም ከዚያ ጋር አብረው የሚሄዱ ተጓዳኝ ነገሮች የመኖራቸው ሐቅ ሊሸሸግ አይችልም፡፡ ፖለቲከኛ መሆን ብዙ ረግዳሮት የሚበዛበት፣ ብዙ ተቃዋሚም ጠላትምንም የሚያፈሩበት ፣ ከተሳካም ደግሞ ለብዙ ሽልማትና ክብር የሚያበቃ ከፍ ያለ ሙያ ነው፡፡ ይህ ሙያ በህብረተሰቡ ውስጥ ልዩነትን የሚያመጣ በመሆኑ የዚያኑ ያህል አቅም የሚጠይቅ ነው፡፡ በሙያው ውጤታማ ለመሆን ጥንክሮ ከመሥራት ጋር ጠቢብ መሆንም ያስፈልጋል፡፡ ግን ውጤታማ ፖለቲከኛ ምን ዓይነት ነው፡፡
·         ተናጋሪነት( Eloquency)፡
የንግግር ችሎታ በፖለቲካው ዓለም ቀዳሚና ተወዳጅ ጉዳይ ነው፡፡ እውቀትን በንግግር መግለጽ የማይችሉ ሰዎች የፖለቲካው መሪ መሆን  ያስቸግራቸዋል፡፡ በሚሊዮን የሚቆጠር ሕዝብ ትኩረት ከሳቡና አድማጫቸውን ማስከተል ከቻሉ የዓለም የፖለቲካ መሪዎች በርካታ ቁጥር ያላቸው በአንድ ርዕሰ -አሳብ ተናግረው የማሳመን ችሎታ ያላቸው ናቸው፡፡ ስለዚህ ነው በፖለቲካው ትምህርት ቤት በሕዝብ ፊት የመናገር Public speaking እና ግንኙነት communication የመሳሰሉት እንደ ዋና ኮርስ ተደርገው የሚሰጡት፡፡ ውስጣቸው በእውቀት የታመቀ ብዙ ምሁራን ቢኖሩንም ፊት ለፊት የሚታዩት ግን ተናጋሪዎች ናቸው፡፡ የሚናገሩ ሰዎች ይደመጣሉ፡፡
በዓለማችን ፖለቲካዊ ተሳትፎ የሚታይ ለውጥ ያመጡ  የቤተ ክርስያቲን መሪዎች እንዳሉ ታሪክ ይመሰክራል፡፡ የሰብዓዊ መብት ተሟጋች የደቡብ አፍሪካው ዴድሞንድ ቱቱ የደቡብ አፍሪካ አንግሊካን ቤተ ክርሰቲያን ካህን ነበር፡፡ ቱቱ በጆሐንስቤርግ  በሚገኘው ቅዱስ ጴጥሮስ ስነ መለኮት ኮሌጅ St Peter Theological College ገብቶ ከተማረ በኋላ ከኪነግስ ኮሌጅ/ King”s College/ በሥነ መለኮት የመጀመሪያ ዲግሪ አገኘ፡፡ ከመንፈሳዊ ትምህርቱ ጋር ለቤተ ክርስቲያን የሰጠው አገልግሎት ከፍተኛ ሥፍራ ያለው ነው፡፡ በተለይም ከቅዱስ ጴጥሮስ ኮሌጅ ከተመረቀ በኋላ የአንግሊካን ቤተ ክርስቲያን ካህን ሆኖ ተሾመ፡፡  ወደ እንግሊዝ አገር በማቅናት  የዓለም አብያተ ክርስቲያናት ምክር ቤት የሚያስተዳድረው የሥነ መለኮት ትምህርት ቤቶች ፌንድ (Theoogical Education fund of the World councel of Churches) በተባለው ድርጅት ውስጥ ምክትል ፕሬዝዳንት ሆኖው አገልግሏል፡፡ ከእንግልዝ የ3 ዓመት ቆይታ በኋላ ወደ ደቡብ አፍሪካ ሲመለስ ደግሞ  የቅድስት ማሪያም ካቴድራል( Dean of St Mary’s Catedral) ዲን ሆነው ተሸመዋል፡፡ ታዲያ ቱቱ ኤች ኤ ቪ ኤዲስን፣ የዘር መድሎን፣ ድህነት፣ ወሲባዊ ትንኮሳን፣እና መሳሰሉትን በጥብቅ በመዋጋቱና በዚህ ረገድ ባስመዘገበው አመርቂ ውጤት የተለያዩ ዓለም አቀፍ ሽልማቶችን ለመቀበል ችሏል፡፡ ዴስሞንድ ቱቱ በትምህርት ብቃቱ እርሱን በብዙ የሚበልጡ ሰዎች ቢኖሩም ግን የንግግር ችሎታው በበለጠ አጉልቶታል፡፡ እንደ ሶቅራጥስ ፣ ሸክስፔር፣ አሌክሳንደር ፖፔ እና የከሳሰሉት የዓለማችን እውቅ  ፈላስፋዎችና መሪዎች የተናገሩት አሳብ እንደ እንደሚጠቀስ ሁሉ የዴስሞንድ ቱቱም ጥቅሶች በርካታዎች ናቸው፡፡ ሌላው አስገራሚ ተናጋሪ ሰው የአሜሪካው የጥቁሮች መብት ተሟጋች የነበረው ማርቲን ሉተር ኪንግ ነው፡፡ ሉተር ስለ ሰብዓዊ መብት የሚከራከር ቢሆንም የመጥመቃውያን ቤተ ክርሰቲያን መጋቢ ነበር፡፡ አባቱም ሆኑ አያቱ በአትላንታ ጆርጂያ ባለው የአቤንኤዜር መጥመቂያውያን ቤተ ክርስቲያን መጋቢዎች በመሆናቸው ሉተር ከልጅነቱ ጀምሮ ከቤተሰቡ መንፈሳዊ ነገር እየተመገበ አድጎ እንደወላጆቹ ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ራሱን የሰጠ ሰው ነበር፡፡ በአልባማ ሜንቶጎሞሪ የሚገኘው የዳክስተር መጥመቃውያን ቤተ ክርሰቲያን ዋና መጋቢ ሆኖ እስከሞት እለቱ ድረስ አገልገሏል፡፡ ከቤተክርስቲያን አገልግሎቱ ጎን ፍትህ በተጓደሉባቸው ቦታዎች ሁሉ በመገኘት ስለ ሰዎች ልጆች መብት ለመከራከር 6 ሚሊዮን ማይልስ በመጓዝ 25 ሺህ ጊዜ ንግግር አድርጓል፡፡ በተለይም 250000 ሕዝብ በተሰበሰበበት በዋሽንግተን ባደረገው “እኔ ሕልም አለኝ / I have a dream /” በተሰኘው ንግግሩ ታይም መጋዝይን  የተሰኘው መጽሔት  “ man of the year (የዘመኑ ሰው )” የሚል ስም ሰጥተውታል፡፡ ከሰብኣዊ መብት ጋር በተያያዘ 25 መጻሕፍትን ጽፎ ከሕዝብ አስነብቧል፡፡  ለሰብአዊ መብት ባደረገው ተጋድሎ ጥቁሮች ከነጮች ጋር እኩል በሕዝብ አውቶቡስ እንድሳፈሩ እስከማድረግ ከመድረሱም በላይ ባደረገው መስዋዕትነት በተሞላው እንቅስቃሴው ምክንያት ከኖቬል በሽልማት የተገኘውን 54 123 የአሜሪካን ዶላር ከሰብአዊ መብት እንቅስቃሴ እንዲውል አበርክቷል፡፡ በእነዚያ ጊዜያቶች ሁሉ ኪንግ በነጮች ፖሊስ እየተያዘ ወደ እሥር ቤት ወርዷል፣ ቤቱም በቦምብ ጋይቷል፡፡ በመጨረሻም በዚህ እንቅቃሴው ምክንያት በባላንጣዎቹ ደረሰበት ጥቃት ሕይወቱን ሊያጣ ችሏል፡፡ በእነዚያ ሁሉ ጊዜያቶች የሚያሰማቸው ንግግሮች የአድማጩን ትኩረት በመሳብ ልዩነቶች ማምጣት ችለዋል፡፡
ሌላው ሰው ፈራክሊን ግርሃም ነው፡፡ በአሁኑ ጊዜ ወንጌላዊው ፍራንክሊን በፖለቲካ መሪዎች ዘንድ ትልቅ ግምት ያገኘው ስለ ፖለቲካ ተናግሮ ሳይሆን ለውጥ የሚያመጣ እንቅስቃሴ አድርጎ ነው፡፡ በቅርብ ጊዜ ካደረጋቸው አውራ ተግባራት የተወሰኑትን ብንጠቅስ  ፕሬዝዳት ባራክ ኦባማ የግብረ ሰዶማዊን ጋብቻ በጠቅላይ ፍርድ ቤት አስወስነው አንጀታችንን ባሳረሩበት ወቅት ጋብቻን የሚደነግግ እግዚአብሔር እንጂ መንግሥት ወይም ጠቅላይ ፍርድ ቤት አይደለም በማለት ቀጥተኛ ተቃውሞ በማሰማት ግንባር ቀደም ሰው ሊሆን ቻለ፡፡ የአሜሪካው ሕዝብ ፕሬዝዳንታቸውን ለመምረጥ በሚዘጋጁት ወቅት በ50ዎቹ ግዛቶች በመዘዋወር የአደባባይ ጸሎት እንዲደረግ ሕዝበ ክርስቲያኑንን አንቀሳቅሷል፡፡  እኔ በምኖርበት የሚቺጋን ግዛት ጸሎቱ የተካሄደው በግዛቱ ገዥ ቢሮ ግቢ ውስጥ ሜዳ ላይ በብዙ ሺህ የሚቆጡ ወንጌላውያ አማኞች በተሰበሰቡበት ሲሆን አሜሪካውያን በጸሎት ሰዓት ተንሰቅስቀው ሲያለቅሱ ለመጀመሪያ ጊዜ ያየሁት በዚህ የጸሎት ፕሮግራም ነው፡፡ ፍራንክሊንም በንግግር ችሎታው የተመሰገነ በመሆኑ የታላላቅ መሪዎችን ጆሮና ልብ እየማረከ ያለ የዘመናችን እውቅ አገልጋይ ነው፡፡    
ለመጥቀስ ያህል ብቻ እንጂ እነዚህን የሚመስሉ ብዙ የእግዚአብሔር ሰዎችና  ታሪኮቻቸው አሉ፡፡ ስለዚህ እኛ ከእነርሱ ብዙ መማር እንችላል፡፡ አማኞችና አገልጋዮች በፖለቲካው ተሳትፈው ለውጥ እንዲያመጡ እንጂ በፖለቲካው መሳተፋቸው ቁጥር ለመሙላት ብቻ እንዲሆን ይገባል ብዬ የማምንበት አቅም እስከአሁን አላገኘሁም፡፡ ተናጋሪዎች የሆኑ ፣ ፖለቲካን በየአንጓው እየሰበሩ ማስቀመጥና ለሚፈልገውም መስጠት የሚችሉ አባሎቻችን ካሉ እናበረታታቸውና ይሳተፉበት፡፡ መንግሥትንም በእኩይ ተግባሩ ይቃወሙት፣ በመልካም ሥራውም ያወዲሱት እላለሁ፡፡
ባለፈው በአገራችን በሕዝብና በመንግሥት መካከል በተፈጠረው ግጭት ምክንያት መንግሥት የተቃዋሚ የፖለቲካ መሪዎችንና ሌሎችን ለውይይት ጋብዞ ነበር፡፡ በዚያ ውስጥ የወንጌላውያን አብያተ ክርስቲያናት መሪዎችም ነበሩ( የሃይማኖት መሪዎች ስለሆኑ ነው የተጠሩት ማለት ነው)፡፡ እነዚህ ወገኖች በዚያ ሥፍራ ተገኝተው የሚባለውን ሰሙ፣ ከገዥ ፓርቲም ሆነ ከተቃዋሚ የፖለቲካ አባላት የሚወረወረውን ክርክር አደመጡ፣ ከዚያም ወደ ቤታቸው መጡ፡፡ በዚያ ፎረም መሳተፋቸውንም ያወቅነው ምስላቸውን ቴሌቭዥን ስናይ ነው፡፡ ይህም በመሆኑ በጣም ደስ ይለናል፡፡ መሪዎቻችን በስብሰባው በተገኙበት አጋጣሚ ከገዥው ፓሪቲም ሆነ ለተቃዋሚ የፖለቲካ ተቋማት፣ ለመንግሥትና ለሕብረተሰብ የሚሆን ነገር ሲናገሩ ግን አልሰማናቸውም፡፡ በቤተ ክርስቲያናቸው ጣሪያ ሲያርገበግቡ ፣ መድረኩንም ሲያናውጡ የምናያቸው ሰባኪዎች በቤተ መንግስት አካባቢ ጸጥ ረጭ ያሉት ምን ነክቶአቸው ነው ባንል ይሻላል፡፡  እነዚህ ሰዎች የጸሎት ሰዎች ናቸው፣ የመጽሐፍ ቅዱስ ሰዎች ናቸው እንጂ ፖለቲካን የሚያውቁ አይደሉም፡፡ የቤተ ክርስቲያን ቋንቋ እንጂ የፖለቲካ ነገር ውስጣቸው የለም፡፡ ስለዚህ ምን እንዲሉ ይጠበቃል?  መሄድ ሄደዋል፣ መሳተፍንም ተሳትፈዋል፣ የተጠሩበት ቦታ ሁሉ  ዋናውን  መሪ መላክ የቤተ ክርሰቲያን የቆየ ባህል ስለሆነ ያንን ልማድ ይዘው እዚያ ቦታ ሄዱ እንጂ ምን እንደሚያደርጉ ገብቶአቸው  አልነበረም፡፡ እንዳይናገሩ የአገሪቱን የፖቲካ አካሄድ አያውቁትም፣ የፖለቲካው ቃላትም/ terminology/ የላቸውም ፡፡ እነርሱ ያላቸው የሥነ መለኮታዊ ቃል  theological terms ነው፡፡ ያንን እዚያ ቢናገሩ የሚያደምጣቸውም የሚረዳቸውም የለም፡፡  በቤተ ክርስቲያን አካባቢ ያለን አገልጋዮች በሕዝብ ፊት ቆመን የመናገር እድላችን ከፖለቲካኞች ይልቅ የሰፋ ነው፡፡ የምንናገረው ግን የአንድ አቅጣጫ ንግግር/ Monologue/ የሚባል ዓይነት ነው ፡፡ ያውም አንደዳንዴ ተፋልሶ የበዛበት ቢሆንም ማንም አያርመውም፡፡ አንዳንዴ ሰፊ ሰዓት ተጠቅመን በተናርነው ነገር ውስጥ እዚህ ግባ የሚባል ቁም ነገር ሳንሰጥ ከመድረክ ስንወርድ አድማጩ እግዚአብሔር ይባርክህ ብሎ ይመርቀናል፡፡ ሰባኪዎች ሁሉ እንደዚያ ናቸው እያልኩ አይደለም፡፡ ይህ አሳብ በጣም በሚገርም ሁኔታ አስተምረውን  የቤተ ክርስቲያንን ያሳደጉ የተባረኩ አስተማሪዎቻችንን አይመለከትም፡፡ አንዳንድ ትርጉም የሌለው እንጨት እንጨት የሚል ነገር  እየተናገሩ ሕዝቡን የግድ አሜን እንድል ወይም እንዲያጨበጭብ የሚያድርጉ ፣ ቤተ መቅደሱንም በሁኬትና በጩኸት ሞልተው የሚወርዱ የዘመናችን ሰባኪዎችን ነው እንጂ፡፡ እንዲያም ሆኖ ጉባኤያችን ይባርካቸዋል፣ ይመርቃቸዋልም፡፡ በዚህ ልማድ የኖረ ሰው ወደ ሌላው አደባባይ ቢሄድና እናገራለሁ ቢል አሜን የሚለው የለም፣ ተከራካሪ ነው ያለው፡፡ ፖለቲካ በመንፈስ ሳይሆን በአእምሮ የሚሠራ ሰለሆነ አንድ ዓረፍተ ነገር ጣል ባደረግን ቁጥር ሁሉ አሜን በሉ የምንበልበት ቦታ አይደለም፡፡ እስቲ መድረኮቻችንን፣ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ የሚተላለፉ መልእክቶችን ፣ የመልእከቶችንም ይዘት ፣ ከእግዚአብሔር ዘላለማዊ ቃልም ጋር  ስላላቸው መስማማት ተመልከቱ፡፡ በሰማናቸው ቁጥር ምነው መካሪ በተገኘ የሚያሰኙ ናቸው፡፡ ምነው እነዚህን ሰባኪዎች እጃቸውን ይዞ የሚመራ የታጣው ያስብላል፡፡ ይህንን ስናይ ቤተ ክርሰቲያ በፖለቲካው ትሳተፍ ለማለት አቅም ያንሰናል፡፡ ምን ይዛ ፣ ማንን ይዛ የሚለው መሰመር ይኖርበታል፡፡  ስለዚህ ቤተክርስቲያን  በንግግር ችሎታቸው ላቅ ያሉና  ተከራክረው ሌላውን መቋቋም የሚችል  ፣ የሚናገሩትንም ነገር የሚያውዉና ፣ የራሳቸውንም አሳብ ከጥቃት የመመከት ብቃት ያላቸውን  ሰዎችን በፖለቲካው ማሰለፍ ከቻለች ውጤታ ትሆናለች እላለሁ፡፡ ያለዚያ ግን በፖለቲካው እንድትሳተፍ ባንመክራት ይሻላል፡፡  
·         ቆራጥነት፡
ለሰዎች ልጆች መብት ተከራክረው ውጤት ያሰመዘገቡ ቆራጥ አቋም ያላቸው ሰዎች ናቸው፡፡ የሚኖሩት ከራሳቸው ሳይሆን ለሰው ስለሆነ ሞታቸውንም ስለ ሰው ነጻነት ሲሉ ሞተዋል፣፣ በየአሥር ቤቶቹ ተንገላተዋል፡፡ በፖለቲካ መሳተፍ የሚፈልግ ሰው ሁሉ ቆራጥ መሆን ይጠበቅበታል፡፡ የሚያስከፍለው ዋጋ መኖሩን ማወቅና ዋጋውንም ለመክፈል መዘጋጀት ይኖርበታል ፡፡ እነ ማርቲን ሉተር ኪንግ ያደረጉት ይህንን ነው፡፡  ለወንጌላዊ ያሬድ ጣላሁን ትልቅ አክብሮት አለኝ፡፡ ለኢትዮጵያው ጠቅላይ ሚኒስትር ቀጥታ ደብዳቤ ጽፎ በማህበራዊ መገናኛ ለጥፏልና፣ ወንጌላዊ ያሬድ በጽሑፍ ካስተላለፈው መልእክት በተጨማሪ በሕዝብ ፊት ቀርበው ንግግር አድርጓል፡፡ በጣም ጠንካራ አሳቦችን ተናገሯል፡፡ በሕዝቦች መካከል የተፈጠረውን ጥላቻ  በማውገዝ በመናገሩ አደንቀዋለሁ፡፡ ጨለማ ጨለማን ስለሚወልድ  መንግሥት በሕዝብ ገንዘብ በተገዛው መሣሪያ ሕዝብን መልሶ መግደልን እንዲተው፣ ጦር ሠራዊቱ የጠመንጃ አፈሙዙን እንዲያዘቀዝቅ  መንግሥት መማጸኑ በጀ የሚያስብለው ነው፡፡ ድፍረትና የአገር ፍቅር የተሞላበት ንግግር ነው፡፡ “ይህንን ተማጽኖ በኢትዮጵያ ላይ ሰላም ሰፍኖ በፖለቲካ ኃይሎች መካከል ገንቢ የሆነ ድርድር ተደርጎ የሁሉም ሕዝብ ድምጽ ተሰምቶ በሰዎች መካከል እኩልነት ተከብሮ እስከማይ ድረስ ይህንን ጩኼቴን አላቆምም፡፡” በማለት ቃል ገባ፣ ጉባኤተኛውም አጨበጨበለት፡፡ እኔም ስሰማው እንደ አገራችን አባባል በልቤ “ አንበሳ” አልኩት፣ አሁን ቆራጥ የቤተ ክርስቲያናችን ልጅ ተገኘ አልኩ፡፡ በተለይም የአገራችን ሕዝቦች መታሰር፣ መገረፍ፣ አገር ጥሎ መሰደደድ ብቻ ሳይሆን በአገር ውስጥ ያለው ወጣት እየደረሰበት ያለው የህልና ስብራት ከፍተኛ መሆኑን መናገሩ ያስመሰግነዋል፣ የአገርና የሕዝብ ተቆርቋርነቱን ያሳያል፡፡በዚሁ ቢቀጥልበት መልካም ነው ብዬ ተመኘሁለት፡፡  ይህንን ስል ከልቤ ነው፡፡ ወንጌላዊ ያሬድ ለጠቅላይ ሚኒስትሩ በጻፉት ደብዳቤ ምክንያት ሰው ሁሉ ሰግቶ የት እንዳለ ስልክ እየደወሉ እንደጠየቁት ይናገር ነበር፡፡ ግን እኮ ከወንጌላዊ ያሬድ በፊት ወንጌላዊ ጸጋአብ በቀለ ብስለት የተሞላውን ደብዳቤ ጽፏል፡፡ ታዲያ  እነ ወንጌላዊ ያሬድ ጥላሁን ምን ዋጣቸው? እንደዚያ ግዳይ እንደጣለ ሰው በጣም ሲንጎማለሉ የነበሩ ምንነው ከአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ በኃዋላ የውሃ ሽታ ሆኑ? የሆነ ሕዝባዊ ሰልፍ እየተጠበቁ ነው ማለት ነው? ትግሌን እቀጥላሁ አልተውም ሲሉ የነበሩ አስቸኳይ ጊዜ አዋጁ ሲታወጅ ሕዝቡ ወደ ቤቱ ሲገባ እነርሱም አብረው ቤታቸው ገቡ፡፡ ከመጀመሪያውም ቢሆን የሕዝብ እንቅስቃሴ አይተው አለሁ ለማለት ያደረጉት እንጂ እውነተኛ አቋም ኖሮአቸው ፣ በራሳቸውም ተነሳስተው የሕዝብ ጉዳት ከንክኖአቸው አይደለም እንዳያስብላቸው ፈራሁላቸው፡፡ የአስቸኳይ ጊዜ አዋጅ ከታወጀ በኋላስ ቢሆን ሰዎች አላታሠሩም? የመንግሥት ተቃዋሚዎች እስከዛሬ ዝም አላሉም፡፡ የወንጌል ሰባኪዎች ነን ያሉ ግን ለሕዝብ እታገላለሁ፣ ትግሌንና ተቃውሞዬን አልተውም ብለው በዓለም መድረክ ተናግረው ከዚያ ወዳጅ ያፈሩ ወንጌላውያኖቻችን አፋቸውን ዘጉ፡፡ ለነገሩ ወንጌላው ያሬድ መልእክቱን ከመጻፉ ቀደም ብሎ ወንጌላዊ ጸጋአብ በቀለ ጠንካራ መልእክት ጽፏል የሚራግብለትን አላገኘም አንዲ፡፡ ታዲያ ጸጋአብ እስከ አሁን ማን ነካው? ነገሮችን ካካበድናቸው ሳናውቅ የራሳችን አድናቂዎች እንሆናለን፡፡   እኔ እንዲያው ሳየው  ወንጌላዊ ያሬድ ሁለት ችግሮች ተስተውሎበታል፡፡ አንደኛ ምንም የመንግሥት አካል በሌለበት ተቃዋሚዎች ብቻ በተሰበሰቡበት፣ ለንግግሩ ምላሽ የሚሰጠውና ሰምተውም የለውጥ ርምጃ የሚወስድ በሌለበት ፣ በእያንዳንዱ ዐረፍተ ነገር መካካል የሚያጨበጭብ ጉባኤ ፊት ብቻ ነው የተናገረው፡፡ ይህ ብቻ ቆራጥነትን አያሳይም፡፡ በእርግጥ ንግግሩ ጭብጨባ ያንሰዋል የሚያስብል ነው፡፡ በቤተ ክርሰቲያን ያለው ሕዝብ በገባውም ባልገባውም እንዲያጨበጭብ አጨብጭቡ እንጂ አያልን ሕዝባችንን እንዲያው አጭብጫቢ አድርገነዋል፣ ያንን ይዘን ደግሞ ወደ ሌሎች አደባባይ እየሄድን ነው፡፡ አጨብጫቢዎች ሲከተሉአቸው ደስ የሚላቸው መሪዎች ለስህተት የተጋለጡ ናቸው፡፡ ወንጌላዊ ያሬድም ለሚያጨበጭቡ ብቻ ከመናገር እልፍ እንዲል ይጠበቅበታል፡፡ ማርቲን ሉተር ኪንግ  ለውጥ ያመጡት ፍትህ ተጓደለ ወደተባለው ሥፍራ ሁሉ በመንቀሳቀስ በአደባባይ  የመንግሥት አመራር አካላትን ወታደሮቻቸውን ጭምሮ ከ25000 በላይ ሕዝብ በአንድ መቀመጥ የሚያደምጡትን  ንግግር በማድረግ ነው፡፡  በአጭብጫቢው ፊት በተዘጋ ቤት ውስጥ ብቻ ተናግሮ ቢሆን ኖሮ ተደብቆ ድንጋይ የመወርወር፣ በጨለማም የማፍጠጥ ያህል ብቻ ሆኖ በቀረበት ነበር፡፡ ወንጌላዊ ያሬድም  እልፍ ማለት ይገባዋል ባይ ነኝ፡፡ ሁሉም እኮ በየቦታው እንደዚያ ይናገራል፡፡ ለምሳሌ ወንጌላዊ ዳንኤል ጣሰውም እኮ በአንድ ቦታ ንግግር አድርጓል፣ እርሱም ያራገበለት የለም እንጂ፡፡ እርሱ እንዲያውም ሕዝብ ለሰላማዊ ሰልፍ ከመውጣቱ በፊት ነው ይናገር የነበረው፡፡   ወንጌላዊ ያሬድ  እንደ መካለለኛ nutral ሰው ሳይሆን እንደ ፓለቲካኛና እንደ መንግሥት ተቃዋሚ ሰው ነው የተናገረው፡፡ ይህ ደግሞ ከአንድ ወገን ብቻ እንዲደመጥ ያደርገዋል፡፡ ያንን ንግግር ለተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎችና አንድ ጥግ ለያዙ ሰዎች ብቻ ሳይሆን ለመንግስትም መናገር ነበረበት፡፡ መንግሥት ይህን ሰምቶ የለውጥ ርምጃ ወሰደ አልወሰደ መንግሥትን ማሰማት ይገባል፡፡ ሁለተኛ የእግዚአብሔርን ቃል ያለቦታው መጥቀሱ አግባብ አይደለም፡፡ ይህ ቤተ ክርስቲያን ሰባኪዎቿ  አጥብቃ የሚታሳስበውና የምትወተውተው ግን ሊታረም ያልቻለ ድክመታችን ነው፡፡ ቃሉን ከሚገጥመው አሳብ ጋር ካላዘመድነው አድማጩን እናሳስተዋለን፡፡ የእግዚአብሔር ቃል  አማኞች የአንድ አካል ብልቶች፣ ቤተ ክርሰቲያንም የክርሰቶስ የአካል ብልት እንደሆነች ይናገራል፡፡ ይህን ትምህርት ግን አገርና የአገር ሕዝቦች የአንድ አካል እንደሆኑ ለማስተማር መጠቀም ቃሉን እየቦጨቁ ያለቦታው መደረት ይሆናል፡፡ የሕዝቦች አንድነት ለማሳየትና ለመስበክ ከተፈለገ ሌላ ክፍል መምረጥ ይቻል የለምን? “ባሪያ በነገሠ ጊዜ ሰነፍም እንጀራን በጠገበ ጊዜ የተጠላች ገጊዜ ምድር ትናወጣለች” /መጽሐፈ ምሳ 30፡21-22/ የሚለውን የጠቢቡ ሰለሞንን ምሳሌ የጠቀሙ ራሱ በጣም ወጣ ያለ ነው፡፡ እነዚህን መጠቀማቸውን ስናይ የመጽሐፍ ቅዱስ ክፍሎች ያለ ቦታቸው የተለጠፉ ናቸውና ይታሰብበት ለማለት ነው፡፡
ለወደፊትም ቢሆን ለብዙ ዘመናት በአገልጋይነት ቆይቻለሁ፣ ሰባኪ፣ ወንጌላዊ ቄስ ወዘተ ነኝ እያልን ፖለቲካውን ደግሞ መነካካት ስንጀምር ቀጣዩንም ውስብስብ መንገድ ለመጓዝ ቆራጥነትን እንደሚስፈልግ ስለማሰቡ የእኔ ምክር ከሚያስፈልጋቸው ልክ በላይ የላቁ አገልጋዮች ስላሉን በዚሁ ላቁምና አሳቤን ልቋጭ፡፡ የገብሷን እሸት ከመብላት በፊት በደንብ ማሸት፣ ያለዚያ ሳሉ አያስተኛምና እንዲሉ በአንድ ነገር ውስጥ ከመግባት በፊት ማሰብ ፣ የሚያስከፍለውንም ዋጋ መተመን የሚያሻ ይመስለኛል፡፡  ስለዚህ ቤተ ክርስቲያን በፖለቲካ ትሳተፍ ስንል ብቅ ብለው ጥፍት የሚሉ ፣ ነገር ሲሞቅ የሚግሉ፣ ገና ሊበርድ ሲል ደግሞ ቀድመው ወደበረዶነት የሚቀየሩ ሳይሆን በእርግጥ ዋጋ ከፍዬ ለሕዝቤና ለምድሬ ለውጥ አመጣለሁ የሚሉ የቁርጥ ቀን ልጆች ሊኖሩአት እንደሚያስፈልግ እናስምርበት፡፡
       

      



እግዚአብሔር ሲገለጥ

                                                                                                     ከመጋቢ ሳሙኤል ሾንጋ 

መገለጥ የሚለውን አሳብ የምንረዳበትና ለቃሉ የምንሰጠው ፊቺ እንደየሰው ሲለያይ ይስተዋላል፡፡ ይሁን እንጂ መገለጥ ማለት አንድ ተደብቆና ተሸፍኖ የቆየ ነገር በግልጽ የሚታይበት ሂደት ነው፡፡ ለምሳሌ በመጋረጃ የተሸፈነ አንድ ነገር ለሰው ሁሉ ሊታይ በሚችልበት ሁኔታ የመጋረጃው ሽፋን ተነስቶ ግልጥ ሲል ነገሩ ተገለጠ እንለዋለን፡፡  ወይም መኖሩ በማይታወቅና በማይታይበት ቦታና ሁኔታ የነበረ ወይም የኖረ አንድ ነገር በድንገት ወደ እይታ ሲመጣ መገለጥ ሆነ ማለት ነው፡፡ በክረምት ጥቁር ደመና የተሸፈነችውና ከሰው ሁሉ እይታ የተሰውረችው ፀሐይ ባልተጠበቀ ሰዓት ደማናው ሲገፈፍ ሙሉ በሙሉ ግልጥ ብላ ለሁሉ ትታያለች፡፡ ያነ ፀሐይ ተገለጠች እንላለን፡፡ ይህ በመጠኑም ቢሆን የመገለጥን  ሂደት ሊያስረዳን የሚችል ነው፡፡
የእግዚአብሔርን ቃል በምንመለከትበት ወቅት ትልቁ መገለጥ እግዚአብሔር ራሱን ለሰው ልጅ የገለጠበት መንገድ ነው፡፡ ይህ መገለጥ ሪቨሌሺን ተብሎ የሚጠራ ሲሆን ሪቬላቲዮ ከተባለው የላቲን ቃል ጋር ተዛማጅነት እንዳለው ብዙዎች ይስማማሉ፡፡ የቅዱሳት መጻሕፍት አስተማሪዎች እግዚአብሔር ራሱን ለሰው የገለጠበትን መንገድ አስመልክተው አራት  የመገለጥ ዓይነቶች እንዳሉ ይናገራሉ፡፡ አንደኛው አጠቃላይ መገለጥ( General Revelation) ሲሆን ይህ እግዚአብሔር ራሱን በፍጥረተ- ዓለምና በታሪክ የገለጠበት መንገድ ነው፡፡ ሁለተኛው ልዩ መገለጥ(Special Revelation) የተባለው ሲሆን እግዚአብሔር በቅዱሳት መጻሕፍትና በልጁ በኢየሱስ በኩል ራሱን የገለጠበት ሆኖ የሰውን ልጆች ወደ ደህንነት የሚያመራ ነው፡፡ ሦስተኛው ሂደታዊ  መገለጥ ( Progressive Revelation) ነው፡፡ ይህ ዓይነቱ መገለጥ እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳን የገባው ተስፋ ወይም ሊያደርገው የጀመረው ነገር ደረጃ በደረጃና በሂደት እየተከናወነና ይበልጡንም ግልጽ እየሆነ እስከ አዲስ ኪዳን የዘለቀበት ሂደት ነው፡፡ አራተኛው እግዚአብሔር በአንድ ሰው ሕይወት በግሉ የሚገለጥበት ፣ያንን ሰው በተለየ መልኩ ለዓላማው የሚጠራበት፣  በሁኔታው ላይ ጣልቃ የሚገባበትና፣ ያንን ግለሰብ በገጠመው የህይወት ተሞክሮ ውስጥ ተገኝቶ የሚናገርበት ፣ የሚያጽናናበት ወይም የሚመራበትና የሚረዳበት የመገለጥ ዓይነት ሲሆን ይህኛው  ግላዊ መገለጥ ( Personal Revelation) በመባል የሚታወቅ ነው፡፡
 በአራቱም የመገለጥ ዓይነቶች ዙሪያ አንድ ሁለት እያልን ብናወጋ ማለፊያ በሆነ ነበር ግን የዚህ ገጽ ውስንነት ስለማያላውሰን በአራተኛው የመገለጥ ዓይነት ብቻ እናተኩር፡፡ በሕይወታችን እግዚአብሔር መገለጡ እጅግ አስፈላጊ ነገር ነው፡፡ እርሱ ሲገለጥ ሕይወታቸንን ይቀይረዋል፡፡ እኛም እርሱ የተገለጠልንን ቀን ልንረሳው አንችልም፣ ሁኔታውም በፍጹም ከአእምሮአችን አይጠፋም፡፡ እግዚአብሔር ሰውን ሲፈልገው በግሉ ይገለጥለታል፣ ዓላማውንም ያሳውቀዋል፡፡ ክርስትናንም ልዩ የሚያደርገው በእግዚአብሔር መገለጥና በእርሱ መታየት ላይ የሚያተኩር መሆኑ ነው፡፡  እግዚአብሔርን በግላቸው የተረዱት ሰዎች በመንፈሳዊ አኗኗራቸው ከሌሎች ይለያሉ፡፡ ሐዋሪያው ጳውሎስ ጌታ በግሉ ተገልጦለት ስላየመከራን እንኳ ቢቀበልም ከክርስቶስ መለየትና ከሰማይም ለተገለጠለት ራዕይ እምቢ ማለት አልቻለም( ሐዋ 9፣ ገላትያ፣2ኛ ቆሮ 12) ፡፡ በእርሱ ዘመን ክርስቶስን ለመከተል የወሰኑ ግን በትንሽ መከራ ወይም በመጠነኛ ድሎት ምክንያት ከመንገዳቸው የተመለሱ ብዙዎች ነበሩ፡፡  ለዚህም የገላትያ መጽሐፍ ምዕራፍ 3  እንደሚነግረን የዴማስ ሕይወት አንዱ ማሳያ ነው፡፡ ጳውሎስን ግን ኢየሱስን የሙጥኝ ያለው፣ ሰይፍም ቢሆን ሞት፣ ስደት ቢሆን ረሀብ፣ ከፍታ ቢሆን ዝቅታ፣ ልዩ ፍጥረትም ቢሆን ያለውና የሚመጣ ሁሉ በክርስቶስ ኢየሱስ ካለኝ ከእግዚአብሔር ፍቅር ሊለየኝ እንዳይችል ተረድቻለሁ(ሮሜ 8፡39) እንዲል ያደረገው በሕይወቱ የታየው የእግዚአብሔር መገለጥ ነው፡፡
አንዳንድ ጊዜ በቤተ ክርስቲያንና በቤተሰብ ውስጥ አብረውን ያሉ ልጆቻችን ወይም የትዳር ጓደኞቻችን ወይም የቤተ ክርስቲያን አባላት ለጌታ የተሰጡ እንዲሆኑ እንጎተጉታቸዋለን፡፡  በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዲቀጣጠሉ ጌታንም የሙጥኝ እንዲሉት እንጨቀጭቃቸዋለን፡፡ አንዳንዶቹ ወዲያውኑ የሚገርም ለውጥ ሲያመጡ አንዳንዶቹ ደግሞ ስለ መንፈሳዊ ነገር ግድ የሌላቸው ይሆናሉ፡፡ የአገልጋዮች ግፍት ወይም የቤተሰብ ጉትጎታ ሰዎችን ይሉኝታ ያስይዛቸው ወይም ደንደሳም ሃይማኖተኛ ያደርጋቸው እንደሆነ ነው እንጂ ከጌታ ጋር አያጣብቃቸውም፡፡ እግዚአብሔር በሕይወታቸው የተገለጠላቸው ሰዎች ግን የማንንም ግፍት አይፈልጉም፡፡ ሲነገራቸው እንኳ የሰማሪያ ሰዎች “የምናምነው ስለ ቃላችሁ ሳይሆን እኛ ራሳችን ሰምተነዋል እርሱ መድኃኒት እንደሆነ አውቀናል” ማለት ይጀምራሉ( ዮሐ 4፡42)፡፡ ሰዎች ጌታን እንዲወዱትና እንዲያመልኩት ከማበረታታት ጎን እግዚአብሔር እንዲገለጥላቸው መጸለይ የበለጠ ነገር ነው፡፡ 
 በእግዚአብሔርን ቃል በሁለቱም ኪዳናት ስንመለከት ጌታ በግላቸው ተገልጦላቸው ሕይወታቸውን ከለወጠላቸው  ሰዎች  የምማረው ብዙ ነገር አለ፡፡ በእነርሱ ብቻ ሳይሆን በሕይወታችንም ጌታ ሲገለጥ የሚያመጣው ለውጥና ልዩነት እንዳለ በእርግጥ የታመነ ነው፡፡
·      እግዚአብሔር በሰው ሕይወት ተገልጦ ምድረ በዳን ቤተ መቅደስ አድርጓል( ዘፍጥረት 21፡10-21፣ 28፡ 10-19)
የምድረ በዳ ሕይወት እጅግ አሳዛኝ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ቃል እንደሚናገር ምድረ በዳ ሰው የሌለበት ፣ እንጨት ወይም ጥላ የማታይበት፣ ውሃ የሚባል ነገርማ በፍጹም የማይገኝበት ነገር ግን ከድንጋይና ከአሸዋ ሌላ፣ እባብና ግንጥ የሚተራመስበት ደረቅና የተቃጠለ የምድር ክፍል ነው (መዝ 63፡1)  ያዕቆብ ያንን የምድረ በዳ ሕይወት ተለማምዶታል፡፡ እግዚአብሔርም በምድረ በዳ ሕይወቱ ሲገለጥ አይቶታል፡፡  በእንዲህ ዓይነቱ ሕይወት እግዚአብሔር ሲገለጥ፣ ወይም ሲታይ ፣ ወይም ድምጹን ሲያሰማ እንዴት ያማረ ነው! እንዴትስ ያለ እረፍት የሚሰጥ ነው! በምድረ በዳው ሕይወት እግዚአብሔር ሲገለጥ!
ያዕቆብ ከወንድሙ ጦር ሸሽቶ  ላባና ባቱኤል የተባሉ አጎቶቹ ወዳሉበት አገር ሲሄድ ከቤርሳቤህ ምድረበዳ  ተነስቶ ወደ አንድ ሥፍራ ሲደርስ ፀሐይ ጠለቀችበት ማለትም ቀኑ መሸበትና ሌሊቱ ገባ፡፡ አይቶት የማያውቀው አደገኛ ምድር፣  ያውም ምድረ በዳ ሆኖ ጊዜው ሌሊት አስፈሪም ጨለማ የጋረደበት ጊዜ፡፡ ይህ አስጨናቂ  የሕይወት ተሞክሮ ነው፡፡ የሚያስደስተው ግን እግዚአብሔር በዚህ ሁኔታ ለያዕቆብ ለመጀመሪያ ጊዜ ተገለጠለት፡፡ እናቱና አባቱ ሲመሰክሩ በጆሮው ብቻ ሲሰማ የነበረው ያዕቆብ የአባቱንና የአያቱን የቃል ኪዳን አምላክ በአይኑ ያየው ለመጀመሪያ ጊዜ በዚህ ምድረ በዳ ነው፡፡ በዚያ በሌሊት የድንጋይን ቋጥኝ ተንተርሶ በተኛበት አስፈሪ ስፍራ አምላኩ ተገለጠለት፡፡
መሰላል ከምድር እስከ ሰማይ ተዘርገቶ ቅዱሳት መላእክት ሲወጡበትና ሲወርዱበት  ሲያይ ቦታው ምድረ በዳ መሆኑን ሳይረሳው እንደማይቀር  ምንም ጥርጥር የለውም፡፡ መሰላል በእግዚአብሔርና በባሪያው መካከል ሲላለው እውነተኛና የማይበላሸ ው ሕብረት ምሳሌ ነው፡፡ መላእክቱ ደግሞ በምድረ በዳ ያለቺው ነፍስ የእግዚአብሔርን ርዳታ እንዲታገኝ የሚያግዙ የእግዚአብሔር አገልጋዮች አብረው መኖራቸውን የሚመለክት ነው፡፡ ምስኪኑና  ረዳት የሌለው ያዕቆብ በተኛበት ሥፍራ ከተተከለው መሰላል በላይ የተገለጠው ያህዌ የተባለው የአባቶቹ አምላክ እግዚአብሔር ማንነቱንና ለእርሱ ያለው ዓላማ በቃላት አስረዳው፡፡ በዚያ ምልክት እንኳ ማሳየት በማይቻልበት ፣አቅጣጫውን መለየት በማይታሰብበት ጭው ባለው ምድረ በዳ አምላክ ተገለጠለት ማለት ነው፡፡  ያዕቆብም እግዚአብሔር የተናገረውን የተስፋ ቃል ሁሉ ከሰማ በኋላ “ይህ ሥፍራ እንዴት ያስፈራል፡፡ ይህ የእግዚአብሔር ቤት ነው እንጂ ሌላ አይደለም ፣ ይህም የሰማይ ደጅ ነው” አለ፡፡ ለዚህ ነው እግዚአብሔር በሰው ሕይወት ሲገለጥ ምድረ በዳውን ቤተ መቅደስ ያደርጋል ያልኩት፡፡ ያውም መላእክት አምልኮን ሲያጅቡ በግልጥ የሚታይበት ድንቅ ቤተ መቅደስ!
·         እግዚአብሔር በሰው ሕይወት ተገልጦ በምድረ በዳ ምንጭን አዘጋጅቷል (ዘፍ 21፡8-21)፡፡
እግዚአብሔር በምድረ በዳ ከተገለጠላቸው ሰዎች ታሪከ የአጋር ሕይወት አንዱ ነው፡፡  አጋር ለአብራሃም የወለደቺው ልጅ ሲሰቅ ያየች ሣራ የባሪያይቱ ልጅ ከይስሐቅ ጋር አይውርስምና ከልጇ ጋር እንዲያባርራት በፈቀደች ጊዜ አብርሃም አቁማዳ ሙሉ ውሃ አሸክሞአት ከነልጀዋ ከቤት አስወጣት ፡፡ እነርሱ በነበሩበት የጥንት ባህል የቁባት ልጅ እናቱን እንጂ አባቱን ስለማይወርስ ( መሳፍንት 9፡1-3) አብርሃም ከነልጇ ከቤቱ አስወጣት፡፡ አጋርም የመከራከር መብት ስላልነበራትና ዳኛም ስለማታገኝ  እርሱ ያሸከማትን እንጀራ ( ዳቦ ማለት ነው፣) የውሃ አቁማዳና ልጇን ተሸክማ ወጣች፡፡ አቁማዳ ማለት ከከብት ቆዳ የሚሠራ እንደ ከረጢት ያለ ነገር ሆኖ እንደነ ውሃ ፣ ዘይትና የወይንን ጠጅ የመሳሰሉት ፈሳሽ ነገሮችን የሚይዙበት ስልቻ ሲሆን በአብዛኛው በሰው ትከሻ ሳይሆን በአህያ ወይም በሌላ ከብት የሚጫን ከበድ ያለ ነገር ነው፡፡  አብርሃም ለመንገዷ እንዲሆንላት ካሸከማት ጓዝ ውስጥ ይህ አቁማዳ የተባለ ንቅንቅ የማይል ነገር አለበት፡፡ እርሷም ይህን ሁሉ ተሸክማ  የት እንደምትሄድ ሳታውቅ  እየተቅበዘበዘች ቤርሳቤህ ወደሚባል ምድረ በዳ ስትደርስ አብርሃም የሰጣት ውሃ ከአቁማዳዋ  አለቀባት፡፡ የሰው ውሃ ያልቃልና፣ ሲያልቅም በምድረበዳ ነውና የአጋርና የልጇ  ሕይወት አደጋ ላይ ወደቀ፡፡ በተለይም ልጇ በሞትና በሕይወት መካከል ሲሆን ሞቱን በዓይኗ  ላለማየት ስትል ጥላው መሄድ ነበረባትና ርቃ ሄደች፡፡ የጭንቅ ጊዜ፣ የምድረበዳ ሕይወት ማለት እንግዲህ ይህን የሚመስል ነው፡፡ ልጇ ቢጮኽም ጩኸቱ በውስጡ እንጂ ቃሉን ለማሰማት አቅም አንሶታል፡፡ ከምድረ በዳ ቃጠሎ የተነሳ ደክሞት ተዝለፍልፎ ሊሆን ይችላል፡፡ እግዚአብሔር ግን በዚህ ሁኔታ የልጁን ጩኸት ሰማ ፣ የእናቲቱንም ጭንቅ ተመለከተ፡፡ በምድረ በዳው ተገልጦላቸው አጋር የውሃ ምንጭ እንዲታይ አይኗን ከፈተላት፡፡ እግዚአብሔር በሰው ሕይወት ሲገለጥ በምድረ በዳ ምንጭን ይሰጣል ይሏል ይህ ነው፡፡ ይህ መገለጥ እንግዲህ ለአጋር ለብቻዋ የታየ፣ በእርሷና በአምላኳ መካከል የተከናወነ የሕይወቷ ተሞክሮ ነው፡፡ ይህንን አብርሃም አያውቀውም፣ ለሣራም አልታያትም፡፡ ለአጋር ብቻ የሆነላት መገለጥ ነው ምክንያቱም ያለችበትን የምድረበዳ አስከፊ ሕይወት የምታውቀው እርሷና እርሷ ብቻ ናትና፡፡ ይህ ዛሬ የምድረ በዳ ሕይወታቸውን ብቻቸው እየተጋፈጡ ላሉት ወገኖች ትልቅ መልእክት ነው፡፡ አብርሃም ለአጋር እንደባሏ ፣ ለልጁ እንደ አባቱ ያደረገላቸው  ርዳታ ቢኖር ከቤት ሲወጡ ውሃና እንጀራ መስጠት ነው፡፡ ያ ግን ጊዜያዊና በምድረ በዳ የሚያልቅ ነበር፡፡ የእግዚአብሔር መገለጥ ያመጣላት መፍትሔ ግን ከአብርሃም አቁማዳ በላይ ሆነውን  ነው፡፡ ሰው የሚሰጠው ውሃ በምድረበዳ ቢያልቅ በእግዚአብሔር እንታመን ምክንያቱም እርሱ ውሃው ያለቀበትን አቁማዳ ሳይሆን የማያልቀውን ምንጭ የምናይበትን ዓይን ይከፍቶ ይሰጠናልና፡፡ 
ጌታ ኢየሱስ በምድረ በዳ ተፈትኗል፡፡ በምድረ በዳው ሳይረታ ሰይጣንን በሥልጣናዊ ቃሉ አሸንፏል፡፡ ዛሬም የሞተላቸው ውድ ባሪዎቹ ነፍስ በምድረ በዳ ስትቅበዘበዝና ስትጮኽ ተገልጦ ሕይወታቸውን በመለወጥ በተስፋ ቃሉ መጽናናትን ይሰጣቸዋል፡፡  ሕይወቴ ምድረ በዳ ሆነብኝ ለምትል ነፍስ  መኖሩን ያሳያታል፡፡ ያኔ ተንከራታቹ እረፍት፣ ተቅበዝባዡ እፎይታን ያገኛል፣ ሚስክኑም በክንዱ ተደግፎ ከምድረ በዳው ይወጣል፡፡ ኑሮዬ፣ ትዳሬ፣ አገልግሎቴ ምድረ በዳ ሆነብኝ ለምትል ነፍስ ሁሉ እርሱ ፈጥኖ ይደርስላታል፡፡
·         እግዚአብሔር በሰው ሕይወት ተገልጦ በእሥር ቤት መውጪያን አዘጋጅቷል(ሐዋ 12 ፡-12)
እግዚአብሔር በአስር ቤት ተገልጦ እስረኛውን ከእሥር አስመልጧል፡፡ ንጉሥ ሄሮዲስ የጌታን ሐዋሪያ ያዕቆብን በሰይፍ ከገደለው በኋላ ድርጊቱ የአይሁድን ሕዝብ ደስ ስላሰኛቸው ጴጥሮስን ጨምሮ ያዘው፡፡ ጴጥሮስም እንደ ያዕቆብ ከደቀመዛሙርት መካከል  እንደ አእማድ የሚታይ ስለሆነ በአይሁዶች ዘንድ የእርሱ መታሠር ብቻ ሰይሆን መገደል ራሱ ለንጉሡ ትልቅ አክብሮትን ሊያሰገኝለት የሚችል ነው፡፡  ይህ ጊዜ በኢሩሳሌም ውስጥ ያሉ አማኞች ከአይሁዶች ብቻ ሳይሆን ከንጉሥ ሔሮድስ ጭምር ከፍተኛ መከራና  ስደት የሚቀበሉበት ጊዜ ነበር፡፡ በዚህን ጊዜ ጴጥሮስ በጥብቅ እስራት ተደርጎበት እያዳንዳቸው አራት ጭፍራ ባለበት በአራት ግሩፕ ወታደሮች ይጠበቅ ነበር፡፡ በሰንሰለት ታሰሯል፣ያውም በሁለት ሰንሰለት፡፡ የእሥር ቤቱም ደጆች በሙሉ በጥንቃቄ ተዘግተዋል፡፡ ነገር ግን ቤተ ክርስቲያን መለኮታዊ የሆነ የጦር መሣሪያ ስነበራት ያንን ትጠቀምበት ጀመረች፡፡ እርሱ “ጥብቅ ጸሎት” ይባላል፡፡ ያን መሣሪያ ተጠቅማ በእግዚአብሔር ፊት ጥብቅ  የሆነ ጸሎት ስታደርግ እግዚብሔር የወህኒ ቤቱን አልፎ ተገለጠ፡፡
ሄሮድስም ሊያወጣው ባሰበ ጊዜ፥ በዚያች ሌሊት ጴጥሮስ በሁለት ሰንሰለት ታስሮ ከሁለት ወታደሮች መካከል ተኝቶ ነበር፤ ጠባቂዎችም በደጁ ፊት ሆነው ወኅኒውን ይጠብቁ ነበር።እነሆም፥ የጌታ መልአክ ቀረበ በቤትም ውስጥ ብርሃን በራ፤ ጴጥሮስንም ጎድኑን መትቶ አነቃውና። ፈጥነህ ተነሣ አለው። ሰንሰለቶቹም ከእጁ ወደቁ። መልአኩም ታጠቅና ጫማህን አግባ አለው፥ እንዲሁም አደረገ።ልብስህንም ልበስና ተከተለኝ አለው። ወጥቶም ተከተለው፤ ራእይንም የሚያይ ይመስለው ነበር እንጂ በመልአኩ የሚደረገው ነገር እውነት እንደ ሆነ አላወቀም።የመጀመሪያውንና የሁለተኛውንም ዘብ አልፈው ወደ ከተማ ወደሚያወጣው ወደ ብረቱ መዝጊያ ደረሱ፤ እርሱም አውቆ ተከፈተላቸው፤ ወጥተውም አንዲት ስላች አለፉ ወዲያውም መልአኩ ከእርሱ ተለየ። ጴጥሮስም ወደ ልቡ ተመልሶ፦ ጌታ መልአኩን ልኮ ከሄሮድስ እጅና የአይሁድ ሕዝብ ይጠብቁት ከነበረው ሁሉ እንደ አዳነኝ አሁን በእውነት አወቅሁ አለ( ሐዋ 12፡1-11)።
 በጊዜው በክርስቲያኖች ላይ የሚደርሰው ስደት ከሃይማኖታዊ ወደ ፖለቲካዊ እንድምታ መሸጋገር የጀመረበት ሁኔታ ነበር፡፡በሐዋሪያት ሥራ 12 ላይ የምናነበው ስደት ከምንም ሁኔታ ወይም ከማንም ተነስቶ ሳይሆን ንጉሡ ሄሮዲስ በአይሁዶች ፊት ሙገሳንና ዝናን ለማግኘት ሲል ብቻ ያስነሳው ስደት ነበር፡፡ የያዕቆብ አንገት በሰይፍ ስለት መቀላቱ አይሁዶችን ሲያስፈነጥዛቸው ማየት ለሄሮዲስ ሌሎችንም ጨምሮ እንዲቀላ ወኔውን ቀሰቀሰለት፡፡ ስለዚህ ቀንደኛ የሆነውን ሐዋሪያ መግደል የተለየ ስሜት የሚፈጥር እንደሆነ ስለገመተ ጴጥሮስን ወደ ወህኒ አስገባው፡፡ ሔሮዲስ ጴጥሮስን ቢይዘውም ግን ፍርሃት እንዳለበት የሚያሳየው ለጥበቃ የተመደበው የወታደሩ ብዛት፣ የሰንሰለቱ ብርታት( አንድ ሊበቃው ሲችል በሁለት ሰንሰለት መታሠሩ)፣የብረት መዝግያውን ጨምሮ በአራት በሮች የሚዘጋ ወህኒ ቤት መሆኑ ራሱ የንጉሠ ነገሥቱን በራስ አለመተማመንና ክርስቲያኖች ተጽዕኖ አሳዳሪዎች መሆናቸው የሚያስረዳ ነው፡፡ ንጉሡ መፍራቱና እሥራቱን ማጥበቁ በሱ ቤት ተገቢ ነው ምክንያቱም በተለያዩ ጊዜያቶች ተይዞ ወደ ወሂኒ ቤት ሲጣል የወህኒው ደጆች እየተከፈቱ ከወጡት እሥረኞች አንዱ ይኸው ጴጥሮስ ነው፡፡  ስለዚህ እንዳያመልጥ በሚል 16 ወታደሮች በ4 ጭፍራ ሆን እዲጠብቁና ፣ እያንዳንዱ በር ጠንካራ መዝግያ የተጠመለት እንዲሆን አደረገ፡፡ ከውህኒ የማምለጡ ሂደት በሰው ኃይል የሚሆን ስለመሰለው ነው፡፡ ጴጥሮስ ግን በሁለት ሰንሰለት ታሥሮ በሁለት ወታደሮች መካል መካከል ተኝቶ ነበር፡፡ ትናንትና የያዕቆብ አንገት መቀላቱን ካየ በኋላ አሁን እንቅልፉን የሚለጥጠው እርሱ የማይቀላበት ምን ምክንያት ይኖራል ብሎ ነው ያስብላል፡፡ አገልግሎቴን ጭርሻለሁ ብሎ ነው? ልጅ እንዳለው ባናውቅም ቢያንስ ሚስት እንዳው በቃሉ ተነግሯልና ስለ ትዳር ጓደኛው እንኳ አያሳስበውም የሚያስብል ነው፡፡  ከእግዚአብሔር ቃል እንደምንረዳው ጴጥሮስ በእንዲህ ባለ ሁኔታ ውስጥ ገብቶም ቢሆን እንቅልፉን የተኛት ምክንያት አለው፡፡ አንደኛው ገና ኢየሱስ በምድር በነበረበት ወቅት በዕድሜው እስከ እርጅና እንደሚኖር ነግሮታል( ዮሐ 21፡18)፡፡ ስለዚህ የሚመጣበትን መከራ ሳያስብ አስጨናቂ በሚመስሉ ሁኔታው ውስጥ ያለፍርሃት የተኛ ነበር፡፡ እርሱ ቢተኛም የሄሮዲስ እቅድ በያዕቆብ እንዳደረገው የእርሱንም አንገት መቅላት ወይም በአይሁዶች ፊት በእንጨት መንጠልጠል፡፡ ነገሩ አልታወቀም ግን ይፋ የሚሆነው ሌሊቱ ሲነጋ ነው፡፡ በዚህ ሁኔታ እያለ ነው እንግዲህ ከላይ እንዳነበብነው የእግዚአብሔር መልአክ በወህኒ ቤት ውስጥ የተገለጠው፡፡ ሰንሰለቱም ከጴጥሮስ እጅ የወደቀው፣ የነሐሱ ደጅ ያለ ቁልፍ ተከፈተው፡፡ በቤተ ክርስያን የሚደረገውን ጥብቅ ጸሎት የሰማው እግዚአብሔር በአደገኛ ሁኔታ ታስሮ ተስፋ ላጣው ሰው እሥራቱን ሲበጥስለት ጠላቱንም መና ሲስቀረው እናያለን፡፡ ይህ የእግዚአብሔርን ሉዓላዊ ጣልቃ ገብነትን የሚያሳይ ነው፡፡ እግዚአብሔር በአስቸጋሪ ነገሮቻችን ጣልቃ ሲገባ  እንዴት ያለ መልስ እንደሚሰጥ ከዚህ ክፍል መረዳት ይቸላል፡፡

እግዚአብሔር በእኛ ሕይወት የሚገለጠው አንድ ጊዜ ብቻ ሰሳይ በተደጋጋሚ ፣ ሁል ጊዜም ነው፡፡ እኛ የእርሱን ርዳታ በምንፈለግበት ወቅት ወይም እርሱ ራሱ ለዓማው እኛን በሚፈልገን ጊዜ ሁሉ በሕይወታችን ይገለጣል፡፡ ትላንት ተገለጥኩላችሁ አይበቃችሁምን ያዕቆብ በረከትን ለማግኘት ሲል  ወንድሙን አታሏል የፈለገውንም በረከት አግኝቷል ግን ያ በማጭበርበር ያገኘው በረከት ሙሉና  የሚያሳርፈው  አልነበረም፡፡ በማጭበርበር የሚመጣ በረከት ለመንከራተት ይዳርጋል፡፡ እግዚአብሔር ተገልጦ የሚሰጠው የሚሰጠው በረከት ግን ያሳርፋል፣ባለጠጋም ያደርጋል፡፡ የእርስ በረከት እውነተኛ በረከት ነው፡፡
የሰው ሕይወት ደግሞ በየዕለቱ ለውጥና ተሃዲሶን የሚፈልግ ነው፡፡ የእኛ ሕይወት ትርጉም ያለው የሚሆነው የተለወጠ እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ እግዚአብሔርም በተለወጠ ማንነት መሥራት ደስ ይለዋል፡፡ እግዚአብሔር የያዕቆብን ስም ሲቀረው እንመለከታለን፡፡ ይህ ማለት የያዕቆብ የሁለንተናው መቀየርን የሚያመለክት ነው፡፡ ስሙን ቀየረ ማለት ሁለመናውን ቀየረ ማለት ነው፡፡ ዛሬ እኛ የእግዚአብሔርን መገለጥ የምንፈልገው ለምን እንደሆነ ራሳችንን መመልከት ይኖርብናል፡፡ ሕይወታችን እንዲለውጥ ብለን የእርሱን መገለጥ ልንጠባበቅ ይገባናል፡፡ እግዚአብሔር ሲገለጥ ከጓዳ እስከ የአደባባይ ሕይወታችን ድረስ ይቀየራል፡፡ የአምልኮ ሕይወታችን ይቀየራል፣ ዝማሬው ሁሉ ይቀየራል ፣ አኗኗራችንና አካሄዳችን ሁሉ ይቀይራል፡፡ እነሲሳያስ፣ እነቂስ ልጅ ሳዖል፣ የመሳሰሉት የተቀየሩት እግዚአብሔርን ስላዩ ነው፡፡ ስለዚህ በግል፣ በቤተሰብና በቤተክርስቲያን  ሕይወታችን የሚያስፈልገን የእግዚአብሔር መገለጥ ነው፡፡ በምድራችን መለኮታዊ መገለጥ ሲሆን እገዚአብሔርን ያየ ሁሉ ይከተለዋል ይሰግድለታልም፡፡ እግዚብሔርም ፊት ለፊት አየሁት ሰውነቴም ድና ቀረች ማለት ይጀምራል፡፡ እግዚብሔር ተገልጦ ሲነካ የሚሰብረው የአካል ክፍል እያለም የሚሰማን ግን ፈውስና ደህንነት ስሆነ ሰውነቴ ድናለች ማለት እንጀምራለን፡፡ ሁለንተናዊ ፈውስ የሚሆነው እግዚአብሔር ሲገለጥ ነው፡፡ የኢየሩሳሌም አማኞች አጥብቀው በመጸለያቸው የእግዚአብሔርን ጣልቃ ገብነት እነዳዩት ሁሉ እኛ ዛሬ ከምንመ በላይ ስለ እግዚአብሔር መገለጥ አጥብቀን መጮኽ ይኖርብናል፡፡ እግዚአብሔር ሲገለጥ!