Monday, March 19, 2018

ንቅስ ያለ የልብ ሰው ይሁንላችሁ፡፡

   ንቅስ ያለ የልብ ሰው ይሁንላችሁ፡፡



I. መግቢያ
ቆንጅናና ውበት በምን ይለካል? በጥቁረት ወይ በቅላት? በውፍረት ወይስ በቅጥነት? በርዝመት ወይስ በእጥረት? ውበት በእርግጥ ውበት የሚሆነው እንዴት ነው? እኔ እንደምረዳው ለቁንጅና የሚሰጠው ብያኔ እንደየሰው አተያይ ይለያያል፡፡ ለአንዱ ምድር ፊት የሆነ ፉንጋ የተባለ ለሌላው ታይቶ የማይጠገብ የዓይን ምሳ ነው፡፡ ለአንዱ እራሪ -ድንኪዬ የተባለ ለሌላው ጌጥ ፣ ለአንዱ ሸበላ ሲባል የኖረ ወደ ሌሎች ጋ ሲደርስ ፊታቸውን ሊያዙበት ሁላ ይችላሉ፡፡ ክብ ፊት የላቸውን ሰዎች የሚወድዱ እንዳሉ ሁሉ ረዘም ያለና ሾጣጣ ፊት የሚማርካቸው ብዙ ናቸው፡፡ የረዘመ አፍንጫ ያለውን ሰው ሰልካካ ብንለውም አፍንጫ ቢርዝም ማር አይቆርጥ የሚሉ ያዚያኑ ያህል ናቸው፣ እንዲያውም የተጠረበ እንጨት የሚመስላቸውም አይታጡም፡፡ ታዲያ ውበትና ቁንጂና የቱጋ ናቸው? በአገራችን አንድ ሰው ወፈር ካለና ሆዱ አካባቢ ቦርጭ ጣል ካደረገበት ተመችቶታል ከማለት አልፎ ሀብት እንዳለውም ሲታሰብ በተቃራኒው በምዕራባውያን ዘንድ ሰውን ወፍራም ነህ ማለት ሊያቀያይም ስለሚችል የማይፈለግ ነገር ነው፡፡ እንግዲህ ውበት አንጻራዊ ነው ብል ብዙዎቻችሁ የምትስማሙ ይመስለኛል፡፡ የውጭ ሰውነታችን የሚያምር ብቻ ሳይሆን የሚያየን ሁሉ የሚወድደው እንዲሆን እንቀባባዋለን ፣ በተቻለን መጠን እናስውበዋለን፡፡ በሰለጠነው ዘመን ብዙዎች እድሜያቸው እየጨመረ ሲሄድ ውበታቸው የቀነሰባቸው ስለሚመስላቸው የፍታቸውን መልክ በቀዶ ጥገና ዜዴ እንደ ወጣት ደምግባት ያላቸው ለመምሰል ሲሉ ከፍተኛ መጠን ያለውን ንዋይ ያፈስሱበታል፡፡ ይህን ያህል ከተለፋም በኃላ ሰው ለቁንጅና የሚሰጠው ቢያኔ ለየራስ ስለሆነ በሁሉ መደነቅና ሁሉን መማረክ አለማቻላቸው ከንቱ ኪሳራ ያስብላቸዋል፡፡ ሰው የቱንም ያህል ፊቱን ቢያሳምርና ቢቀያይር የውጭ ገጽታው እውነተኛ ማንነቱን ሊወክል አለመቻሉ በጣም አሳዛኝ ከመሆኑም በላይ ለዚህ የሚደረገው ጥረት ከፈጣሪ ጋርም የሚያጣላ ሆኗል፡፡ በሰው ፊት መልካቸው የሚያምር ግን ስንት ሰም- ለበስ የሆኑ ክፉዎች እንዳሉ ቤት የቁጠረው ማለት ብቻ ይበጃል፡፡ አንነድች ውበት ማለት የውስጥ ጉዳይ ነው የሚሉት ለዚህ ሳይሆን አይቀርም፡፡ እኔም ላሰምርበት የምፈልገው ይህንን የሚመስል ብርቱ ጉዳይ ነው፡፡እናም እንዲያው ባጭሩ ስለ የውስጥ ሰውነት ማማር ለቅምሻ ያህል የወግ ወጉን ብቻ መርጠን በእጥኑ እንመልከት፡፡
የእግዚአብሔርም ቃል ሲናገር ሰው ፊትን ያያል ይለናል፡፡ ሰው ፊትን ያያል ሲል መልክን ፣ ቁመናን፣ አለባበስን፣ አነጋገርን፣ ከሌሎች ጋር ያለ “አቀራረብ ሁሉ ሊሆን ይችላል፡፡ እግዚአብሔር ግን እኛ እንደምናይ ፊትን አይቶ አይበይንም፡፡ እርሱ የሚያየው ልብን ነው፡፡ የሰው ልብ ከባልንጀራው የተሰወረ ነው፣ ለእግዚአብሔር ግን በግልጽ ይነበብለታል፡፡ ሰውን ሁሉ ግሩምና ድንቅ አድርጎ የሠራው እግዚአብሔር ያ ቆንጆ ነው ይህ ግን አይደለም የሚል ድራማም ከእኛ ጋር ለመጫወት ጊዜውን አይሰጥም፡፡ የኢየሱስ ደቀ መዝሙር የሆነው ሐዋሪያው ጴጥሮስ ጌታ የውስጥ ሰውነታችንና ማንነታችን እንደሚያይ ብቻ ሳይሆን እንደሚያከብረውም ጭምር ሲያመለክት በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ ፣ የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለውን የማይጠፋውን ልብስ ለብሶ የተሰወረ የልብ ሰው ይሁንላችሁ ይለናል (1 ጴጥ 3፡4)፡፡ ሐዋሪያው በወንድና በሴት ማለትም በባልና በሚስት መካካል ስላለው የፍቅር ትሥሥር ሲያስተምር ነው ይህንን አሳብ ያመጣልን፡፡ ባልና ሚስት ሁለቱም በየራሳቸው ለትዳራቸው መስመር ሊጫወቱ ስለሚገባቸው ሚና በመተንተን እየተናገረ የልብ ሰው ይሁንላችሁ የሚለውን ወሳኝ መልእክት ያስተላልፍልናል፡፡ እረ ለመሆኑ እንደ ፊት መልክ የልብ ሰውነትን ተመልክቶ ነጭ ወይ ጥቁር ወይም ጠይም፣ አይነ ልም ወይም መልከ መልካም ማለት ይቻል ይሆን; ካልተቻለስ ;
II. የልብ ሰው መገለጫዎች 
1. በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው የከበረ ነው፡፡
ምእራባውያን ጊዜ ወርቅ ነው ፣ ክቡር ነው ይላሉ፡፡ ቤንጃሚን ዲርሳይሊ የተባሉ ሰው ግን- "ጊዜ ወርቅ ነው እውነት ግን ከጊዜ ይልቅ ውድ ነው " ሲሉ ፣ኤልሳቤጥ ጆርጅ የተባሉ እግዚአብሔርን የሚያገለግሉ ሴት ደግሞ "እያንዳንዱ ቀን የሚናደርገውን ሁሉ እግዚአብሔርንና መንግሥቱን ለማገልገል የሚናውለው ከሆነ የከበረ ነው " አሉ፡፡ ጆን ፓይፔር የተባሉ ታላቅ የእግዚአብሔር ሰውም እንዲህ ብለው ሰበኩ- "የሚያድን እምነት ያላችሁን ሁሉ ብትሸጡና በኃጢአት የሚገኘውን የዓለም መዝገብ ሁሉ ብትተውት የሚያስተማምናችሁ ነው፡፡ የተሰወረው የቅዱስ ደስታ መዝገብ ጥልቅ ለሆነው የውስጣችሁ ጥማት ርካታን ይሰጠዋል፡፡ ከልብ የሆነው የሚያድነው እምነት ኢየሱስን በውስጣችሁ እውነት ማድረግ ብቻ ሳይሆን እርሱን ሁል ጊዜ እንድትናፍቁት ያደርጋችኋል ፣ ኢየሱስ በተስፋው በኩል ወደ እናንተ መምጣቱ በዓለም ካለው ሁሉ ይልቅ አብልጠን የምንፈልገው ትምክህታችን ነው፡፡"
ውድ ዋጋ አውጥተን ልብስና የወርቅ ጉትቻ የምንገበየው ለብሰን በሰዎች ፊት ለማማርና ለማጌጥ ነው፡፡ የሚያዩንም ደግሞ በለበስነው ልብስና የወርቃችን ጥራት መጠን ያከብሩናል፡፡ የምንሠራውን ሽሩባና የምናንጠለጥለውን ጉትቻ እኛ አናየውም የሚያዩልን ሰዎች ናቸው፡፡ እግዚአብሔር ግን የሚያከብረው የልባችንን ጌጥ ነው፡፡ እርሱ ሰው ስለሚያየው የውጭ ማማር ስንጨነቅና ስንወጠር እግዚአብሔር የሚያየው የውስጥ ውበታችን አመድ እንዲለብስብን አይፈልግም፡፡ በእርሱ ፊት እጅግ የከበረ ዋጋ ያላቸው እንደነ ጋብቻ፣ የቅዱሳን አገልግሎትና ሕይወት ወዘተ፣ ያሉ ነገሮች አሉ፡፡ ከእነዚህም አንዱና አውራ የሆነው ሰው ለእግዚአብሔር የሚሰጠው በውስጥ የተሸለመ የልብ ሰውነት ነው፡፡ በእግዚአብሔር ፊት የሚለው ቃል ክብደት ሊሰጠው እንደሚገባ ላሰምርበት እፈልጋለሁ፡፡ 
2. የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለው ነው፡፡ 
በዚህ ሁለት ቁልፍ አሳቦች ተጠቃለው ቀርበዋል፡፡ አንደኛው የዋህነት ሲሆን ሁለተኛው ዝግተኛ መንፈስ ነው፡፡ የዋህነትና ዝግተኛ መንፈስ ማለት ምን ማለት ነው? ሁለቱም አሳቦች ትህትናን፣ ሰላማዊነትንና ጸጥታን ለማመልከት የተጠቀሱ አይደሉምን? የውጭ ሰውነታቸውን በመሸለምና በማስጌጥ ቁንጅናቸውን ለዓለም ለማሳየት የሚዳክሩ ዓለማውያን ሴቶች በበዙበት ዓለም ለእግዚአብሔር ሰዎች ደግሞ በሚያዩአቸው ሁሉና በአምላካቸው ፊት እውነተኛው ዉበታቸው የዋህና ዝግ ያለ መንፈስ ነው፡፡ በተለይም በጴጥሮስ ዘመን ያላመኑ ባሎች ያሉአቸው ክርስቲያን ሴቶች ባሎቻቸውን ለክርስቶስ ለመማረክ ውጫዊ ሰውነታቸውን ከመሸለምና በማስዋብ ይልቅ በየዋህነትና ዝግ ባለው መንፈስ በመመላለስ እንዳለባቸው ሐዋሪያዊ ትምህርት ተሰጥቶአቸዋል፡፡ የዋህነት በእግዚአብሔር ቃል ውስጥ በብዙ መንገድ ተጠቅሷል ፡፡ ሐዋሪያው ቅዱስ ጳውሎስ እንደሚገልጸው የዋህነት የመንፈስ ቅዱስ ፍሬ ነው( ገላትያ 5፡22)፡፡ ጌታችን ኢየሱስም የዋህነትን ከእርሱ እንድንማር አሳስቦናል( ማቴ 11፡29-31)፡፡ አማኞች በየዋህነት መንፈስ በመመላለስ ክርሰቶስን መምሰል ይችላሉ፡፡ በቤትና በውጭ የክርስቶስ እውነተኛ ደቀመዝሙርነታችን ከእርሱ በምንማረው የዋህነት ልንገልጸው እንችላለን፡፡ የዋህነት በባልና በሚስት መካከል ላለው ግንኙነት እጅግ በጣም አስፈላጊ በመሆኑ የተለየ ግምት እንስጠው፡፡
3. የማይጠፋውን ልብስ የለበሰ ነው፡፡ 
የክርስትና ሕይወት ለማይጠፉ መንፈሳዊ ቅርሶች አድሎናል፡፡ በክርስቶስ ኢየሱስ በማመናችን የምናገኘቸው ሰማያዊ በረከቶቻችን የማይጠፉ በመሆናቸው ደስታችን የላቀ ነው፡፡ ለምሳሌ፡ የማይጠፋ ሕይወት(1ጴጥሮ.1፡3-4) የማይጠፋ ርስት፣ የማይጠፋ ተስፋ(1ኛ ጴጥ1፡3-4) ፣ የማይጠፋ አክሊል( 1ቆሮ.9፡) ፣ የማይጠፋ ዘር( 1ጴጥ 1፡23)፣ የማይጠፋ ቤት ወይም መኖሪያ(2 ቆሮ 5፡1-4)፣ ወዘተ በክርስቶስ በማመናችን ምክንያት ያገኘናቸው መንፈሳዊ በረከቶቻችን ሲሆኑ እነዚህ ከማናቸውም ምድራዊ እሴቶች ሁሉ ይለያሉ፣ ይበልጣሉም፣ እኛም ልንወርሳቸው ተጠርተናል፡፡ በምንም ሁኔታ ቢሆኑ ከማይጠፉ መንፈሳዊ በረከቶቻችን አንዱ የውስጥ ሰውነታችን የምንሸልመው የማይጠፋው ልብስ ነው፡፡ የልብ ሰው የሚለብሰው ልብስ የማይጠፋ በመሆኑ የተለየ ግምትና ክብር ይሰጠዋል፡፡ ይህን የውስጥ ሽልማታችንን የሚወስድብንም ሆነ የሚያስረጅብን የለም፡፡ የውስጥ ሽልማታችን በወረት ወይም በፋሽን ሽሚያ ምክንያት በሚከወን ድንገተኛ ማባከን አይጠቃም፡፡ ስለዚህ ሐዋሪያው ክርስቲያን ባለትዳር ሴቶችን ከውጭ ይልቅ ውስጣቸውን እንዲያስጌጡና እንዲሸልሙ አጠንክሮ ይመክራቸዋል፡፡ እውነተኛ ውበት የፊት ወዝ ሳይሆን በነፍስ ላይ የሚታይ ብርሃን ድምቀት ስለሆነ የዓለም ያርግልህ/ሽ ማለትስ በውስጥ ሰውነታቸው በማይጠፋ ልብስ የተሸለሙትን ነው! ውስጣችን ምንም ወዝ የጠፋበት ነጫ ጭባ ከሆነ ውጫዊ ሽልማት ብቻ ውብ አያስብለንምና፡፡
4. የተሰወረ የውስጥ ሰው ነው
የውስጥ ሰው የምንለው የማይታየው ማንነታችንን ነው፡፡ ለምሳሌ፡ ነፍሳችንን፣ መንፈሳችንን፣ እና ህሊናችንን ማለታችን ሲሆን የልብ ጉዳይ ግን አውራ ነው፡፡ የሕይወት መውጫ ልብ ናት፡፡ የሰው ውድቀቱም ሆነ ጥንካሬው እንደልቡ ነው፡፡ የሕይወት አሸናፊነታችንና ጀግንነታችንም የሚገለጸው እንደ ልባችንና እንደ ሐሞታችን ነው፡፡ በእውነት እንነጋገር ካልን ብዙ የመናገራችን ብዛት የልባችንን ምስል አያሳየንም ፣እንዲያውም የጠቢብ ሰው አፍ በልቡ አይደል! ልብና ታማኝነትስ ፍጹም የማይለያዩ ሰምና ፈትል አይደሉ! ስሜታችን ግለቱ ከፍ ሲል ሰዎችን አቅፈን ልንስማቸው እንችል ይሆናል፣እውነተኛ ማፍቀር ግን ከዚያ ይለያል፡፡ አክብሮትንም ለሰዎች ልንቸራቸው እንችላለን ግን ግን ስሜትን ፣አእምሮን፣ስጋንና፣ አስተሳሰብን ሁሉ የሚማርክ ፍቅር የሚመነጨው ከውስጥ ሰውነት ከሆነው ከልብ ነው፡፡ ከልብ የሚመነጨው ፍቅር እንደገለባ እሳት በቅጽበት አይከስምም፡፡ ስለዚህ ነው ፍቅር በትዳር ውስጥ ምሶሶ ነው የምንለው፡፡ ከልብ የመነጨ ፍቅር ካለ የሕይወት ተግዳሮት በሚበዛበት ጊዜ ሁሉ እንኳን ጎጆው ሳይዘምም ይኖራል ምክንያቱም ያ ፍቅር ተሸክሞታልና፡፡ 
ስለዚህ አማኞች እህቶች ወይም ባለ ትዳሮች የውስጥ ሰውነታቸውን ማጌጥ መርሳት የለባቸውም፡፡ ከሥጋችን ይልቅ ለነፍሳችንና ለመንፈሳችን ግድ ሊለን ይገባናል፡፡ ጌታ ኢየሱስም ሲያስተምር ነፍስ ከመብል ከሰውነትም ከልብስ ይበላጣል ብሎአል(ማቴ 6፡25)፡፡ በእግዚአብሔር ጸጋና በመንፈስ ቅዱስ በመሞላት እለት እለት ነፍሳችንን ልናረካት እንችላለን፡፡ ታዲያ ውስጣችን እንዴት ነው? ለሰው የተሰወረው ለእግዚአብሔር ግን የሚነበብለት ውስጣዊ ማንነታችን ሕያው ነው ወይ ሞቶብናል? ያ የተሰወረው የውስጥ ሰው! 
ለ. የልብ ሰው ባሕሪያት
ይህ ክፍል በጌታ የሆንነውን ሁላችንንም የሚመለከት ሲሆን በተለይም የማያምኑ ባሎች ያሉአቸው ክርስቲያን እህቶች እንዲያተኩሩበት ይሻል፡፡ ክርስቲያን ሴቶች ወይም ሚስቶች የተሰወረ የልብ ሰው መሆናቸውና ውስጣዊ ውበታቸው የሚታወቅባቸው መንገዶች ምን እንደሆኑ የጌታ ቃል የሚናገረንን ግልጽ አሳብ ከዚህ ቀጥሎ እንመልከት፡፡ 
1. ለባሎታቸው ይገዛሉ፡( 1ጴጥሮ 3፡1፣ ኤፌ 5፡21-22)፡፡
ሚስቶች ለባሎቸቸው እንዲገዙ የሚነግረን የእግዚአብሔር ቅዱስ ቃል ነው፡፡ ክርሰቲያን ተጋቢዎች ወደ ክርስትና በመለወጣቸው ምክንያት በሚኖሩበት አካባቢና ዘመን ያለው የትዳር ደንብና ሥርዓት የእነርሱን የማይመለከታቸው አድርገው ለራሳቸው እንዳያስቡና ሌሎች ሰዎች እንደሚያደርጉት ሁሉ ራሳቸውን ለባሎቻቸው እንዲያስገዙ ይመክራቸዋል፡፡ ሐዋሪያው ጴጥሮስ በነበረበት ዘመን ሴት ልጅ ሙሉ በሙሉ በአባቷ ቁጥጥር ሥር ትሆናለች፡፡ ሴቶችን እንደ ሰው በማይቆጥረው የሮማውያን መጥፎ ልማድና ባህል መሠረት አንድ ሰው በሴት ልጁ ላይ የፈለገውን ከማድረግ አልፎ ቢፈልግ ሊገድላት ሁሉ የሚችልበት መብት ሲኖረው ይህንን የሚከለክል ሥርዓት አልነበረም፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ሴት ባል ስታገባም ፈቃዷ ሙሉ በሙሉ ለባሏ ይሆናል፣ እርሱም በሚስቱ ላይ የፈለገውን የማድረግ ሥልጣን ነበረው፡፡ ባል ሚስቱን ቢገድል እንኳ የሚከለከልው እስከማይኖር ድረስ ሴት ለባሏ እንደ ዕቃ ወይም እንደ ባሪያ ትገዛለት ነበር፡፡ ነገር ግን ክርስቲያን የሆኑ ሚስቶች ለባሎቻቸ እንዲገዙ ጴጥሮስ የሚያሳስበው ከአሬማውያን አገዛዝና ሥርዓት በፍጹም የተለየ ነው፡፡ ክርስቲያን እህቶቻችን ለሚወዱአቸው ባሎቻቸው ሥልጣን ከልባቸው በመነጨ ፍቅር ተነስተው መገዛት እንዲኖርባቸው ጴጥሮስ ያሳስባቸዋል፡፡ ይህ ደግሞ በእግዚአብሔር ፈቃድ የማይኖሩና አስቸጋሪ የሆኑ ባሎችን ለማሸነፍ የሚረዳ ዋንኛ መንገድ ነው፡፡ ፍቅር የትኛውንም ኃይል የማንበርከክ አቅም አለው፡፡ ለእግዚአብሔር ቃል የማይገዙ ለቤተሰባቸውም የማያስቡ አስቸጋሪ ባሎች በፍቅር ሊንበረከኩ ይችላሉ፡፡ ልዩነቱ አረማውያን ሴቶች ለባሎቻችው የሚገዙት እንደ ባሪያ በግድና በጉልበት ሲሆን የክርሰቲያን ሴቶች መገዛት ግን በፍቅር አስገዳጅነት በገዛ ፈቃዳቸውና በራሳቸው ተነሳሽነት ብቻ መሆኑ ነው፡፡ ተገዙ የሚለው ቃል ሴቶች ለወንዶች ባሪያ ሆነው እንዲረገጡላቸው የሚያዝ ሳይሆን ወድደውና ፈቅደው የሚደርጉት ልዩ መንፈሳዊ ትርጉም ያለው ነው፡፡ የመገዛቱ አስገዳጅነት ለሚስቶች ብቻ የተሰጠ ሳይሆን ባሎችም እኮ ለሚስቶቻቸው እንዲገዙ ቅዱስ ቃሉ ያስተምራል(ኤፌ 5፡21፣ 1ጴጥ 3፡7)፡፡ የክርስቲያናዊ ሥልጣንና መገዛት በእግዚአብሔር ፍጹም ፍርሃት በእርስ በርስ የሚደረግ እንጂ አንዱ የበላይ ሌላው የበታች እግር አጣቢ የሚሆንበት አይደለም፡፡ ይልቁንስ የክርስቶስ ፍርሃትና ባልን የመውደድ ምስጢር ለገባት ሴት ሚስትነት እኮ የተከበረ ፣ ከፍ ያለና ወሳኝ ሰማያዊ ጥሪ ነው፡፡ ስለዚህ ራሷን ለበሏ ስትሰጥ የባሏ ፍቅር ደስታዋን ሙሉ ያደርግላታል፡፡ ምክንያቱም መጽሐፍ ቅዱስ ተገዙ የሚለው አንድ መንገደኛ ለሆነ ወንድ ሳይሆን፣ ወይም የሆነ የጎረበት ሰው ሳይሆን አካሏ ለሆነው ባል ነው፡፡ ባሏ ለእርሷ አካሏ፣ ምርጫዋ ከማንኛውም ወንድ ጋር የማታወዳድረው ልዩ ጌጧ ነው፣ ከወንድሟም ይልቅ የሚቀርባትና የሚጠጋጋት ወዳጇ ነው፡፡ እናት አባትዋን ትታ የተጣበቅችበትና የተጣበቃት አጋሯ ነው ፣ እርሷም አጋሩ ናት፡፡ ታዲያ ራሷን በመስጠት ብትገዛለት ይበዛባታልን? እርሱስ ቢገዛላት ክብር አይሆንለትምን? ክርስቲያን ሚስቶች በፈቃዳቸውና በፍቅር ብቻ ሳይሆን በደስታ ሊያደርጉት ይገባቸዋል፡፡ ለትዳር ጓደኛቸው መልካምን የሚያደርጉ ሰዎች ምንም እንኳ የባሎቻቸው ወይም የሚስቶቻቸው ልብ የብረት ያህል የጠነከረ ቢመስልም በፍቅርና በደስታ በሚያደርጉት መሰጠትና መገዛት ያንን ሁሉ ሊያለሰልሱ ይችላሉ፡፡ አስቸጋሪና አመጸኛ የሆነውን ሰው ልብ ለመለወጥ በምድር ሕግ ከመግዛት ይልቅ በቤተሰብ ውስጥ የሚደረገው ፍቅርና ደግነት የተሻለ ተመራጭነት አለው፣ አላወቅንበትም እንጂ፡፡
2. ሰውነታቸውን በተገቢ ልብስ ይሸልማሉ፡፡
ሐዋሪያው ጴጥሮስም ከውጭ ማገጥ ይልቅ የተሰወረና የከበረ የልብ ሰው ይሁንላችሁ ብሎ ባለትዳሮችን መከረ፡፡ የልብ ሰው መሆን ለእግዚአብሔርም ሆነ ለሰው የሚመች እንደሆነ የእግዚአብሔር ቃል ይናገራል፡፡ የውስጥ ሰውነታችንን ስለማማር ለእናንተ ጸጉርን ማሸረብ፣ወርቅን በማንጠልጠል ወይም ልብስን በመጎናጸፍ በውጭ የሆነ ሽልማት አይሁንላችሁ፡፡ ነገር ግን በእግዚአብሔር ፊት ዋጋው እጅግ የከበረ የዋህና ዝግተኛ መንፈስ ያለውን የማይጠፋውን ልብስ ለብሶ የተሰወረ የልብ ሰው ይሁንላችሁ፡ ይለናል፡ 
እግዚአብሔር ስለ አለባበሳችን ይገደዋል ወይ፣ እኛ የፈለግነውን ብንለብስ ምን ኃጢአት አለበት የሚሉ በርካታ ወገኖች እንዳሉ አልጠራጠርም፡፡ በእርግጥ ይህን አትልበስ ይህንን ደግሞ ልበስ የሚል የአዲስ ኪዳን ትምህርትም ሆነ ትዕዛዝ የለም፡፡ ሆኖም በተገቢ አለባበስ ራሳችንን እንድንሸልም ተመክረናል ፡፡ 
ሐዋሪያው ባገለገልበት ዘመን በዓለም ላይ ምግባረ ብልሹ፣ ሕይወታቸው በርኩሰትና በብልግና የተሞላ ሴሰኛ የሆኑ ሴቶች ነበሩ፡፡ እነዚህ ሴቶች በአካላቸው ላይ የተለያዩ ምልክቶችን ከማድረጋቸውም በላይ የአለባበስ ሥርዓታቸውም ሁሉ ከክርስቲያን ሴቶች ሁኔታ በጣም የራቀና ለአእምሮ የማይመች ነበር፡፡ ከእነዚያ ሁኔታዎቻቸው አንዱ የጸጉር አሠራራቸው ነው፡፡ አሬማውያን ሴቶች ያንን ያደርጉት የነበረው በውጭ ሰውነታቸው ብቻ በማማር የውስጣቸውን ባዶነት የሚሞሉ ስለመሰላቸው ነው፡፡ አሬማውያን ሴሰኛ ሴቶች የውጭ ሰውነታቸውን ለመሸለም ከፍተኛ ገንዘብ የሚያፈስሱት ለትዳር ጓደኛቸው፣ ለልጆቻቸው ወይም ለአጠቃላይ ትዳራቸው የሚሉት፣ የሚቆረቆሩለት የወይም የሚገዳቸው ነገር አልነበራቸውም፡፡ የቤተሰብ ሃላፊነት ስሜትም ስለማይሰማቸው የሚያገኙትን ገንዘብ በሽሩባና በወርቅ ያጠፉት ነበር ክርስቲያኖች ሴቶችም ከእነርሱ በመኮረጅ ልክ ዓለማያን ሴቶች እንደሚያደርጉት ዓይነት ሽሩባ መሠራትና የእነርሱን ዓይነት ልብስ መጎናጸፍ ቢሞክሩ ደግሞ በኑሮአቸው ማባከንንና በትዳራቸውም አለመስማማትን ሊፈጠር ይችላል፡፡፡፡ እነርሱ ከእግዚአብሔር የተሰጣቸው የቤተሰብ ኃላፊነት ስለነበራቸው ከአሬማውያን ሴቶች ይለያሉ፡፡ ከባሎቻቸው ጋር በፍቅር ገመድ የታሠሩ በመሆናቸው ውበታቸው ለባሎቻቸው ነው፡፡ ብዙን ጊዜ የትዳር ጓደኛችንን በምን እናስደስተው ወይም በምን እናስደስታት ለሚለው የብዙዎች መልስ የሚሆነው ልብስ በመግዛት ልዩ ልዩ ስጦታዎችን በማበርከት ወዘተ ነው፡፡ ይህ አባባል እውነት ነው ግን የትኛውም ስጦታና ምግብ ፍቅርን አይተካም፡፡ ሰው የሚፈልገው ምግብና ጨርቅ ሳይሆን ፍቅር ነው፡፡ ሐዋሪያው ሦስት ዓይነት የውጭ ማጋገጫ መንገዶችን ይከለክላቸዋል፡፡ የመጀመሪያው ጸጉርን መሸረብ ሲሆን ሁለተኛው ወርቅን ማንጠልጠል ነው፡፡ ሦስተኛው ደግሞ ልብስን መጎናጸፍ ነው፡፡ እንግዲህ ይህንን ስንመለከት መልበስን፣ የወርቅ ጌጥን ፣ ጸጉርን መታጠብና ማማርን እግዚአብሔር አይቀበልም እያለ ነውን; ወይም ደግሞ ወርቅ ማድረግና በልብስ መሸለም ነውር ነው እያለ፣ ጸጉርን መሽረብን እየከለከለ፣ ኃጢአት ነውና ወርቅን አታድርጉ የወርቅንም ጉትቻ ከእናንተ አርቁ እያለ ነውን; በፍጹም አይደለም፡፡ ነገር ግን ወርቅን ማንጠጥልጠል አይሁንባችሁ የሚለው የሐዋሪያ ምክር ክርስቲያን ባለትዳሮች ውጭአቸውን ከልክ በላይ ሊያደምቅ በሚችል ልብስ ራሳቸውን ለመሸለም ሲሉ የሚያደርጉት ጥድፊያ ለመንፈሳዊ ነገር ደንታ ቢሶች እንዳያደርጋቸው የሚያሳስብ ምክር እንጂ፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ የነበሩ የጥንት ሰዎችን ስንመለከት እነ ርብቃና አስቴርን የመሰሉ የእምነት ሰዎች ከወርቅ በተዘጋጀው ጌጣጌጥ ተውበዋል፡፡ ይሁን እንጂ ከዚያ በኋላ አመንዝራዎች ሴቶችና ጋለሞታዎች ውድ በሆነ ዋጋ ወርቅን በመግዛት ራሳቸውን መሸለምን ምልክታቸውና መታወቂያቸው አድርገዋል፡፡ እንዲሁም ደግሞ እግዚአብሔርንም እንዳያመልኩ እንቅፋት ሆኖባቸው ነበር፡፡ የምንምበላው የምንጠጣውና የምንለብሰውና እንዲሁም የምናጠለጥለው ጌጥ ለመንፈሳዊ ሕይወታችን እንቅፋት ሊሆንብን አይገባም፡፡ የእምነትን ኑሮ ስንኖር ፣ ብንበላም ብንጠጣም፣ ብንብስብም ሆን ወርቅን ብናጠለጥል ለመንፈሳዊ ህይወታችን ትልቅ ትኩረትና ጥንቀቄ ልናደርግ ይገባናል፡፡ ከጌታ ከኢየሱስ ጋር ያለንን መንፈሰዊ ትሥሥራችንን የሚያበላሽብንን ማንኛንም የውጭ ማማር ልንንቀው ያስፈልጋል፡፡ በተጨማርም የምንለብሰው ልብስ፣ የምንሠራው ሽሩባና የምናንጠለጥለው ወርቅ ለትዳር ጓደኛችንና ለልጆቻችን ወይም ለቤተሰባችን ያለንን ፍቅርና ኃላፊነት ካበላሸብን አደጋ መጣብን እንበል፡፡ ክርስቲያን እሕቶቻችን በሁሉም በኩል የቅድስና ኑሮን እንዲታይባቸው እግዚአብሔር ይፈልጋል፡፡ እንደ ክርስቲያን ሴት እኔ ምን ዓይነት ወርቅ ማድረግ ይገባኛል፣ ምን ዓይነትስ ሽሩባ ልሠራ ይገባኛል፣ ለቤተሰቤም ፣ ለእኔም ፣ እንዲሁም ለትዳር አጋሬ ደስ የሚያሰኘን ምን ዓይነት ልብስ ብለብስ ነው ማለት አስተዋይነትም ክርስቲያናዊ ጨዋነትም ነው፡፡ ለእግዚአብሔር ክብር የሚሆን ልብስ እንዳለ ሁሉ ለእግዚአብሔር ክብር የማይሆኑ ብዙ ልብሶች እንዳሉ አይኖች ይመልከቱ፡፡ የሚያዩትን ሌሎች ሰዎችን የሚማርኩ ልብሶች እንዳሉ ሁሉ ሰዎችን ለአላስፈላጊ ፈተና የሚያጋልጡ አለባበሶች እንዳሉ ያልተገነዘበ ሰው ያለ አይመስለኝም፡፡ ደስ ያለንን ብቻ ሳይሆን ልክ የሆነውን ልንለብስና ልናደርግ እንደሚገባን ሁላችንም የምንስማማ ይመስለኛል፡፡ እንመለስበታለን !

Friday, February 23, 2018

አራቱ የኢትዮጵያ ሕመሞች


ከዛሬ አምስት ዓመት በፊት አገራችን ኢትዮጵያ ፈውስ ያስፈልጋታል በሚል አንድ ጽሑፍ አዘጋጅቼ በማኅብራዊ ገጽ ላይ መለጠፌ ይታወቃል። የጽሑፌ ርዕስ “ምድራችሁን እፈውሳለሁ ይላል እግዚአብሔር” የሚል ሲሆን ብዙዎች አንብበውታል። የጽሁፉ ቁልፍ አሳብ ምድራችን/ አገራችን/ ኢትዮጵያ ያጣችሁ በረከት ሳይሆን ፈውስ ስለሆነ ለፈውሷ እንጸልይ የሚል ነበር። ምድራችን መታመሟን ሁሉም ያውቀዋል። እግዚአብሔር አምላከ “ምድራችሁን እፈውሳለሁ” ያለው ምድር በሕመም ስለምትሰቃይ ነው። የአገራችን ሕመም ቀስ በቀስ የውስጥ ሰውነትን እያዳከሙ በጊዜ ቆየታ ሕይወት እንደሚቀጥፉ ሥር የሰደዱ ሕመሞች ነው። እነዚህ chronic በመባል የሚታወቁ ሲሆን ይኸውም በሰውነት ውስጥ ሥፍራ ይዞ ቀስበቀስ አካልን የሚያደክም አደገኛ የሕመም እድገት ነው። ሰውን የሚገድሉ ሥር የሰደዱ ሕመሞች ናቸው።
እንደዚሁም ሁሉ ምድርም ለሕይወት በሚያሰጋ በከባድ በሽታ ትታመማለች። ስለዚህም ነው እግዚአብሔር ምድራችሁን እፈውሳለሁ ያለው። ሰው ሲታመም ወደ ሐኪም ቤት ይወሰዳል። ምድር ስትታመም ግን ከመለኮት ጣልቃ ገብነት በቀር ሌላ ሐኪም ቤት የለም። ምድር ከእግዚአብሔር በቀር ሌላ ምን ሐኪም የላትም። መድሃኒቱም ያለው በእርሱ እጅ ብቻ ነው። ኢትዮጵያ መታመሟን ያወቅነውም ብዙ ቆይተን አሁን በቅርቡ ቢሆንም እኛም አብረን እየታመምን ነው። ስለዚህ ይህቺን አገር የሚወዳት ሁሉ ሊጸልይላት ይገባዋል። የአገሬ ፍቅር አለኝ የሚል ማንም ከሚዘፍንላት ይልቅ ፣ ከሚዘምርላትም ይልቅ ፣ አሁን የሌላትን መንፈሳዊ ስም ከሚስጣት ይልቅ ሊጸልይላት ይገባዋል። ስለዚህች አገር ማቅ ለብሰን ፣ አመድም ነስንሰን ፣ ከካህን እስከ ምዕመን ቢቻል በር ዘግተን ፣ ከእህል ከውሃ ተለይተን ማልቀስና መቃተት ያለብን ጊዜ ቢኖር አሁን ነው። ሕመሞቿን በቀላል አማርኛ ፣ እንደሚከተለው እንድገልጽ ይፈቀድልኝ።
፩. በዘርና በጐሳ የሚከፋፍል ሕመም።
እስትሮክ አንዱን የአካል ክፍል ለይቶ የሚጐዳ የህመም ዓይነት ነው። ይህ ቀኙ እየሠራ ግራውን እንዳይንቀሳቀስ የሚያደርግ ወይም ግራው ደህና ሳለ የቀኙን በኩል ከላይ እስከታች የሚያሽመደምድ በሁሉ የተረገመ በሽታ ነው። ። ይህ ዓይነቱ በሸታ ቶሎ ባይገድልም የሕመምተኛውን የመዳን ተስፋ ያጨልማል። እንደዚሁም የአገራችን ሕመም በዘር በጐሳ፣ በወገን፣ በክልል የሚከፋፈል እንደ ስትሮክ ዓይነት ነው። ሌሎች የበለጠጉና ያደጉ አገሮች የጐሳ ፖለቲካን /Ethnic politics/ በጐጂነቱ ፈርጀው ወደ እንጥሮጦስ ከጣሉና ዳግም ተንስቶ ለአገራቸውና ለሕዝባቸው ጥፋት እንዳያመጣ መንገዱን በጥርብ ድንጋይ ከዘጉ በኋላ ይህ አደገኛ ፖለቲካ በአገራችን የዕድገት፣ የዴሞክራሲና የልማት አምድና ምሶሶ ተደርጐ ተወስዷል። ኢትዮጵያ የብዙ ብሔር ብሔረሰቦች፣ የቋንቋዎች፣ የባህሎች ፣ የዘርፈ ብዙ ማህበራዊ እሴቶች ባለቤት መሆኗ ከፍሎ ለሚያሰቃይ በሽታ ምቹ አድርጐአታል። የአገራችን ሕዝቦች በመካከላቸው ያለውን ልዩነት እንደጌጥ እየቆጠሩ እርስ በእርሳቸውም እየተቻቻሉ ፣ በአካባቢቸውም ያለውን ግብአት በጋራ እየተጠቀሙ ያለ አንዳች መገፋፋት ለዘመናት መኖራቸው፤ ሰሜኑ ከደቡቡ ሕዝብ፣ ምሥራቁ ከምዕራቡ፣ የመሀሉ ከዳሩ ሕዝብ ጋር ተረዳድተውና ተከባብረው የኖሩባትና የሚኖሩባት አገር መሆኗ እውን ቢሆንም አሁን በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት ባመጣብን ከፋፋይ ፖለቲካ የተነሳ ሕዝቦቿ እርስ በርሳቸው ከመከፋፈልም አልፎ እስከ መገዳደል ደርሰዋል። ሥር የሰደደ በሽታ የሰውን የቀድሞ መልኩን እንደሚለውጠው ሁሉ አሁን ያለችው ኢትዮጵያ ድሮ የምትታወቀዋ በታሪክ ስለ እርሷ የምንሰማው፣ምሁራን ያስቀሩልንን ታሪክ የምናነበው ሳይሆን ታሪኳ ተቀይሮ፣ መልኩዋም ጠፍቶ ፣ ከቀደሞው ታሪክ ጋር የማይገጥም እንግዳ ነገር እንድናይ የሚያደርግ ሕመም ሥር እየሰደደባት ነው።
በአገሪቱ ያለው እያንዳንዱ ብሔር መነሻ ማንነት ቢኖረውም በቅድሚያ ሰው መሆኑን ያምናል፣ከዚያም ኢትዮጵያዊ መሆኑን ያምናል። አማራው አማራ ነኝ ቢልም ኢትዮጵያዊነቱን አይክድም ነበር። የበላይ ዘለቀ ልጅ ጐጃሜ ነኝ፣ ደግሞም ምንጃሬ፣ ሸንኮራ ነኝ ዘራፍ፣ዘራፍ ዘራፍ ቢልም ኢትዮጵያዊነቱን ሳይክድና ሳይለቅ ከሌላው ሕዝብ ጋር እርሱም አብሮ ኢትዮጵያዊ እንደሆነ ያምን ነበር። ሌላው ብሔር ቢሆንም እንደዚያው ነው። የአባጁራፍ ልጅ ኦሮሞ ነኝ ፣ የካዎ ጦና ልጅ ወላይታ ነኝ፣ የንጉሥ አይማሎ ልጅ ጋሞ ነኝ፣ የንግሥት ፉራ ልጅ ሲዳማ ነኝ ወዘተ ቢልም ከሌሎች ሕዝቦች ጋር ኢትዮጵያዊ ነኝ፣ አገሪቱ የጋራችን ነች፣ ወንዙ ሸንተረሩ ተራራው፣ ጋራው፣ ሁሉ የጋራችን ነው፣ እያለ በልዩነቱ ውስጥ ያለውን ውበትና ጣዕም እያጣጣመና እያደነቀ፣ አንዱ የሌላውን ሕመም እየታመመ፣ በደስታውም አብሮ እየተደሰተ፣ ኢትዮጵያን በጋራ ተሸክሞ የኢህአዴግ መንግሥት አገሪቱን እስከሚቆጣጠርበት ጊዜ አደረሳት። ያውም ክብሯ ዝቅ ሳይል፣ ዳር ድንበሯ ሳይደፈር፣ አንድ ስንዝር መሬት ለጐረቤት አገር በድርድርም ሆነ ጦርን በመፍራት አሳለፎ ሳይሰጥ ነው ታዲያ! የኢህአዴግ መንግሥት ምድሩን ማስተዳደር ሲጀምር አፉን የፈታው “መገንጠል” ፣ “ክልል”፣ “የራስን መብት በራስ መወስን” በሚሉ ቃላቶች ነው። ቃላቶቹ/ አሳቦቹ ልበላቸው/ ለኢትዮጰያ ሕዝቦች አንድነትና እኩልነት ፣ ለመብታቸውም መከበር ዘብ የሚቆሙ ቢመስሉም አሁን ለሚታየው መከፋፈልና መናቆር የተጣሉ የመሠረት ድንጋዮች ናቸው። ቃላቶቹ አሳችና ግራ አጋቢዎች ናቸው። አሁን በሥልጣን ላይ ያለው መንግሥት የሕዝቦችን ትሥሥር ለመበጣጠስ የቻለው በእነዚህ የመሠረት ድንጋዮች ላይ ቆሞ ነው። ይህ መንግሥት ወደ ኢትዮጵያ ሲገባ አንዱን ብሔር ከሌላው፣ አንዱን ክልል ከአንዱ ጋር የሚያባላው እነዚህን በሽታ አምጪ ሕዋስ የሆኑ ቃላቶችን በምድሪቱ ላይ በመበተን ነው። ይህም በመሆኑ ኢትዮጵያ ከተፈጠረችበት ጊዜ አንስቶ እስከአሁን ድረስ ተቻችለው የኖሩ፣ ተሳስበው፣ ተከባብረው፣ ተጋብተውና ተዋልደው ፣ በሁሉም ማኅበራዊ ጉዳዮች አንድ ሆነው በመልካም ትሥሥር ለዘመናት የቆዩ ሕዝቦች እርስ በርሳቸው ለመጐሻሸም፣ ለመገዳደል ፣ ለመፈነቃቀልና ለማሳደድና ለመሰደድ ከተጋለጡ ይኸው የአንድ ጎልማሳ ዕድሜ እያስቆጠሩ ነው። ለዚህ ሕመሟ መድኃኒት ያልተገኘላት አገራችን ሕመሟ እየጠናባት በመሆኑ መድኃኒትና መላ ፣ መፍትሔም ያስፈልጋታል። ከመጀመሪያውም መፍትሔ ሊገኝ በማይችል ሁኔታ መርዙ ስለተቀነባበረና በየቦታውም ስለተቀበረ ሕመሟ እየባሰባት መጣ። የኢሀአዴግ መንግሥት የኢትዮጵያ ሕዝቦች በአንድነት እንዳይኖሩ በቋንቋና በብሔር እንዲከፋፈሉ ማድረግ ብቻ ሳይሆን የሳለው የአገሪቱ ካርታና ክልላዊ መዋቅሩ እንኳ ቢታይ ብሔርን ባህልንና ቋንቋን መሠረት ያደረገ ነው። ይህ የኢትዮጵያ ሕዝቦች ወደፊት አንዱ ከሌላው ለመገንጠል እንዲያመቸው ሆን ተብሎ የተሠራ ተንኮል መሆኑ ሳይገባን ኖረናል። በአሁኑ ጊዜ መቻቻልን ትተው ወንድም ወንድሙን በጦር እያሳደደ፣ ክልሌ ስለሆነ በዚህ አካባቢ መኖር ፣ መንቀሳቀስ ፣ መሥራት ወዘተ አትችልም እያለ አብሮት የኖረውን፣ አብሮት ያደገውን ያሳድደዋል። ሁለት ሰዎች ቢጣሉና አንደኛው ቢጐዳ እነማን ናቸው የተጣሉት ተብለው በሰውነታቸውና በስማቸው መሠረት መጠየቅና ማስረዳት አግባብ ሆኖ ሳለ አሁን የሚጠይቀው ብሔር ፣ ዘር ወይም ክልል ነው። ይቀጥልና የዚህ ብሔር የዚኛውን ብሔር ደበደበ፣ ወይም የዚህ ብሔር የዚኛውን ብሔር ገደለ ይባልና ጠቡ የብሔር ይሆናል። አሁንም ይቀጥልና ይህ ብሔር ከዚኛው ብሔር ጋር ተጣላ፣ ከዚሀ ብሔር ይህን ያህል ሰው ሞተ፣ ይህን ያህል ሰው ተጐዳ የሚል ዜና ይሰራጫል። ወያኔ ሕዝባችንን እጁን ይዞ ሀ ሁ ሂ እያለ ፊደል ያስቆጠረውና ያለማመደው ይህንን ክፉ ሥራ ነው። የግለሰቦቹ ጠብ ዕለታዊ ጉዳይ የግል እንጂ የብሔር ጠብ አልነበረም ግን የተዘረጋው መዋቅር እና የተቀመመው የፖለቲካ መርዝ ይህንን መሰል በሽታ በሕዝባችን ላይ አመጣ። እውነት ለመናገር አንዱ ሕዝብ አብሮት ከኖረው፣ በባህል ፣ በሃይማኖት በጋብቻ ወዘተ ተሳስሮ፣ ተቀላቅሎ፣ አንዱ ከሌላው ጋር ተጋብቶና ተዋልዶ ለዘመናት ከኖረበት ከሌላው ህዝብ ጋር መጋጨትም ሆነ መቃቃር እንደሚገባው የሚያምን ኢትዮጵያዊ የለም። የአማራ ሕዝብ ከሮሞና ከሌላው የሲዳማ ሕዝብ ከወላይታ ህዝብ ጋር ፣ ጉጂ ከቡርጂ ጋር መተላለቅ አይገባውም ነበር። በቅርቡ እንኳ በዝዋይ ከተማ በሁለት ኢትዮጵያውያን መካከል ጠብ ቢፈጥር የኦሮሞና የወላይታ ሕዝቦች ግጭት ተደርጐ መወሰዱ ፣ አሁን ደግሞ በምሥራቁ የአገራችን ከፍል የብዙዎችን ሕይወት እየቀጠፈ ያለው ቀውስ እንደ ምሳሌ ሊጠቀስ የሚችል ነው። ሕመሙ በኢትዮጵያ መላ ሰውነቷ ላይ ስለተሠራጨ ይህ አሳዛኝ ነገር ሊሆን ቻለ። የኢህአዴግ ወያኔ መንግሥት መሪዎች አሸናፊውን ለመለየት በመሀል እንዳለ ታዛቢ ነገሩን በትዝብት ያዩታል ወይም እንደ ተመልካች ይዝናኑበታል እንጂ መፍትሔ አይሰጡበትም፤ የጸጥታ ሃይሉም ሬሳ ቆጥሮ ሪፖርት ያደርጋል እንጂ በሚተላለቀው ሕዝብ መካከል ገብቶ የሕዝቡን ዋስትና አያረጋግጥም፣ ምክንያቱም ፖሊቲካው ሲጠነሰስ የተፈለገው ይኸው ነውና። ይህ በሽታ ኢትዮጵያን እንዳያጠፋት የተቻለውን መፍትሔ ሁሉ መፈለግ ያሻል። ከመፍትሔዎቹ አንዱና ቀዳሚው በእግዚአብሔር ፊት ማልቀስ ነው። ያለዚያ አሁን የተበተነው ሕመም አመንጪ የፖለቲካ ሕዋስ አካሉዋን በጣጥሶና ገነጣጥሎ ይጨርሰዋል። መንግሥት እንደሆነ የኢትዮጵያን መሬት ሲያሻው ለጐረቤት አገር እየሸጠ ፣ ሲያስፈልገው ከመሃሉ አርሶ አደሩን አፈናቅሎ መሬቱን ለባዕድ እየሸጠ ሕዝባችን ላይ ድራማ ይሠራበታል፣ ቁማርም ይጫወትበታል። በምዕራቡ በኩል አንድ የአካል ክፍል ተቆርሶ ወደ ሱዳን በኩል ወድቋል። የነገ ተረኛ ማን እንደሆነ አናውቅም።
አካልን የሚደመስሰው የፖለቲካ ሕዋስ በቤተመንግሥት ብቻ ሳይወሰን ወደ ሃይማኖቱ ውስጥም መግባቱ የኢትዮጵያን የወደፊት ዕጣ፣ በሕይወትም የመቆየቷን ጉዳይ የበለጠ አሳሳቢ አድርጐታል። ቸር ወሬ ያሰማን እንጂ ቤተክርስቲያንም በዘር ፣ በጐሳ ከተከፋፈለች ጊዜ የለውም። እንዲያውም ፈጥና ራሷን የሰባበረችው ቤተ ክርስቲያን ነች። በብሔር ወገንተኝነት ላይ የተመሠረተ ቤተ ክርስቲያን ሁሉ አለ። መንግሥትም ለመከፋፈል ዓላማው እንዲያመቸው በሁሉም የሃይማኖት ተቋማት ውስጥ የራሱ ካድሬዎች ሰግስጓል። በየእምነት ተቋማት ውስጥ የኢህአዴግ የደህንነት ካድሬዎች አሉ። የፖለቲካ መዋቅሩ ከመንግሥት ተቋማት እስከ አጥቢያ ቤተክርስቲያናት ድረስ ተዘርግቷል። የወንጌል ቃል በሚገለጥበት ሥፍራ ላይ ቆመው መንግሥትን የማሞካሸት የሚቃጣቸው የቤተክርስቲያን መሪዎች ጥቂት አይደሉም።
የሕመም አምጪው ሕዋስ በአገር ቤት ብቻ ሳይወሰን ባህር ተሻግሮ በመምጣት ሕዝቦቿን እያተራመሳቸው ነው። ከቤተሰቦቻቸው ጋር በልጅነታቸው ከአገር የወጡ ልጆች የመጡበትን አገር ሲናገሩ ከምሥራቅ አፍሪካ ፣ ከኦሮሚያ ነው የመጣነው ሲሉ ከኢትዮጵያ ናችሁ ሲባሉ አይደለም ከኦሮሚያ ነው ይላሉ። እንግዲህ እነዚህ ልጆች ኢትዮጵያ የምትባል አገር እንዳለች አያውቁም ማለት ነው። ከእነርሱ በኋላ የሚመጣው ትውልድ ኢትዮጵያ የምትባል አገር እንደነበረች አድርገው እንደ ታሪክ መናገራቸው አይቀርም። ጂቡቲ ከኢትዮጵያ ክፍላተ ሀገራት አንዷ እንደነበረች የማያውቅ ወጣት ብዙ እንደነበረ ሁሉ ኦሮሚያ ፣ አማራ፣ ሐሬሪ፣ ቤንሻንጉል ፣ ሲዳማ፣ ወላይታ ወዘተ የሚባሉት አገሮች እንደ አንድ አገር በአንድ መንግሥት አስተዳደር ሥር ነበሩ እያሉ ማውራታቸው አይቀሬ ነው። ይህ የዘመኑ መንግሥት ያመጣብን ገዳይና ኢትዮጵያን በቁሟ እያለች ሰውነቷን አፈራረሶ የሚያጠፋት በሽታ ነው።
ወያኔ ካመጣው የፖለቲካ ቀውስ የተነሳ ሰዎች በአገሪቱ ከአንዱ ክልል ወደ ሌላው ክልል የመዘዋወር ነጻነታቸው ጠባብና ግዱብ ነው። አንድ ኢትዮጵያዊ ከደቡብ ክልል ወደ አማራ ክልል ሄዶ መኖር ፣ መሥራት፣ መነገድ ይችላል? ከሰሜንም ክልል ወደ ምዕራብ ክልል ሄዶ በነጻነት መኖር የሚችልበት የዜግነት መብትም ሆነ የሕግ ዋስትና አለው? ኢትዮጵያ አለኝ የምትለው ዲሞክራሲ ይህንን ያረጋገጣል? ካልሆነ ለዚህ ሰው ኢትዮጵያ የምትባለዋ አገር የቷ ነች? የኢትዮጵያ ሉአላዊነትና ዴሞክራሲ የሚረጋገጠው በሕዝቦቿ አንድነት ከሆነ በተከፋፈለ ህዝብ የአገር ሉዓላዊነትና ዴሞክራሲ ሊረጋገጥ የሚችለው እንዴት ነው? እስቲ ከአሜሪካ ፖለቲካ እንማር! አሜሪካ ከሁሉም የዓለም ዙሪያ የመጡ ሕዝቦች የሚኖሩባት አገር ብትሆንም አሜሪካውያን ሌላውን ሕዝብ በእኛ ላይ መጣችሁብን በሚል አንድም ቀን ተነስተውባቸው አያውቁም። ሁሉም ከአንዱ ግዛት ወደ ሌላው በመዘዋወር መሥራት፣ መማር፣ ቤት መግዛት ወዘተ የሚችሉበት መብታቸው የተጠበቀ ነው። በአገራችን ግን ዴሞክራሲ አለ ቢባልም በዴሞክራሲው ተጠቃሚዎቹ ፖለቲከኞችና ተከታዮቻቸው እንጂ ዜጋው አይደለም። የጐሳ ፖለቲካ ዜጋዎች በአገራቸው ውስጥ በየትኛውም ክልል በነፃነት የመንቀሳቀስና የመኖር ዋስትናቸውን የሚገድብ አደገኛ ሥርዓት ነው። የጐሳ ፖለቲካ ባለበት የሕዝቦች እኩልነት በሕልም ካልሆነ በውኑ አይታሰብም፣ አይሞከርምም። በአገራችን አለ የሚባለው የሕዝቦች እኩልነት በጦርነትና በጭፈራ ቀን እንጂ ሥልጣንን በመጋራት፣ ፍትሐዊ የሀብት ክፍፍል ወዘተ በማድረግ ላይ የተመሠረተ ሳይሆን ለተወሰኑ ቡድኖች ጥቅም የቆመ፣ የአንዱን ወገን የበላይነትና የሌሎችን የበታችነት( Ethinic inequality)የሚያጎላ ነው። ግደይ በጠገበበት ገመዳ ጨፈረ ነው ነገሩ። የውጭ ኃይላት ወረራና ለዘመናት የነበረው ጦርነት ሊያፈርስ ያልቻለው የኢትዮጵያ ሕዝቦች አንድነት በጐሳ ፖለቲካ እያፈራረሰ ይገኛል።
የጐሳ ፖለቲካ የመልካም አስተዳደርም (good governance) እንቅፋት ነው። መልካም አስተዳደር ማለት የአገሪቱን ዜጐች መብትን፣ ምጣኔ ሀብትን፣ ብሔራዊ ዋስትናን፣ የአገር ሉዓላዊነትን፣ የውጭ ግንኙነትን፣ ብዝሃ ህይወት፣ ትምህርትና ጤናን የአገር መከላከያንና ዳር ድንበርን ወዘተ በሚመለከት የሚደረስ ሚዛናዊ ውሳኔ ነው። በዚህ ዓይነቱ ውሳኔ ማዕከላዊ ተዋኒያን/ central figure / መንግሥት ነው። መልካም አስተዳደር ቢያንስ ቢያንስ ስምንት ባሕሪያት አሉት። አሳታፊነት Participatory/፣የጋራ ስምምነት/Concensus/ ተጠያቂነትaccountable፣ ግልጽነት transparency ፣ ምላሽ ሰጪነት rsponsiveness፣ ውጤታማነትና ብቃት effectiveness and efficiency ፣ ሁሉን ያማከለና በእኩልነት የተከተለ equitable and inclusiveness ፣ በውሳኔ አሰጣጡ ወቅት የህግ የበላይነትን የሚከተል follows the rule law,፣የአናሳዎችን አመለካከት የሚቀበል፣ የተጠቂዎችን ድምፅ የሚሰማና የማኅበረሰቡን የአሁኑናን የመጻኢውን ጊዜ ፍላጐት አጥኖ መላሽ የሚሰጥ ነው /the views of minorities is taken into account and the present and future need of the society are heared in decision making/ ። በቃላት ደረጃ በኢትዮጵያ መልካም አስተዳደር ና የሕግ የበላይነት እንዳለ በመንግሥት በኩል ቢወራም አመራሩ ግን የአምባገነናዊ ነው። ስለዚህ ይህች አገር መላ እሷነቷን እየፈራረሰ ካለው ከዚህ በሽታ ድና በሕይወት እንደትቀጥል፣ ከሕምሟም ነጻ እንድትሆን የመለኮት ጣልቃ ገብነት ያስፈልጋታል። ይህም እንዲሆን ሁሉም ወደ አምላኩ መጮኸ ያለበት ጊዜ አሁን ነው።
፪. ሥርቆት፣ ጉቦና ዝርፊያ
ሌብነትና ጉቦ የአገራችን መጣኔ ሀብት የሚጐዳ ሕመም ነው። ምድሪቱ ታማለች ስንል ኢኮኖሚው ታሟል ማለታችን ነው። ይህ ጉዳይ በአንድ ወቀት በኢትዮጵያ ፓርላማ ተነስቶ ጥልቅ ውይይት እንደተደረገበት ሁሉም ኢትዮጰያዊ ያውቀዋል። ገዥው ፓርቲ የኢትዮጰያ ኢኮኖሚ ጤናማ ነው ሲል ተቃዋሚዎች ደግሞ ኢኮኖሚው በጣም ታማሚ ነው። እንዲያውም አንድ ቀን ተዝለፍልፎ ሊወድቅ ሁሉ ይችላል ብለው ምላሽ ሰጥተዋል። ወያኔ ወደ አገራችን እንደገባ የመጀመሪያው ያደረገው ነገር ቢኖር የአገሩን አንጡራ ሀብት እየዛቀ በሰዎች ኪስ መክተት ነው። ሕዝባችንን ያማረረ ያጐሳቆለ፣ ቢያንስ የዜግነት መብቱ በአግባብ እንዳይከበር ያደረገ ፣ ምድሪቱን ከዳር እስከዳር የሸፈነ አደገኛ ሕመም ቢኖር ጉቦና ሥርቆት ነው። የኢትዮጵያ መንግሥት ጉቦ ወይም ሌብነት አይልም። ኪራይ ሰብሳቢነት ይለዋል። ካልሆነ ስኳር መላስ ይለዋል፣ ወይም ሙስና ይላል። ሙስናንና ኪራይ ሰብሳቢነትን እዋጋለሁ ይላል። ግን ሙስናውና ጉቦው መጠኑን እየጨመረ ሄደ እንጂ መፍትሔ አልተገኘለትም። በጉቦውና በሙስና የተዘፈቁት የመንግሥት አመራር አካላት፣ የፖሊቲካው ካድሬዎች፣ እና ገዥ ፓርቲ ያስቀመጣቸው የመመሪያ ኃላፊዎች በመሆናቸው ሕመሙ መድኃኒት ያልተገኘለት በዚህ ምክንያት ነው። እንዲያውም ሕመሟ ከጊዜ ወደ ጊዜም እየባሰ ሄደ። በቴሌቭዥኑና በራዲዮ ሙስናን እንዋጋ እያሉ ሕዝቡን ያጃጅላሉ። ሕዝቡ ጉቦ አይቀበል፣ መሬት የሚሸነሽነውና የሚሸጠው ተርታው ሕዝብ አይደለም፣ ወያኔና የወያኔ ካድሬዎች እንጂ! የህዝብና የመንግሥት ገንዘብ እየዘረፉ ኪሳቸው እየከተቱ በአጭር ጊዜ ሚሊየነር እየሆኑ ያሉትን ቁልፍ መሪዎችን ከእኩይ ተግባራቸው እንዲቆጠቡና እጃቸውን እንዲሰበስቡ መናገር ያለበት ለእነርሱ ሆኖ ሳለ በሌቦች እየተዘረፈ ያለውን ሚስኪን ሕዝብ ሙስናን ተዋጉ ይላል። ቀልድ ቢባል በሕዝብ ላይ መቀለድ አንድ ቀን ዋጋ ማስከፈሉ አይቀርም። የኢህአዴግ መንግሥት ጠላትን አሸንፌአለሁ የሚል፣ ከራሱ አልፎ የሌላውን አገር ሰላም አስጠብቃለሁ የሚል፣ በአፍሪካ ቀንድ በጐም ይሁን አሉታዊ ተጽዕኖ የማምጣት ብቃት አለኝ የሚል መንግሥት ነው። ይህ ሁሉ ብቃት ኖሮት ሀዝቦቿን የሚቦጠቡጠውን ሙሰኛ አደብ እንዲገዛ ያላደረገው አቅም አንሶት ሳይሆን መንግሥትራሱ ሙሰኛ ስለሆነ ነው። ያለ ጉቦ የሚፈጸም ጉዳይ በኢትዮጵያ ምድር ላይ እንደሌለ በአመራር መዋቅሩ ከላይ እስከታች ያሉ እያንዳንዱ ያውቃል። የትኛውም ቀላል ይሁን ከባድ ጉዳይ ያለ ጉቦ አይከናውንም። የሚከናወንላቸው ለወያኔዎችና ለፖለቲካ ድጋፊዎች ብቻ ነው። አገሪቱ የእነርሱ እንጂ የዜጋው አይደለችም። መነገድ የሚችሉት ወያኔዎችና የፖለቲካው ደጋፊዎች ብቻ ሲሆኑ ንግዳቸውን ሲነግዱም ሆነ ሲሸጡ ቀረጥ የማያስበረግጋቸው ናቸው። ዜጋው ግን የንግድ ፈቃድ ቢኖረውም ያንኑን ለማግኘት የሚከፍለው ጉቦ ሌላ ድርጅት ሊያራምድ ይችላል። በመሣሪያ አስፈራረቶም ሆነ ሰዓት እላፊ አወጆ የአገሪቱን አንጡራ ሀብት ማጋዝ ሥራዬ ብሎ ተያይዞታል። እግዜር የለሹ የደርግ መንግሥት ወንበዴ የሚል ስም የሰጠው ለዝርፊያ ያለውን መቋመጥ ስለታዘበው ይሆናል። አሁን ምድራችን በዝርፊያ የታምሰች ናት። እናት አገራችንን ብንወዳትም፣ በሰፈነባት እንደ ባህል እየተገነባ ባለው ሌብነትና ዝርፊያ እናፍራለን። ሌባ እናት በሰረቀች ቁጥር ልጆቿ ይሸማቀቃሉ፣አንገታቸውንም ይደፋሉ።
ነቢያት ስለ ኢኮኖሚው እድገት ይናገራሉ። መጻሕፍትም እየተጻፉ ናቸው። በየመድረኩ የምንሰማው ኢትዮጵያን እግዚአብሔር ይባርካታል የሚል ነው። አንዳንዶቹ ሌሎች የሚሉትን ሰምተው እንጂ በእርግጥም እግዚአብሔር ተናግአቸው አይደለም። በአገራችን የምንሰማው ትንቢት አብዛኛው የነቢያቶቹ የግል ምኞታቸው ነው እንጂ እግዚአብሔር የሚሰጣቸው መልእክት አይደለም። ምኞትና መልእክት ይለያያል።
3ኛ. ውሸትና ማታለል፡
መንግሥታችን ልማታዊ ነኝ ይላል ግን አይደለም። ዴሞክራት ነኝ ቢልም ዴሞክራሲው የማስመሰል፣የፖለቲካ ሽፋን ለማግኘት ሲል የሚያደርገው የቃላት ቅመማ ነው። በአገራችን ኢትዮጵያ ሕገ መንግሥት ቢኖርም ያ ሕገ መንግሥት የበላይ አይደለም። በአንድ ቀን ጉቦ ሊናድ የሚችል በአሸዋ ላይ እንደተሠራ ቤት ነው። እውነት እንነጋገር ካልን በአገራችን ላይ የመሪዎችና የካድሬዎች የበላይነት እንጂ የሕግ የበላይነት የለም። የኢሀአዴግ መንግሥት የሕገ መንግሥቱን ሥርዓት በሃይል ለመናድ የሚሹ ኃይሎች እያለ በሌሎች ላይ የሚፈረድ ቢሆንም ውሸትን እውነት አስመስሎ በመናገር የኢትዮጵያ መሪዎችን የሚያክል የለም። አንዱ ጄኔራል ሲናገሩ፡ የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዳር እስከ ዳር የወያኔን ሠራዊት ይወደዋል ያፈቅረዋል ማለታቸው ብቻውን ለዚህ ማሳያ ነው። ክ1997 ምርጫ ጋር በተያያዘ በተነሳው ረብሻ በመንግሥት ታጣቂዎች የተገደሉ ስዎች ጉዳይ ሲነሳ የመንግሥት ባልሥልጣናት መልስ ሲሰጡ ሰዎቹ የሞቱት ባንክ ሲዘርፉ ነው ማለታቸው ሌላው ማሳያ ነው። አፈሩን ገለባ ያርግላቸውና የሞቱ ጠቅላይ ሚኒስትራችን ደመወዛቸው ስድስት ሺህ ብር ብቻ ስለሆነ ባለቤታቸው ያንን እንደምንም አብቃቅተው እንደሚኖሩና በዓለም ላይ የመጨረሻ ዝቅተኛ ገቢ ያለው ሰው ማነው ቢባል እኒህ ጠቅላይ ሚኒስትር መሆናቸውን መስማታችን እንደ ተጨማሪ ማሳያ እንውሰድ። በምዕራቡ በኩል መሬት ለሱዳን ሊሰጥ የኢትዮጵያ መንግሥት እየተፈራረመ ያለው ለምንድነው ሲባል ለሱዳን ምንም መሬት አልተሰጠም፣ አንድም የኢትዮጵያ ገበሬ ከቦታው አልተፈናቀለም ማለቱ ሌላው ተጨማሪ ማሳያ ነው። መንግሥታችን ይህን ሁሉ እያለ መሬቱን ግን አሳልፎ እያሰጠ ነበር። ቴሌቭዝኑና ራዲዮ ቢሆን የኢህአዴግ መንግሥት ልሳን ስለሆነ እውነት ተናገረ ቢባል ሰዓት ብቻ ነው። ፖለቲካ በራሱ የቆሸሸ ጨዋታ ቢሆንም አሁን አመራር ላይ ያለውን መንግሥት ተከትሎ ወደ አገራችን የገባው የውሸት መንፈስ ግን የትም የሌለ ነው።
4ኛ. ሰብአዊ መብት ረገጣ
በዓለም አቀፍ ደረጃ የታውቁ የሰብአዊ ተሟጋቾች በኢትዮጵያ ውስጥ የሚደረገውን የመብት ረገጣ መስማት እጅግ የሚዘገንን ነው። በተለይም ከብሔራዊ ምርጫ ጋር በተያያዘ ብሶት የወለደው ጀግናው የኢህአዴግ ሠራዊት በሚወስደው ከመጠን በሚያልፍ እምጃ በመቶዎች የሚቆጠሩ ንጹህ ዜጎች ሕይወት ይቀጠፋል። የኢህአዴግ መንግሥት ኢትዮጵያን ከተቆጣጠረ ወዲህ የዩኒቨርሲቲ ተማሪዎችን ጨምሮ በግፍ የተገደሉ ኢትዮጵያውያን ቁጥር መገመት ከሚቻለው በላይ ነው። በሮሚያ ክልል በተቀሰቀሰው ተቃውሞ ወቅት ብቻ ሕይወት የመንግሥት ታጣቂዎች በወሰዱት ተመጣጣኝ ባልሆነ የግፍ ርምጃ ክ500 በላይ ንጹሐን ሰዎች ሕይወት ተቀጥፏል። አምኔስቲ ኢንተርናሽናል የተሰኘው መንግሥታዊ ያልሆነ ድርጅት እንደሚገልጸው ከ2015( እ ኤ አ) ጀምሮ በአንድ ዓመት ውስጥ 800 ስዎች ተገድሏል። ከዚህም በተጨማሪ መንግሥት አስታጥቆ በሕብረተሰቡ ውስጥ ያሰማራቸው ሠራዊት በንጹሐን ላይ የሚያደርሱት ከመጠን ያለፈ ጥቃት ዓለምን ሁሉ ያንገሸገሸ ነው። ምንም የፖለቲካ አቋም የሌላቸውንም ጨምሮ ያለ ፍርድ ቤት ውሳኔ ያለ ጠያቂ በእሥር ማጎር፣ ማሰቃየት፣ መገረፍ ፣ስብዕናን የሚያዋርዱ ቅጣቶችን ማድረስ ፣ ያሉበት እንዳይታወቅ ማደረግ ወዘተ ይገኙበታል። አሁን ያለ የአገራችን ስብአዊ መብት ረገጣ በየትኛውም ዘመናትና አገዛዝ ያልነበረ መሆኑ ግልጽ ነው።
ይህ በሽታ እየሰፋና መጠኑን እየጨመረ መሄዱ በሁሉም ዘንድ የታወቀ ነው። ይህቺን አገር ከዚህ ችግር የሚያላቅቃት መፍትሔ ፣ የበሽታዋም መድኃኒት ከየት ይመጣ? ከተባበሩት መንግሥታት? ከልዕለ ኃያሏ አሜሪካ? ከአፍሪካ ሕብረት? ወይስ ከአውሮፓ ህብረት? ኢትዮጵያን ለመፍትሔ ፍለጋ በአሜሪካን አገር ከጮኹ፣ መንገድ አጣብበው ኡኡታና እሪታ ካበዙ ዘመን የለውም። አሁን አሁን እሱም ተከልክሏል ወይ እነርሱ ስልችቶአቸው ተውት መሰለኝ ጋብ ብሏል። በሰማይ ንጉሥ በእግዚአብሔር እጅ ግን መፍትሔ አለ። እርሱ በሰዎች ልጆች መንግሥት የሚሰለጥን ነው። ምድራችሁን እፈውሳለሁ ያለው እርሱ ስለሆነ መፍትሔና መላ ፍለጋ በእርሱ ደጅ እሪ እንበል፣ ኡኡታም እናሰማ። እርሱ ምድራችንን የፈውሳታል ፣ ለገዥዎቻችንም ልቦና ይሰጣቸዋል፣ የሕዝባችን እምባና የግፍ የሚፈሰው ደም ያበቃል። የአገራችን ጉዳይ ፈውስ የሚያስፈልገው ሕመም በመሆኑ ለመድኃኒትጥ ፍለጋ መሮጥ አለብን። መድኃኒቱ በጦርነት አይገኝም፣የሃያላን አገሮች ቢሮ በር ላይ ተሰባስበው እሪታ በማሰማትም አይገኝም። መድሓኒቱ እንዲገኝ በፍጹም ልብ ወደ እግዚአብሔር በመመለስ ፊቱን ስንፈልግ ብቻ ነው። የአገራችን ፈውስ ከእግዚአብሔር ዘንድ እንጂ ከሌላ ቦታ ከየትም አይመጣምና። እግዚአብሔር አገራችንን የጐሳ ፖለቲካ፣ ሥርቆትና ዝርፊያ፣ውሸትና ማታለል እና ሰብአዊ መብት ረገጣ ከተባሉት ሥር የሰደዱ በሽታዎች አገራችንን ይፈውሳት! አሜን እንበል።

LikeShow more reactions
Comment
Comments
Workneh Koyra Pastor, it is so powerful and absolutely right. May the Lord heal our land and bless our country.
Manage


LikeShow more reactions
Reply8w
Silas Amenta Belete እውነትን በመግለጥ ላይ የተመሰረተውን መጣጥፍህን በጣም እወደዋለሁ ሸክምህን እጋራዋለሁ ሁሉን ለሚችል ጌታ እንደ ግለሰብና እንደ ቤተክርስቲያን በፀሎት ማስታወቅ ይጠበቅብናል ጌታ ይባርክህ መጋቢ ሳሚ
Manage


LikeShow more reactions
Reply8w
Jara Tekleab Pastor, you are right to the point and well explained. I hope our country will heal from these 5 Chronic deceases. May God give all Ethiopians his blessing to love one another and unite.
Manage


LikeShow more reactions
Reply8wEdited

Thursday, May 11, 2017

የተዋረድን ቢመስለንም የክብር ቀን ይመጣል፡፡

                                                            ከመጋቢ ሳሙኤል ሾንጋ

ይህንን ጽኹፍ ለማዘጋጀት ከመጀመሪያው ዕቅድ አልነበረኝም፡፡ ነገር ግን በየ15 ቀኑ እየጓዝኩ በሚሰብክባት የሰውዝፍልድ ሚቺጋን ኢትዮጵያ ወንጌጌላዊት ቤክ አባልና አገልጋይ የሆነች እህት በራዕይ መጽሐፍ 11 ፡ 4 ላይ ስለሚገኙ ስለ ሁለት ወይራዎች ምስጥራት እንድነግራት ስለጠየቀችኝ ለእርሷ ምላሽ እንዲሆን ብዬ ያዘጋጀሁትን ምላሽ ነው አሁን የማቀርብላችሁ፡፡ መቼም በመድረክ ማገልገል በተለይም ቃሉን እየተረጎምን የምናስተምር ከሆነ ከአገልግሎት በመልስ ሌሎች ክፍሎችንም እንድናብራራላቸው የሚጠይቁ ሰዎች አሉ፡፡ ይህ ደግሞ በጣም የሚያስደስት ነገር ነው፡፡ ይህንን ክፍል እንዳብራራላት የጠየቀቺኝን እህት እያሰገንኩ እኔም አሳቡን ለመመልከት ችያለሁ፡፡ ጭንቀቴ እንደ ፓስተሯ ለምታየኝ ቅንና የቃሉ ወዳድ ለሆነቺው እህቴ የተሳሳተ ነገር እንዳልናገር ነበር፡፡ እንግዲህ አሳቡን፡ካየሁና ለእርሷም ምላሽ ከሰጠሁ በኋላ ለራሴም ትልቅ መልእክት ስለሆነኝ  ጓደኞቼም እንዲያነቡት ባደርግስ ብዬ ስላሰብኩ ይኸውና ከነማብራሪያ ከዚህ እንደሚከተለው ስላስቀመጥኩ ተቋደሱት፡፡
የዮሐንስ ራዕይ መጽሐፍ በመጽሐፍ ቅዱስ ውስጥ ከሚገኙ ለመተርጎም ከባድ ከምንላቸው መጻሕፍት አንዱ ነው፡፡ ይህ የሆነበት ምክንያት መጽሐፉ አቡቀለም ሲስ ተብሎ ከሚጠሩት መጽሓፍት ጋር የሚመደብ ስለሆነ ነው፡፡ እንደዚህ ባሉት መጽሓፍት አንዳንድ አሳቦች ከተለመደው ውጭ በሆኑ ቋንቋዎች ወይም የአገላለጽ ዘይቤዎች ስለተነገሩ ትርጉሙን በቀላሉ ማግኘት አዳጋች ይሆናል፡፡ አቡቀለም ሲስ ማለት መገለጥ ወይም ራዕይ እንደማለት ነው፡፡
በምዕራፍ 11 ቁጥር 4 ላይ የተጠቀሱ ሁለቱ ወይራዎች እነማን ናቸው የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ ወደ ምንባብ ክፍል መሄድ ያስፈልጋል፡፡ በታላቁ መከራ ጊዜ በምድር ላይ ሊነሱ ስላሉት ሁለት ምስክሮች ፣ ሁለቱ ወይራዎች ወይም ሁለቱ መቅረዞች የሚናገር ሲሆን የክፍሉን ሙሉ አሳብ ለማግኘት ከቁጥር 1-13 ሙሉን ማበብ ያስፈልጋል፡፡ ይህ የንባብ ክፍል በራዕይ መጽሐፍ ውስጥ ከሚገኙ ሰባት ወዮዎች በሁለተኛው ውስጥ ያለ ነው፡፡ በተለይም ስለ ሁለቱ ምስክሮች ሦስት መሠረታዊ አሳቦችን እናገኛለን፡፡ 1. ስለ ሁለቱ ምስሮች አገልግሎት (3-6)፣ 2. ስለ ሁለቱ ምስክሮች አሟሟት( 7-10) እና 3. ስለ ሁለቱም ምስክሮች ትንሳኤ ( 11-13) እናያለን፡፡ 
ታዲያ እነዚህ ማናቸው የሚለውን ለመመለስ የሞከሩ ብዙ የስነ መለኮት አስተማሪዎችና ተማሪዎች አሉ፡፡ በዚህ ላይ የእግዚአብሔር ሰዎች በመከራው ጊዜ ስለ እምነታቸው ቢሰደዱም እግዚአብሔር ግን ለሕዝቡ የሚሆን መልእክት መስጠትን አልተወም፡፡ እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች በታላቁ መከራ ጊዜ ለእግዚአብሔር ሕዝብ እጅግ በጣም አስፈላጊዎች ነበሩ፡፡ እግዚአብሔር በዚህ ክፍል ውስጥ እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች እነማን እንደሆኑ አልገለጻም፡፡ ስለዚህ ነው የመጽሐፍ ቅዱስ ተርጓሚዎች የተለያዩ ትርጉሞችን መስጠት የቻሉት፡፡ እነዚህን የተለያዩ ትርጎሞቹን እንደሚከተለው አስቀምጬዋለሁ፡፡
1. ሙሴና ኤልያስ ናቸው፡፡ ይህንን ትርጉም የሚከተሉ ሰዎች በዮሐንስ ራዕይ ምዕራፍ 11 ላይ ያሉ ምስክሮች ሙሴና ኤልያስ በብሉይ ኪዳን ጊዜ ያደርጉ የነበሩትን አይነት ተአምራት ማድረጋቸው ስለተጠቀሰ የብሉይ ኪዳን ነቢያት የሆኑት ሙሴና ኤልያስ እንደገና ወደ ሕይወት ተመልሰው ይመጡ ይሆናል ብለው ነው የሚተረጉት፡፡
2. ሄኖክና ኤልያስ ይሆናሉ፡፡ በዚህ ትርጉም መሰረት እግዚአብሔር ሄኖክንና ሙሴን ሳይሞቱ ወደ ሰማይ እንደወሰዳቸው በብሉይ ኪዳን ስለተጸፋና አሁንም እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች ከሞት ከተነሡ በኋላ ሳይሞቱ መወሰዳቸው በምንባብ ክፍል ስለተጠቀሰ እነርሱ ይሆናሉ፡፡
3. ኤልያስና ሚልክያስ ይሆናሉ፡፡ መሲሁ ኢየሱስ ከመምጣቱ በፊት ኤልያስ ይመጣል ብሎ ሚልክያስ ስለተነበየ ኤልያስና ትንቢቱን የተናገረው ሚልክያስ ራሱ ይሆናል ብለው ያስተምራሉ፡፡
4. ያዕቆብና ጴጥሮስ ናቸው፡፡ እዚህ ሁለቱ ሮማውያን የኢየሩሳሌምን ቤተ ክርስቲያንን ባሳደዱበት ጊዜ የተገደሉና ለከፍተኛ እሥራትና ግርፋት ከዚያም ለሞት የተሰጡ በመሆናቸው በዚህ መከራ ጊዜ ከሙታን ተነስተው የሚያገለግሉ እነርሱ ይሆናሉ በሚል ነው፡፡
5. ቅዱሳን በሙሉ ናቸው፡፡ ይህንን አሳብ የሚሰጡ ሰዎች እንደሚናገሩት ሁለቱ ምስክሮች የተባሉት ሁለት ግለሰቦች ሳይሆኑ ሁለቱን የብሉይና የአዲስ ኪዳን መጻሕፍትን ይዘው በመከራ ውስጥ ላሉት ሁሉ የሚመሰክሩ ቅዱሳን ወገኖች ናቸው፡፡
እንግዲህ የምንባብ ክፍሉ ስለ ሰዎቹ ማንነት በግልጽ ባይነግረንም እነዚህ ሰዎች የእግዚአብሔርን መልእክት በጊዜው ላሉ አማኞች የሚተነብዩ ወንጌሉን የምስራች የሚሰብኩ መሆናቸው ግን እሙን ነው፡፡ አገልግሎታቸውም በትንቢተ ዳንኤል 12፡11 ላይ እንደተጠቀሰው ዓይነት ለ 1260 ቀናት ወይም 42 ወራት ነው፡፡ ያ ማለት ለሶስት ዓመት ተኩል ያገለግላሉ ማለት ነው፡፡ የዮሐንስን ራእይ በምናጠናበት ወቅት የትንቢተ ዳንኤልንም መጽሐፍን አንድ ላይ ማጥናት ያለብን ለዚህም ጭምር ነው፡፡ የትንቢተ ዳንኤልም መጽሐፍ እንደ ዮሐንስ ራዕይ ዓይነት የአቡቀለም ሲስ የሆኑ መልእክቶች አሉበት ፡፡ ስለዚህ ከዚህ ክፍል ያሉትን አሳቦች በሦስት ከፍለን እንይ፡፡
1. የሁለቱ ምስክሮች አገልግሎት
ሁለቱ ምስክሮች በሚገለግሉበት ወቅት ማቅ ለብሰው እንደሚሆን ዮሐንስ ይነግረናል፡፡ የእግዚአብሔር ቃል መጽሐፍ ቅዱስ በሙላት በሚሰበክበትና የእግዚአብሔር ክብር በምንቀሳቀስበት ወቅት በአንጻሩ ደግሞ ሰዎች ኃጢአትን ሲለማመዱ ሲያዩ ነቢያትና ነገሥታት ካህናትም ማቅን መልበሳቸው የእግዚአብሔር ፍርድ ስላለ ንስሐ መግባት በጣም አስፈላጊ መሆኑን ለማሳየት ነው፡፡ ለዚህም ኢሳ 12፡22፣ ኤር.4፡8፣ኤር 6፡26፣ ዮናስ3፡5፣6፣8፣ ማቴ 11፡21ን መመልከት ይቻላል፡፡
የሁለቱ ምስክሮች አገልግሎት ከምርኮው ወደ እሥራኤል አገር ከተመለሱ በኃላ ወደ ተሐዲሶ ለማምጣት ያገለገሉ የዜሩባበልና የካህኑ የኢያሱን አገልግሎት ይመስላል( ዘካርያስ 4፡2-3፣11-14)፡፡ ምክንያቱም እነዚህ መቅረዞች ተብለዋል፡፡ በዘካርያስ መጽሐፍ አንድ
መቅረዝ ያለ ሲሆን በዮሐንስ ራዕይ ግን ሁለት መቅረዞች ተጠቅሰዋል፡፡ በዮሐንስ ራዕይ በራሱ ደግሞ መቅረዝ የክርስቶስን ቤተ ክርሰቲያን የሚወክል መሆኑን ደግሞ በመዕራፍ አንድ ላይ መመልከት ይቻላል( 1፡12-13)፡፡ በዘካሪስ ላይ ያለው መቅረዝ መንፈስ ቅዱስን የሚያመለክት ሲሆን በታላቁ መከራ ጊዜ የሚነሡ ሁለቱ ምስክሮች ( ሁለቱ መቅረዞች) የአገልግሎታቸውን ኃይል የሚቀበሉት ከመንፈስ ቅዱስ ነው፡፡ ይህን ኃይል ከመንፈስ ቅዱስ ከተቀበሉ በኋላ በመቅደሱ ሆነው ልክ እንደ መቅረዝ የጌታን ብርሃን የሚሳዩ የእግዚአብሔር እውነተኛ ምስክሮች ይሆናሉ፡፡ በመንፈስ ቅዱስ ተደግፈው ዓለምን ሁሉ ለሚቆጣጠረው እግዚአብሔር ምስክሮች ይሆናሉ፡፡
ሁለቱ ምስክሮች ነቢዩ ኤልያስ በ2ኛ ነገስት 1፡10-14 እንዳደረገው ሊጎዱአቸው በሚመጡ ጠላቶቻቸው ላይ እሳትን ከሰማይ በመጥራት ራሳቸውን ለመከላከል የሚችሉበት እግዚአብሔር ኃይል እንደሚሰጣቸው እንመለከታለን፡፡ ከእነዚህ ምስከሮች አፍ እሳት እንደሚወጣ መናገሩ ቀጥተኛ ትርጉም ሊሆን ይችላል፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን ተአምራትን እንዲያደርጉ በኃይል እንደሚሞላቸው ከክፍሉ እናገኛለን፡፡ ልክ ሙሴና ኤልያስ ሲያደርጉ እንደነበረው ሁሉ ውሃን የመለወጥና መቅሰፍትን በምድር ላይ የማምጣትና ዝናብ እንዳይወርድ የመከልከል ሥልጣን እንደሚሰጣቸው እንመለከታለን( ዘጸአት 7፡17-21፣ 9፡14፣ 11፡10፣ 1ሳሙ.4፡8፣ ፡፡ የመጽሐፍ ቅዱስ ትርጓሚዎች ሁለቱ ምስክሮች ( ሁለቱ ወይራዎች) ኤልያስና ሙሴ ናቸው ያሉበት ምክንያትም ይህ ነው፡፡
2. የሁለቱ ምስክሮች ሞት
አገልጋዮች በታላቅ ኃይልና ጸጋ ሲያገለግሉ ሁል ጊዜ አድፍጦ የሚጠብቃቸው ጠላት እንዳለ ማወቅ ይኖርብናል፡፡ አውሬው እነዚህን ሰዎች ሊገድላቸው የሚችለው ግን እነርሱ ከእግዚአብሔር የተሰጣቸውን አገልግሎት ከጨረሱና እግዚአብሔርም የፈቀደለት እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ምስክሮቹ ከትክክለኛ ጊዜአቸው በፊት ሊሞቱ አይችሉም፡፡ የእግዚአብሔር ጊዜ ሲደርስና እነርሱም አገልግሎታቸውን ሲያጠናቅቁ እንዲገድላቸው ተፈቀደለት፡፡ ይህ አውሬ ሐሰተኛው ክርስቶስ ነው፡፡ አውሬው የሁለቱ ምስክሮች ሬሳ በመንገድ ላይ ተኝቶ ሁሉም እንዲያያቸው ማድረጉ እነርሱን ማዋረዱ ሲሆን ይህም በቀድሞ የእግዚአብሔር ቃል በተነገረባቸው ዘመናት ተከናውኗል( መዝ 79፡2,3)፡፡ ጠላት አጋጣሚውን ካገኘ በሙሉ ኃይሉ በመጠቀም የእግዚአብሔር የሆኑትን አገልጋዮች ያዋርዳል፡፡ እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች የሞቱባትና የተዋረዱባት ከተማ ከሰዶምና ከገሞራ ጋር ተመሳሳይነት ያላት፣ በከፍተኛ ሁኔታ በደል፣ የምግባር ውድቀት፣ እግዚአብሔርን አለመውደድና ሕዝብን የመጭቆን ሁኔታ የሚታይባት ናት፡፡ ጌታችን ኢየሱስ የተሰቀለባት ከተማም ከዚህ ጋር ተመሳሳይነት ያላት ናት፡፡ ምክንያቱም ሐሰተኛው ክርስቶስ ከፍተኛ ተጽእኖ እያሳደረ ስለሆነ ነው፡፡ ከላይ እንደተመለከትነው አገልግሎታቸው በታላቅ ተአምራት ሲታጀብ የነበረ ሁለቱ ወይራዎች አሁን ተገድለው ሬሣቸው በመንገድ ላይ ተጥሎ ሁሉም እየመጣ ያየው ጀመር፡፡ ጠላት የእግዚአብሔርን አገልጋዮች ሲያዋርድ እንደዚህ ነው፡፡
የእነዚህ ሰዎች ሬሳ የወደቀው በአንድ ከተማ ሲሆን ቃሉ ግን ከነገድ ከቋንቋ አህዛብ የሆኑ ሁሉ በመንገድ ላይ የወደቀውን የሁለቱ ምስክሮችን ሬሣ ለሶስት ቀን ያዩታል፡፡ እንዴት አድርገው በሁሉም ቦታ ያሉ ሰዎች ይህንን ሊያዩ ይችላሉ፡ እንግዲህ በጊዜ ከፍተኛ ስልጣኔ ስለሚሆን ምናልባት ሁሉም በያለበት ሆነው በቴሌቭዥን ወይም በሌላ የመገናኛ መንገድ ሊመለከቱት ይሆናል፡፡ ወይም ደግሞ ሕዝቦች ከተለያዩ ወገኖች ተውጣጥተው በወቅቱ እነዚህን ሰዎች ለማየት ሲሉ በኢየሩሳሌም የሚገኙበት ሁኔታ ሊፈጠር ይችላል፡፡ በዚህ መጽሐፍ ውስጥ በታላቁ መከራ ጊዜ ሰው ሁሉ የተደሰተበትን ሁኔታ የሚያሳይ ብቸኛው ታሪክ ይህ ነው፡፡ የምድር ወገኖች በእነዚህ ምስክሮች ሞት ምክንያት በጣም ይደሰታሉ ምክንያቱም ከዚያ በኋላ የእግዚአብሔርን የማዳን ወንጌል ስለማይሰሙ ነው፡፡ ልብ እንበል የወንጌል ሰባኪዎች፣ አስተማሪዎች ቅዱሳም ምስክሮች ሲወድቁና ሲዋረዱ ወንጌልን የመስበኩ ሥራ የሚቋረጥ ስለመሰለው አውሬውና ተከታዮቹ አጅግ አድርገው ይደሰታሉ፡፡ ይህኛው በምድር ላይ የመጨረሻው የሰው ልጆች ፈንጠዚያ ነው፡፡ ከዚህ በኋላ ሌላ ደስታ የሚባል በምድር ላይ አይሆንም ወይም ያበቃል ማለት ነው፡፡ ይህ የሚገርም ነው፡፡
3. የሁለቱ ምስክሮች ትንሳኤ
በዚህ ክፍል የሚያስደንቀው ነገር ሁለቱ ምስክሮች ሞተዋል ተብለው ከነገድ ከቋንቋ እና ከየአገሩ ሰዎች ሁሉ ተሰብስበው ደስታቸውን ከገለጹ በኋላ እንደገና ተነስተው፣ ወደ ሕይወት ተመልሰው መታየታቸው ነው፡፡ ከእግዚአብሔር ዘንድ የወጣው ሕይወት መንፈስ ለሞተው ሰውነታቸው ሕይወትን እንደሰጠ እንመለከታለን፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለሞተው ሕይወትን በመስጠት የሚታወቅ አምላክ ነው( ሕዝ 37፡5፣10፣ሮሜ 4፡17)፡፡ የሞቱ ምስክሮች በድን ሰውነታቸው በሰዎች ፊት በእግር መቆሙ በሞታቸው ለተደሰቱት ጠላቶቻቸው ሁሉ ድንጋጤ ሊፈጥር የሚችል ነው፡፡ የእግዚአብሔርንም ሆነ የሰውን የሆኑ ጠላቶችን እግዚአብሔር የሚያዋርደውና የሚስደነግጠው እንደዚህ ዓይነት ተአምራቶችን በማሳየት ነው፡፡ ይህ ብቻ ሳይሆን በዓይናቸው ከሚያዩት ድንቅ በተጨማሪ ከሰማይ የመጣው ድምጽ የበለጠ አስደንጋጭ የሚሆን ነበር፡፡ እንዲህ ነው የሚለው “ወዲዚህ ውጡ”፡፡ ከዚያም እነርሱም ለጣላቶቻቸው እየተመለከቱአቸው በደመና ወጡ፡፡ አውሬ ሐሰተኛው ወይም ሰይጣን መግደል ይችላል፣ ሬሳንም ማዋረድ ይችላል፣ ግን ከእግዚአብሔር ዘንድ የሚመጣውን ትንሳኤና በክብር መውጣትን ሊከለክል አይችልም፡፡ ተገድለው ሬሳቸው እንኳ እንዳይቀበር ተደርገው የተዋረዱና በውርደታቸው ጠላቶቻቸው የተደሰቱበት እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች ወደ ሰማይ የወጡት በእግዚአብሔር ድምጽ ነው፡፡ ይህ ድምጽ የጌታቸው የኢየሱስ ድምጽ ሊሆን ይችላል ምክንያቱም በራዕይ መጽሐፍ ውስጥ ለባሪያዎቹ ይገለጥና ይናገራቸው የነበረው የሞትንና የስዖልን መክፈቻ ቁልፍ የያዘውና በሰባቱ ወርቅ መቅሮች መካከል ይመላለስ የነበረው ኢየሱስ ነውና፡፡ ዛሬ በተለያዩ ሁኔታዎችና ምክንያ የተዋረዳችሁ ካላችሁ፣ የተሰበራችሁና የወደቃችሁ ካላችሁ፣ ከጠላቶቻችሁም ሲፈነጥዙባችሁ እያያችሁ ቅስማችሁ የተሰበረ ልባችሁ የወረደባችሁ ወገኖቼ ዛሬ ለእናንተ የምሥረች አለኝ፡፡ የሞትና የሲዖል መክፈቻ ቁልፍ ያለው ጌታ የናዝሬቱ ኢየሱስ ሞትን ድል አድርጎ ተነስቷል ፣ ውርደታችሁንም በክብር ይለውጥ ዘንድ አለ፡፡
እነዚህ ሁለቱ ምስክሮች ወደ ሰማይ የወጡት በደመና ሲሆን ይህም “ሸክና ግሎሪ” ተብሎ የሚጠራውን የእግዚአብሔርን ክብር የሚያንጸባርቅ ነው፡፡ ደመና የእግዚአብሔር ክብር ምሳሌ ነው፡፡ እነርሱ ወደ ሰማይ የወጡበት ሁኔታ ከጌታ ከኢየሱስ አወጣጥ ጋር ይመሳሰላል፡፡ አንደኛ ሰዎች እያዩ፣ ሁለተኛ በደመና ነው የተወሰዱት( ሐዋ 1፡9)፡፡ ይህ የክብር መነጠቅ በብሉይ ኪዳን ከኤልያስ
መነጠቅ ጋር ተመሳሳይነት ያለው ነው(2ኛ ነገሥት 2፡11)፡፡ እንደዚሁም ደግሞ አማኞች በደመና እንደምንነጠቅ የእግዚአብሔር ቃል ይነግረናል( 1ኛ ተሰሎንቄ 4፡17)፡፡ በሞታቸው የተደሰቱ ፣ በውርደታቸውም የፈነጠዙና የቧረቁ ጠላቶቻቸው ዓይናቸው እያየ ፣ ጆሮአቸውም እየሰማ ሲነጠቁ ደግሞ ምንም ማለት አልተቻላቸውም፡፡ ቁጥር 13ን በምንመለከትበት ጊዜ የምድር መናወጥ 7000 ሰዎችን ሲገድል ሐሰተኛው ክርስቶስ ሊያድናቸው እንዳልቻለና በዚህ ያሉት ደግሞ ለእግዚአብሔር ክብር እንደሰጡ እንመለከታለን፡፡ ሰይጣን ለጊዜው ኃይል ያገኘ እና ያሸነፈ ይምሰል እንጂ እግዚአብሔር ግን ክብሩን ሳይወስድና ባሪዎቹንም ሳያከብር በፍጹም አይተውም፡፡ እንግዲህ ከሰባቱ ወዮዎች የሁለተኝ ወዮ የተጠናቀቀው አገልጋዮች ሞት በሕይወት፣ ውርደታቸውንም በክብር ለውጦ ራሱም ከጠላቶቹ ሁሉ ክብርን በወሰደበት አስደናቂ ክንውን ነው፡፡ ሃሌሉያ

Thursday, April 6, 2017

እንጀራው


በዚህ ሳምንት እኔና ውድ ባለቤቴ የወር አስቤዛችንን ( ቀለባችንን ማለቴ ነው) ለመሸማመት ከመኖሪያ ቦታችን ትንሽ ራቅ ብሎ ወደሚገኘው ገበያ አዳራሽ ሄድን፡፡ የገበያ ቦታው ሜድቴራኒያን ፉድ ማርኬት Mediterranean food market ተብሎ የሚጠራ ነው፡፡ ኢትዮጵያውያንና ኤርትራውያን ከሌሎች ገበያ አዳራሾች ሁሉ ይልቅ ይኸኛውን አዘውትረው የሚጎብኙበት ትልቁ ምክንያት የአበሻ ምግብ ለመሥራት የሚያስችሉ ቅመማቅመሞች በየዓይነቱ ስለሚገኙበት ነው፡፡ ለምሳሌ ፡ በርበሬ፣ ኮረርማ፣ እርድ፣ ቀረፋ ፣ ጥቁር አዝሙድ፣ ምጥምጣ፣ ቡና፣ ወዘተ ሁሉም በየዓይነቱ ይሸጥበታል፡፡ ቅመሞቹ በትናንሽ ብልቃጦች እየታሸጉ በላያቸው ላይ ምንነታቸውን የሚያሳይ ጽሑፍና መለያ ቁጥር ከታተመባቸው በኋላ በተመደበላቸው መደርደሪያ ላይ በተርታ ተደርድረው ይገኛሉ፡፡ እንዲያው ባንገዛቸውም እንኳን እነዚያን ማየት ለዓይን ምግብ ነው፡፡ ታዲያ በአገር ቤት ሳለን እንደነበረው በትንሽ ብር ፌስታል ሞልቶ መመለስ ያለ እንዳይመስለን አደራ፡፡ በአንዲት ትንሽ ብልቃጥ የታሸገችው በርበሬ ዋጋ አይቶ በአገራችን ገንዘብ ካሰሉት ዋጋው ያስደነግጣል፡፡ ስለዚህ አንድ ነገር ለመግዛት ሲታሰብ በአገር ቤቱ ገንዘብ ማስላት አይታሰብም፣ ማስላቱም ተገቢ አይደለም፡፡ 
የአሜሪካኖች ምግብ በአጭር ጊዜ ውስጥ ያልታሰበ ቦርጭ እያሸከመ ስለሚያስቸግር ከዚህ ሁሉ እዳ ውድም ቢሆን የአገራችንን ምግብ ለምን አልበላውም በሚል እዚህ አገር ከገባንበት ጊዜ ጀምሮ ሽሮና እንጀራ ተለይቶን አያውቅም፡፡ ለታናሽ ልጃችን ፌቬን ደግሞ የአሜሪካኖች ምግብ ተመራጭ ብቻ ሳይሆን ከተመራጭ በላይ ነው፡፡ አልፈ አልፎ እንገዛላታለን እኛም የምንቀማምሰው በእርሷ ምክንያት ነው፡፡ ከፈቀድንላትማ ያለ እርሱ ባትበላ ደስታውን አትችለውም፡፡ እውነት መናገር ይሻላል የአሜሪካኖች ምግብ ሲጣፍጥ አይጣል ነው፡፡ ቢሆንም የሽሮን ውለታ መርሳት ጥሩ አይደለም ብለን ስለመከርናት እግዘር ይስጣትና እሺ ብላ ከእኛ ጋር የአበሻውን ምግብ በሥነሥርዓት እየበላችው ነው፡፡ ከምግብ ሁሉ ታማኝና ባለውለታችን ሽሮ ነው፡፡ መሸለም ቢያስፈልግ በመጀመሪያው የክብር መዳሊያ መጥለቅ ያለበት በሽሮ አንገት ነው፡፡ አንድም ቀን ሰልችቶን አያውቅን ፣ እኛም አንሰለቸውም፡፡ ይኸውና ሽሮአችን ባሕር ተሸግሮ በመምጣት የተለመደ አገልግሎቱን እየሰጠን ነው፡፡ ባለቤቴ ተዋበች ሌላ ማንኛውንም ምግብ ብትበላ እንጀራ ካልቀመሰች የሆነ ነገር የሚጎድልባት ይመስላታል፡፡ በፌቬንና በእርሷ መካከል ያለው ልዩነት በጣም ሰፊ ነው፡፡ እኔ ባለቤቴን አልፌ አልፎ እመክራታለሁ፡፡ ታበዥዋለሽ እላታለሁ፡፡ እምቢ ስትለኝ “ቃሉ ሁሉንም በልክ አድርጉ ይላል” ብዬ ልሰብካት ብሞክር የቱጋ ነው የጻፈው ትለኛለች፡፡ የተጻፈ ነገር ካለ ንገረኝ እንጂ ያልተጻፈውን አታንብብ ትለኛለች፡፡ በመጽሐፍ ቅዱስ አጠናን ዘዴ ውስጥ “አውድ” የሚባል ነገር መኖሩን በሰበብ በአስባቡ የነገርኩአትን ይዛ “አውድ ጠብቅ” እያለች ወደ እኔ ታነጣጥርብኛለች፡፡ በገዛ እጄ ስለ አውድ ነግሬአት ራሴው አፍ አጣሁ፡፡ እንዲያውም የእንጀራና የቡና ፍቅር እየባሰባት መሄዱን ሳይ “ይህ የእንጀራ ፍቅር በዝቷል፣ ወደ ሰማይም ሄደሽ እንጀራ እበላለሁ እንዳትይ እዚያ እንጀራ የሚባል ምግብ አይኖርም ይልቁንስ የተሻለና ከሁሉም የላቀ ሕይወት ነው የሚጠብቀን እንጂ” እያልኩ ሊሰብካት ቢሞክር አሁንም “ይህ ትምህርት ከእውነተኛው አስተምህሮ ጋር ስለጣጣሙ እርግጠኛ ሁን እንጂ እኔ መንግሥተ ሰማይ ሄጄ እንጀራ አልጋግርም የሚጋግርልኝም ይኖራል ብዬ አላስብም” ትለኛለች፡፡፡ ባለቤቴንና ልጀቼን ይህንን አታድርጉ ብዬ በቃል ጥቅስ ከመገሰጼ በፊት አውዱን በጥንቃቄ የመመልከት ግዴታ ውስጥ ገብቻለሁ፡፡ ያውም እኔው ራሴ አውድ context ስለሚባል ነገር ነግሬአቸው ያመጣሁት መዘዝ ነው፡፡ እኔ የሚቀለኝና ነጻነት የሚሰማኝ በመነቃቂያ ኮንፍራንስ ስሰብክ ነው፡፡ እዚያ ከየት አመጣኸው የሚል የለም፡፡ የተሳሳተም ቢሆን ተናግረው አሜን በሉ ሲባል አሜን የሚባልበት ቦታ ነው፡፡ እኔ እዚያም ቢሆን አውድ እጠብቃለሁ እንጂ ምክንያቱም ወደ ቤት ስመለስ ባለቤቴ “እሺ የዛሬው አገልግሎት እንዴት ነበር ታዲያ?" ብላ ሳትጠይቀኝ አልፋ አታውቅም፡፡ እኔም ‘ጌታ ይመስገን በጣም ጥሩ ነበር” እላታለሁ፡፡ እዚያጋ ቢያበቃ መልካም ነበር ግን አያበቃም፡፡ “ስለ ምን ሰበክ?” የሚለው ጥያቄ ይከተለኛል፡፡ ይህን ጊዜ ከስብከቴ መካከል ደግ ደጉን መርጬ በጥንቃቄ እነግራታለሁ፡፡ ባለቤቴ አገልግዬ ስመለስ በጥያቄ ማጣደፍ ብቻ ሳይሆን በጌታ የተሳካ የስብከት አገልግሎት እንዳቀርብ አጥብቃ ትጸልይልኛለችና ስለ እርሷ ጌታን አመሰግናለሁ፡፡ ታዲያ በእኔ ቤት መንፈሳዊ ነጻነት ፣ በነጻነት መስበክ፣ ጥቅስ እየጠቀስኩ አንዱን ከአንዱ ጋር አገናኝቼ ማሳመን በቀላሉ እልሆን እያለ መጥቷል፡፡ በመሆኑም ደስተኛ ነኝ፡፡ ባለቤቴንና ልጆቼን እግዚአብሔር ስለሰጠኝ ምስጋናዬም የላቀ ነው፡፡
ባለቤቴ ቡናንም ስትወድ አይጣል ነው፡፡ እኔ ደግሞ ቡና አልጠጣም፡፡ ጧትና ማታ ቡና ካላፈላሽ እያልኩ የማስቸግር ባል ባለመሆኔ ራሱ ልታመሰግነኝ ሲገባት “ባትጠጣ ሙሉ መብት አለህ፣ ማንም በግድ ጠጣ አይልህም፣ ደግሞ ብትጠጣም ችግር የለውም ለራሴ ሳፈላ እግሬ መንገዱን ትጠጣለህ” ትለናለች፡፡ይህ እኮ በእኛ ቤት የሴቶች እኩልነት ብቻ ሳይሆን የሴቶች የበላይነትም መኖሩንም ያሳያል፡፡ አሁን አሁን በተለይም ወተት በቡና የሚባለውን በትንሽ በትንሹ ስትሰጠኝ ቀየችና ለእኔ በማይገባኝ ሁኔታ የቡናውን መጠኝ ከቀን ወደ ቀን በዛ እያደረገች ምን አለፋችው በቡና ሱስ አስያዘቺኝ፡፡ አሁን በቁጥጥሯ ሥር ገብቻለሁ፡፡ በአገሬ ሳለሁ ለቡና ሱስ ያልተንበረኩ ሰው አሁን ከምሳ በኋላ ያቺን ወተት በቡና የምትለዋን ካልጠጣሁ ይደክመኝ ጀመረ፡፡ 
ለማንኛም እኔና ባለቤቴ ወደ ሜዲትራኒያን ገበያ አዳራሽ የሄድነው ጤፍ፣ ገብስና ቡና ለመግዛት ነው፡፡ እዚያ የኢትዮጵያ ቡናም አለ፡፡ባለቤቴ የምትፈልገውን ዕቃ እየመረጠች በጋሪው ላይ ስታስቀምጥ የእኔ ሥራ ጋሪውን እየገፋሁ ከኋላዋ መከተል ነው፡፡ እርሷ የመረጠችውን ብቻ ነው እንጂ የእኔ ምርጫ ውሃ አያነሳም፡፡ ከኋላዋ ሆኜ ያንን ጋሪ እየገፋው እያለ ዓይኔ በአንድ ነገር ላይ አረፈ፡፡ ከፊት ለፊታችን ባለው ጠሬጴዛ ላይ በሚያምር ንጹሕ ላስትክ ታሽጎ የተደረደረ ደስ የሚል ነገር፡፡ ምግብ ነው ታዲያ! ገበያተኞች አንዱ ከሌላው እየተከተሉ የሚያነሱት፡፡ ገበያ አዳራሹ የዐረቦች በመሆኑ ምክንያት ብዙ ዐረቦች ይገበዩበታልና እነርሱም ያንን ሲያነሱ አየሁ፣ ሶማሊያውያንም ፣ ሱዳናውያንም በየተራ እየመጡ ሲወስዱ አየሁ፡፡ እኔም ተጠጋሁና አይቼ ልቤን ደስ አለው፡፡ ለባለቤቴ አሳየሁአት፣ አየሽው ይህንን ነገር አልኩአት፡፡ ለካ እርሷ ከእኔ በፊት አይታዋለች ግን እንደ እኔው አልገረማትም፡፡ ነገሩ እንጀራ ነው፡፡ እንጀራ በዚህ ገበያ ሲሸጥ ከዚያም አልፎ ደግሞ ኢትዮጵያውያን ያልሆኑትም ጭምር ተሻምተው ሲወስዱ አታይም እንዴዬ አልኳት፡፡ ያውም እኮ ነጭ ወረቀት የመሰለ እንጀራ እኮ ነው፡፡ የእንጀራ ፍቅር የባለቤቴን ያህል ባይሆንም እንጀራን እወደዋለሁ ፡፡ የአገሬ ምግብ እንደዚያ ሲሸጥ በማየቴ ኩራት ኩራት አለኝ፡፡ በአገራችን የነጭ ጤፍ እንጀራ የሚበላው ሀብታም ሰው ቤት ነው ፡፡ ይህ ደግሞ ከንጣቱ ጋር ልስላሴው ራሱ ብላው ብላው የሚያሰኝ ነው፡፡ ነገር ግን እንጀራ ወዳድ ባለቤቴ ያሳየችው ቸልተኝነት አንድ ጥየቄ እንድጠይቃት አደረገኝ፡፡ ይህንን እንጀራ አልወደድሺውም አልኳት፡፡ እርሷም መልሳ እንዲህ አለችኝ “እንጀራ ይመስልሃል? ይህ እኮ እውነተኛ እጀራ ሳይሆን ዱቄቱን ሳልፍራይዜር ከሚባል ኬምካል ካር ቀላለቅለው ስለሚጋግሩ የነጣው በዚያ ምክንያት ነው የለሰለሰውም ለዚያ ነው፡፡ እውነተኛ እንጀራ ግን እንደዚህ አይለሰልስም አይነጣምም፡፡ ይህኛው ሁለትና ሦስት ቀን እዚህ ቢውል አይደርቅም አይሰባበርም፡፡ እውነተኛው እንጀራ ግን ጠሬጴዛ ላይ እንደዚህ አይቀመጥም ፣ በልዩ ጥንቃቄ በኮባና በሌሎች ቅጠሎች ተሸፋፍኖ በእቃ ውስጥ ነፋስ በማይነካው መልኩ ይቀመጣል፣ ይህኛው እንጀራ ከኬሚካሉ የተነሳ ለጤና ጎጂ ሲሆን እውነተኛው ግን በጣም ጤናማ ነው፣ ጤፋችን ብረት በተባለ ንጥረ ነገር የበለጸገ ስለሆነ ለጤና ጠቃሚ ነው፣ አሁን እኔ የጤፉን ዱቀት ወስጄ ስጋግረው የሚወጣው እንጀራና ይህኛው እንጀራ በምንም ሊገናኙ አይችሉም” አለችና አስዳችኝ፡፡ 
ከዛ በኋላ ራሴን ጠየቅኩኝ እነዚያ ሰዎች ታዲያ እንጀራ እንጀራ እያሉ የሚሻሙት ለምንድነው አልኩ፡፡ መልሱ እውነተኛውን እንጀራ ስለማያውቁ ነው፡፡መለስለሱንና መንጣቱን እንጂ በማስመሰል የተሠራ የሀሰት እንጀራ መሆኑን አላውቁትም ማለት ነው፡፡ ሐሰት መሆኑን የምታውቀው ኢትዮጵያዊቷ ባለቤቴ የእውነተኛው እንጀራ ጋጋሪ ኢትዮጵያዊት ስለሆነች ነው፡፡ በመሠረቱ እንጀራ ከመነሻው የኢትዮጵያውያን ባህላዊ ምግብ እንጂ የዓረቦችም የሶማሊያውያንም አይደለም፡፡ የሱዳኖችም ምግብ አይደለም፡፡ የኢትዮጵያውያን ምግብ ነው፡፡ ስለዚህ ኢትየጵያውያን ሐሰተኛውን እንጀራ ከእውነተኛው የመለየት ብቃት አላቸው፡፡ ሌሎች ግን ይህ ብቃት ስሌለላቸው በብረት የበለጸገውን የጤፍ እንጀራ ሳይሆን ኬምካል የተሞጀረበትን ነጭ እንጀራ ይበሉታል፡፡ 
ከዚህ የተማርኩት አንድ መንፈሳዊ ቁም ነገር አለ፡፡ ዛሬ በቤተ ክርስቲያን የሐሰት አስተማሪዎችንና የሐሰት ትንቢቶችን፣ ተአምራቶችን እንዲሁ በቀላሉ ልንለያቸው አንችልም፡፡ እውነተኛውን ትምህርት ካላወቅን በቀላሉ እንወሰድባቸዋለን፡፡ የሐሰት ትምህርቶች ይመርካሉ፣ ብዙዎች ይከተሉአቸዋል፣ ያደንቁአቸዋልም፡፡ ነገር ግን ከእውነተኛው ትምህርት ጋር ሲያስተያዩት ውስጣቸው በገዳይ መርዝ የተመላ ነው፡፡ እውነተኛው እንጀራ ዋጋው ውድ ሲሆን ሐሰተኛው ደግሞ ቀለል ባለ ዋጋ እንደሚገኝ ሁሉ የስህተት ትምህርትቶችና ትንቢቶች እንደ ልብ ይገኛሉ፡፡ ሐሰተኛውን ከእውነተኛው ለመለየት ቀላሉ መንገድ እውነተኛውን ትምህርት በሚገባ ማወቅ ነው፡፡ባለቤቴ ኢትዮጵያዊ በመሆኗ እውነተኛውን እንጀራ ስለምትጋግር ሱዳናውያንና ሶማሊውያን የሚገዙት ሳልፍራይዜር ያለበት እንጀራ እንደምግብም አልታይ አላት፡፡ እኔም ምስጥሩም ስለማላውቅ ልቤ በዚያ እንጀራ ተማርኮ ነበር፡፡ እንደዚሁም ሁሉ ቤተ ክርስቲያን በሐሰት ትምህርትና በጤናማ ትምህርት፣ በሐሰት ትንቢትና በእውነተኛ ትንቢት ፣በሀሰት ተአምራትና በእውነተኛው ተአምራት መካከል ያለውን ልዩነት ምዕመናን ተረድተው በሐሰተኛው መርዝ እንዳይጠቁ እውነተኛውን ትምህርት በማስጨበጥ ልትተጋ ይገባታል፡፡ ፈጣሪ በቸርነቱ ይጠብቀን ይርዳንም ፡፡ አሜን

ረጅም ነኝ ግን ሰሞኑን ቁመቴ የማጠሩ ነገር ኣሳሰበኝ፡፡




ረጅም ነኝ ግን ሰሞኑን ቁመቴ የማጠሩ ነገር ኣሳሰበኝ፡፡
እኔ ስለራሴ የተረዳሁትና ሰዎችም የሚመሰክሩልኝ በጣም ረጅም እንደሆንኩ ነው፡፡ እንዲያውም በቤተሰባችን ብቻ ሳይሆን በተወለድኩበት አካባቢ እንደ እኔ ያለ ረጅም ሰው የለም ማለት እችላለሁ፡፡ ለቀበሌያችንና ለወረዳችን የመረብ ኳስ ስጫወት በጣም ነበር የማስደስተው፡፡ በቤተክርስቲያን ስናገለግልም መዘምራን በደረጃ ላይ ሲቆሙ እኔ ከፊት ባለው ደረጃ ላይ ከቆምኩኝ በሶስተኛ ደረጃ ላይ ከቆሙት ጋር እኩል እሆናለሁ፡፡ በኳየር አገልግሎት ጊዜ ከኋላ መቆም የማልፈልገው ጭንቅላቴ ኮርኒሱን ስለሚነካብኝ ነው፡፡ ስለዚህ ፊቴን ወደ ሌሎች መዘምራን አዙሬ ጎኔን ለጉባኤው ሰጥቼ ከዳር በኩል እቆማለሁ፣ ከዚያ መዘምራኑ ከያዙት ከየትኛውም ደብተር ላይ እያየው መዘመር እችላለሁ፡፡
ወደ ስብከት አገልግሎት ስገባ ከመዘምራን ተለየሁ እንጂ መዘምራን ሲያገለግሉ ደስ ይለኛል፡፡ የዛሬውን አያርገውና ኳየሮች የሚዘምሩት መዝሙር ለረጅም ጊዜ ከልብ አይጠፋም ነበር፡፡ በመከራም ቀን እንደ ትንቢት ቃል የቅዱሳንን ልብ ደግፏል፡፡ ለምሳሌ “ድሉ የጌታችን ነው ፣ድሉ የአምላካችን ነው ድሉ” የሚለውን መዝሙር የሰማሁት በኢትዮጵያ ዘመን አቆጣጠር በ1973ዓ.ም ማለትም ከ36 ዓመት በፊት ነው፡፡ ሌሎችም በጊዜው የተዘመሩ መዝሙሮች አይረሱኝም፡፡ በጊዜው የወላይታ ቤተ ክርስቲያን በመራራ ስደት ውስጥ ሳለች የመሠረተ ክርስቶስ ቤክ መዘምራን ወደ ቦታው ተንቀሳቅሰው በ”ኦቶና” ዓመታዊ ኮንፍራንስ ላይ ሲዘምሩና ሕዝቡ አብሮአቸው በእምባ ሲራጭ እኔና እኩያዎቼ ከመድረኩ ፊት ለፊት በመሬት በተጎዘጎዘው ሣር ላይ እንድንቀመጥ አስተናጋጀች ስላስገደዱን እዚያው ሆኜ ነው የሰማሁት፡፡ ይህ መዝሙር ዛሬም ለእግዚአብሔር ሕዝብ ትኩስ መልእክት ያለው ነው፡፡ ከዚያ ጊዜ ጀምሮ በመዝሙር የማገልገል ጥማት ውስጤ ገብቶ ስለነበር እስከአሁን አራት በሚያህሉ ኳየሮች አገልግያለሁ፡፡ ታዲያ መዘምራኖቹ በቁመቴ ብቻ ሳይሆን ድምጼም ዝማሬውን ስለሚያተራምስባቸው ይቸገሩብኝ ነበር፡፡ እኔም ከመዘምራን ጋር ባገለገልኩባቸው ጊዜያቶች ቅር ያለኝ ነገር ቢኖር አብሬአቸው ፎቶ መነሳቴ ነው፡፡ ከእነርሱ ጋር የተነሳሁአቸው ፎቶዎቼ አብዛኛዎቹ ወይ ከአንጌቴ፣ ወይ ከፍንጫዬ በላይ የላቸውም፡፡ ጌታ ኃጢአቴን ሁሉ ይቅር እንዳለኝ መጽኸፉ ስለነገረኝ እኔም ይቅር ብዬአቸው ነው እንጂ ያኔ ፎቶ ባነሱን ሰዎች ላይ ቂም ቢጤ ሁሉ ቋጥሬባቸው ነበር ፡፡አጫጭሮቹ ከእግራቸውም ከጭንቅላቸውም በሌንሳቸው እንዲገቡ ብለው እኔን ከአጭሮቹ ትክክል ቆርጠውኛልና፡፡
በቤተ ክርስያቲናችን የበረውን ትልቁን ፑልፒት አጫጭሮቹ ሰባኪዎች አይወዱትም ነበር፡፡ ያንን ፑልፒት ያስቀየረን አንዱ የእነርሱ ብሶት ነው፡፡ ፑልፒቱ ስለሚከልላቸው ከሥሩ ለእነርሱ ተብሎ የተዘጋጀ ኩርሲ አይነት ነገር ስላለ ሲሰብኩ እዚያ ላይ ይወጣሉ፡፡ ከዚያ እንደምንም ብለው ከደረታቸው በላይ ይታያሉ፡፡ ሊሰብኩ እዚያ ላይ ወጥተው "እታያለሁ?"ብለው ጉባኤውን የጠየቁ ሁሉ ነበሩ ብል ታምኑኛላችሁ? አሁን ብዙ ሲዘመር አልሰማውም እንጂ አንድ "መሸሸጊያ ዋሻ 2x መከታ ጋሻችን" የሚል ተወዳጅ መዝሙር ነበርና ከምንወዳቸው ሽማግሌዎቻችን አንዱ ይህን ምዝሙር እያዘመረ ጉባኤውን ሲመራ በተለይ መሸሸጊያ ዋሻ የሚለው ቃልጋ ሲደርሱ በዚያ ፑልፒት ሥር እየተደበቀና ከዚያም ብቅ እያለ ሲመራ ጥሩ ምሳሌ ይሆንለት ነበር:: ታዲያ ከመድረኩ ጫፍ ወደ ሌላው ጫፍ የሚሯሯጥ ሰባኪ ያ ፑልፒት አይመቸውም፡፡ እኔ ስሰብክ ግን ያንን ኩርሲ ስለማልፈልግ ወደ ጎን አሽቀነጥረውና መሬቱ ላይ ቆሜ እንኳ ጉባኤው ከደረቴ ሳይሆን ከወገቤ በላይ ያየኝ ነበር፡፡ አስቡ እንግዲህ! የቤተክርሰትያናችን አባቶች ቅጽል ስም ሁላ አውጥተውልኛል፡፡ በጣም የምናከብራቸው የነበረ ጋሼ ጥላሁን “ሰማይ ዛፉ” ፣ “ብቅል አውራጅ”፣ ይሉኝ ነበር፡፡ ጋሼ ወልደአምላክማ በስሜ ከሚጠሩኝ “ቀውሌ” ሲሉኝ ይቀላቸዋል፡፡ ጋሼ ማሞ ደግም ልክ እንደ ጋሽ ጥላሁን “ሰማይ ዛፉ” እንደሚሉኝ ልንገራችሁ፡፡ የማታውቁኝ ወገኖቼ ምን ያህል ረጅም እንደሆንኩ በዚህ ይግባችሁ ብዬ ነው፡፡
በረዶ ካልዘነበ በቀር አንዳድ ጊዜ ከባለቤቴ ጋር በእግር እንጓዛለን( ባለንበት አገር ዎክ ይባላል)፡፡ ታዲያ የምንጓዘው እያወራን ነው፡፡ ምን አለፋችሁ ባለቤቴ ቀስ ብላ የመናገር ባሕሪይ ስላላት እሷ የምትለው እኔጋ አይደርስም፡፡ እኔ ከላይ ሆኜ ስለምናገር እያንዳንዱን ነገር ትሰማለች፡፡ ስንቸገር ለምን እኔና አንቺ በስልክ አናወራም እላታለሁ፡፡ አብረን እየተጓዝን ወደ አንድ የገበያ አዳራሽ ስንደርስ እርሷ የሆነ ዕቃ እንግዛ ብላኝ ወደ ውስጥ ስንገባ ህንዳዊው የሱቁ ባለቤት አላየንም ነበር ግን ኮሜዲኖው አጠገብ ቆመን ስናናግረው በሆነ ወንበር ላይ የቆምኩ መስሎት አንገቱን አሰግጎ ወደ ጫማዬ አየኝና "በምን ላይ ቆመህ ነው ?" ያለኝ ቀን እንዴት እንደሳቅኩ ልነግራችሁ አልችልም፡፡ የሰውዬው አባባል በአዲስ አበባ ቦሌ ቃለ ሕይወት ቤክ አገልግዬ ስመለስ አንዲት የሀብታም ልጅ የምትመስል ከእናቷ ጋር ስትሄድ ነበርና በአጠገባቸው ሳልፍ አይታኝ እንደመሞላቀቅ አድርጎአት "ወይኔ ጂሴስዬ....ሰውዬው ምን ያክላ.....ል" ማለቷን አስታወሰኝ፡፡ አንዳንድ ጊዜ ደግሞ ተቃራኒውም ይገጥመኝና አቤት የጌታ ሥራ እንዴት ግሩም ነው እላላሁ፡፡ ለአገልግሎት ሌላ ቦታ ካልሄድኩ በግራድ ራፒዲስ ከተማ ወደሚገኘው ካልቬሪ ቤተክርስቲያን ሄደን የጌታን ቃል እንሰማለን፡፡ ቤተ ክርስቲያኑ ትልቅ ከመሆኑ የተነሳ ስድስት የሙጪያና የመግቢያ በሮች አሉት፡፡ አንድ ቀን ግን ወደ ቤተ ክርስቲያኑ ስንገባ የመጀመሪያውን ፈረቃ ተካፍለው የሚወጣውና ሁለተኛውን ለመካፈል የምንገባው ሰዎች ዌስት ጌት (የምዕራቡ መግቢያ በር) በኩል ባለው በተላለፊያ ላይ ተገናኘን፡፡ ታዲያ በፈረንጆች አካባቢ ረጅም ሰውና ሽማግሌዎችን ማየት እንደ ልብ ስለሆነ እንደ እኛ አይገርማቸውም፡፡ ግን ያን ቀን የሚወጣው ሕዝብ ሲወጣ እኛ ደግሞ ስንገባ ከፊት ለፊቴ አንዲት ዕድሜዋ በግምት ከ25-30 ውስጥ የሚሆናት ወጣት ሴት በሕዝቡ መካከል ወደ እኛ አቅጣጫ ትመጣ ነበር፡፡ ከሰው ሁሉ ከፍ ብለን የምንታየው እኔና እርሷ ብቻ ነበርን፡፡ ግን ሆን ብላ ወደ እኔ መጣችና በአጠገበ አለፈች፡፡ ታዲያ ምን አለፋችሁ ወደ አናቴ ቁልቁል እያየችኝ ስታልፍ አንዱ ሽማግሌ ፈረንጅ ተክ ብሎ ሳቀ፡፡ አንተንም የሚበልጥ መኖሩን እወቅ የሚል ይመስላል፡፡
እኔም ይህንን ሁሉ የዘከዘኩት በቁመቴ ላዝናናችሁ ወይም ላስቀናችሁ አይደለም፡፡ ቁመቴ 6.5 ሃይት መሆኑ በህግ ተረጋግጦ በመንጃ ፈቃዴና በሌሎች ሕጋዊ ሰነዶች ላይ ሰፍሮ እያለ ሰሞኑን አጭር መሆኔ ሲነገረኝ ክው ብዬ ስለ ደነገጥኩኝ የሚያጽናና መልእክት ወይም ምክር ካላችሁ እንድትለግሱልኝ በማለት ነው እንጂ፡፡ አጭር መሆኔ የተነገረኝ ከሀኪም ወይም ከሌላ ባለሙያ አይደለም፡፡ ካለሁበት አገርም አይደለም፡፡ ከነቢያት አገር ከኢትዮጵያ ነው፡፡ አንድ ሰው በቫይበር ግሩፕ ፈጠረና እኔንም እዚያው ውስጥ አካቶኝ መልእክት ስለላከብኝ ማን አንደሆነና የእኔንም ስልክ ከየት እንዳገኘ እንዲነግረኝ መልእክት ላኩበት፡፡ ከዚያ በዚያው በቫይበር ደውሎልኝ ማእረጉን በማስቀደም ስሙን ነገረኝ፡፡ ስሙን ለጊዜው ላቆይና ወንድማችን በማዕረጉ ነቢይ ነው፡፡ ፕሮፌት …….. እባላለሁ ከኢትዮጵያ አለኝ፡፡ ማዕረግ ያልኩበት ምክንያት አሁን አሁን ወንጌላዊነት ፣ መጋቢነት ፣ ወይም ሓዋሪያነትና ነቢይነት ለአገልግሎት እንደተሰጠን የጸጋ ስጦታ ሳይሆን እንደ ማዕረግ ስለሚታይና ሰዎችም በዚያ ማዕረግ ካልተጠሩ ስለሚከፋቸው ነው፡፡ እንግዲህ አሳብ እየተለዋወጥን እያለ ጌታ ስላገናኘን አመሰገነና በሰዓቱ እግዚአብሔር ስለ እኔ የሚያሳየውን ነገር ስላለው ልነግረኝ ፈቃደናነቴን ጠየቀኝ፡፡ ፕሮፌት ነኝ ስላለ እና እኔም የነቢያትን አገልግሎት ስለማከብር ንገረኝ አልኩት፡፡ ብዙ ነገር ነገሮኝ ያንን ሁሉ በምልክት ሊያጸናልኝ ፈልጎ ማረጋገጫ በምልከት ይደረድርልኝ ጀመር፡፡ “አንደኛ፣ በ1996 ዓ. መጨረሻና በ1997 መግቢያ ላይ በሕይወትህ አንድ ነገር ሆኗል፡፡ ሁለተኛ፣ አንተ ጥቁር ሰማያዊ መኪና አለችህ፡፡ ሦስተኛ፣ በግራ እግርህ ከጉልበትህ በታኝ ቆስሎ የዳነ ምልክት አለብህ፡፡ አራተኛ አንተ ረጅም ሰው አይደለህም በቁመትህ ከአጭር ሰው ትንሽ ከፍ ትላለህ፡፡ ይህንን የምነግርህ እምነት እንዲሆንህ ነው አሜን በል፣ ” አለኝ፡፡ እኔም አሜን አልኩ፡፡ ለምን አሜን አልክ አትበሉኝ
ስለ ቁመቴ ማጠር ስሰማ በጣም ደነገጥኩ፡፡ መልሼ “እኔ እኮ በጣም ረጅም ሰው ነኝ፡፡ እንዲያውም ድሮ ከጋምቤላ አካባቢ መጥተው ለአየር ኃይል መረብና ቅርጫት ኳስ የሚጫወቱ ረጃጅም ሰዎች ነበሩ:፡ ወይም ከቦረና ነገሌ መጥተው በመረብ ኳስ ሜዳ ያገኘናቸው ሰዎች ካልሆኑ እሰከአሁን በቁመት የሚያክለኝ ሰው አልገጠመኝም፣ አንተ ደግሞ ከአጭር ሰው ትንሽ ከፍ እንደምል ትነግረኛለህ፡፡ ነገሩ እንዴት ነው?” ስለው፣ “እንግዲህ እኔ የማውቀው ነገር የለም ጌታ ያሳየኝ ይህ ነው” አለኘኝ፡፡ የቁጣ መልስ ስለመሰለኝ ጨዋታችንን እዚውጋ አበቃን፡፡ ደግሜም ያንን ሰው አላገኘሁትም፡፡
ታዲያ ምን አሳሰበህ የሚል ቢኖር ከላይ በተጠቀሱት ዓመታት በሕይወቴ የሆኑ ብዙ ነገሮች ነበሩና ትክክል ነው ብዬ ተቀበልኩ፡፡ በእግሬም ላይ ገጣባ መኖሩ እውነት ነው፡፡ በልጅነቴ የአጋም ፍሬ ለመብላት ብዬ ዛፍ ላይ ወጥቼ ከአንዱ ዛፍ ወደ ሌላ እየተሸገጋርኩ እያለ የቆምኩበት እንጨት በመሰበሩ ከከፍታ ላይ ተወርውሬ ስወድቅ ከታች የቆመው ሹልና ደረቅ እንጨት ተቀብሎኝ እግሬ ውስጥ በመሸንቀሩ ምክንያት በጣም ቆስዬ ነበርና ያ ስድን ገጣባው እዚያ አለ፡፡ መኪናዬም ጥቁር ሰማያዊ ነች፡፡ እነዚህ ምልክቶች ልክ መሆናቸውን ሳይ ነው የደነገጥኩት፡፡ ይህን ሰው ከማግኜቴ ከሁለት ሳምንታት በፊት ወደ መታጠቢያ ቤት ስገባ የበሩ የላይኘው ጉበን አናቴን ደርግሞት ስለነበር ያ አሳጥሮኝ ይሆን እንዴ ብዬም አሰብኩ፡፡ ደግሞ የተናገረው ጌታ ነው ሲለኝ እንዴት አልጨነቅም? ቁመቴን የሰጠኝ ጌታ እንደሆነ ሙሉ በሙሉ አምናለሁ፡፡ በቤተ ክርስቲያኔ ከእኔ ጋር አብሮ እንዲሠራ የተመደበ መጋቢ ነበርና ሰዎችን ለመገብኘት አብረን ስንሄድ እርሱ አጭር ብቻ ሳይሆን ሆዱም ላይ ቦርጭ ነገር ጣል ስላደረገችበት እንዲያው ድቡልቡል ነው፡፡ ታዲያ አንድ ቀን አብረን ስንሄድ የእርሱ አባት በርቀት ሆነው አይተውን ኖሯልና ለምን ከዚያ ከረጅሙ ጓደኛው ጋር ይሄዳል ቢቀርበትስ ምን አለበት ብለው እቤታቸው ያወሩትን ወንድሙ ሲነግረን አይዞህ ብዬ አጽናንቼዋለሁ፡፡ አንተንም እኔንም እግዚአብሔር ግሩምና ድንቅ አድርጎ ፈጥሮናለልና ከእኔ ጋር ለመሄድ አትፍራ እለው ነበር፡፡ እጥረቱን ባደንቅለትም በሆድ ላይ ስለሚከመረው ቦርጭ ጥንቃቄ እንዲያደርግ ሁሉ እነግረዋለሁ፡፡ አጭር ሰው ቦርጭ ከበዛበት ደረቱ ላይ ይወጣበትና ወደኋላ ይለጥጠዋል፡፡እንዲያውም በእርሱ ቁመት ልክ ሆነው በጣም ቦርጫም የነበሩ አቢዬ ደመቀ የሚባሉ የእኛ አካባቢ ሰው ከቦርጫቸው መብዛት የተነሳ ሆዳቸውን ወደላይ የሚያዩ ይመስላሉ፡፡ ታዲያ አብዬ ደመቀ ጫማቸውን ማየት ስለማይችሉ ጫማቸውን ሲያስጠርጉ ሊስትሮዎቹን በጣም ሲያስጠነቅቁአቸው "ጫማዬን በደንብ ጥረጉልኝ ፣ እኔ ባላይ እግዜር ያያችኋል" ይሉ እንደነበር ሁሉ ነግሬው እንደ እርሳቸው እንዳይሆን አስጠነቅቀዋለሁ-- ከዚያ ውጭ አጫጭሮች በጣም ያስፈልጉናል እነርሱ ባይኖሩ ማን ረጅም ይለናል? እኛስ ባንኖር እነርሱንስ አጭር ማለት እንዴት ይቻላል? አንዳችን ለሌላችን እናስፈልጋለን ማለት ነው፡፡ እኔን እግዚአብሔር ግሩምና ድንቅ አድርጎ በመፍጠሩ እያመሰገንኩ ስኖር ሳለ ቁመቴ ማጠሩን ከነቢይ መስማቴ እንዴት አያስደንግጠኝ? ደግሞ ረጅም መሆኔን ነግሬው ማብራሪያ ሲጠይቀው “እኔ የማውቀው ነገር የለም እግዚአብሔር ያሳየኝን ነገርኩህ” ማለቱ በበለጠ እንዳስብ አደረገኝ፡፡ ከጌታ የተቀበልኩትን ቁመት ምንም ሳልጠቀምበት ስለቀረሁ ተወሰደብኝ ማለት ነው ብዬም አሰብኩ፡፡ ያንን ጋሽ ጥላሁንና ጋሼ ማሞ ያሉኝን ብቅል እንኳ ሳላወርድ ቀርቼ ይሆናል እያልኩ ሌሊቱን ሙሉ አሰብኩ፡፡ በአንድ በኩል ከብቅል ጋር ምንም ጉዳይ እንዳይይኖረኝ ዳግም ተወልጃለሁና ብቅል ባይወርድም ተጠያቂ አልሆንም ብዬ ልጽናና ሞከርኩ፡፡ነቢይ ኢዩ ጩፋ ቁመታቸው ያጠረ ሰዎችን አስረዝማለሁ በማለት ሲዳክር ያየሁት ስለነበረ እግዚአብሔር አጫጭሮችን እያስረዘመ እኔን ረጅሙን የሚያሳጥረኝ ምን አግኝተብኝ ይሁን ብዬ አሰብኩ፡፡ ቃሉ "ለሰው ሁሉ ከሚሆን በቀር ምንም ፈተና አልደረሰባችሁም"( 1 ቆሮ 10፡13) ይለናል፡፡ ግን እኔ እኮ ለሰው ሁሉ ከሚሆን በቀር የተለየ ፈተና ገጥሞኛል፡፡ ምክንያቱም እግዚአብሔር አስከ አሁን ድረስ ከእኔ በቀር ቁመቱን ያሳጠረለት ሰው አልሰማሁም አላየሁም በማለት ከጌታ ጋር በቃሉ ተሟገትኩ፡፡
ጠዋት እንደምንም ነጋልኝና ቁመቴን ለማየት ወደ ማስታወትጋ ሄድኩ፡፡ እቤታችን ያለው ማስታወት ከደረት በላይ እንጂ ሙሉ ቁመት ስለማያሳይ አልተሳካልኝም፡፡ ነገር ግን ባለቤቴ ሶፋችን ላይ ቁጭ ብላ መጽሐፍ ቅዱስ እያነበበች ሳለ ጠጋ ብዬ በስሟ ጠራሁአትና “ቁመቴ ማጠሩ አያሳዝንሽም?” አልኳት፡፡ ያንን ቃል ስደግምላት አይኗን ከመጽሐፉ ነቀለችና ወደ እኔ አየት ካደረገች በኋላ ወደ ንባቧ ተመለሰች፡፡ አሁንም እንደገና ጠየቅኳት ፡፡ ከዚያ እንዲህ አለቺኝ፡፡ “ምን ሆነህ ነው ደግሞ ዛሬ? ብላ ወደ ንበቧ መለስ አለች ወዲያው ደግሞ ወደ እኔ አየት አደረገቺኝና “ትላንት የት ሄደህ ነበር? ሰሞኑን የሆነ ቦታ ሄደሃል ማለት ነው? አለችኝ፡፡ እግዚአብሔር ቁመቴ ማጠሩን በነቢይ በኩል ተናረኝ ስላት የሳቀቺው ሳቅ ራሱ አስደነገጠኝ፡፡ እኔ የቃሉ አስተማሪ ሆኜ በዚህ መታሌለን እንደ መንፈሳዊ ጅልነት አድርጋ ወሰደቺውና “እግዚአብሔር ሥራ ጨረሰና የአንተን ቁመት እየለካ መዝናናት ጀመረ ማለት ነው?” አለች፡፡ እንግዲህ ነቢያት እውነተኞች ናቸው.፣ ከእግዚአብሔር ናቸው የሚባለው በምልክት የሚነገረው ነገር ካለንበት አካላዊና ማህበራዊ ነገሮቻችን ጋር መግጠሙን ስናይ አይደል? ያ ነቢይ የነገረኝ ምልክት አብዛኛው ትክክል ነው፡፡ ግን ግልጥ የሆነውን ከኢትዮጵያ እስከ አሜሪካ ድረስ ያለው ሕዝብ በአደባባይ የሚያየውን ረጅሙን ቁመቴን አጭር ያለው እግዚአብሔር ነው ሲባል ማመኔ ባለቤቴን ምን ነካህ ቢያስብላት ምን ጥፋት አለባት?እኔም ሳስበው እግዚአብሔር ስለ እኔ የመኪና ቀለምና የቁመቴ ጉዳይ ዋና አጀንዳው አለመሆኑን የነቃሁት ብዙ ከለፋሁ በኋላ ነው፡፡ ባለቤቴ ያንን ጥያቄ ባትጠቀኝና ከእኔ ጋር ብትደነግጥ ምን ልንሆን እንደምንችል ገምቱ፡፡
ከዚህ የምንረዳው ሐሰተኞች ነቢያቶች የሚባሉት ውሸት ብቻ የሚናገሩ እንዳይደሉ ነው፡፡ ሐሰተኞች እውነት በሚመስሉ በርካታ ነገሮች ውስጥ ሐሰተኛ መርዛቸውን ሸፍነው ስለሚያቀርቡ ሐሰትነታቸውን መለየት ቀላል ሥራ አይደለም፡፡ በሰሙት ነገር ወዲያው የሚወሰዱ የእኔ ቢጤዎቹ በቀላሉ ይመረዛሉ፡፡ የሚገርመው ነገር ያ ነቢይ በቫይበር ግሩፕ ካካተታቸው ሰዎች ውስጥ የማውቀው አንድ ወዳጄ ስለነበረ መደወል አስፈከገኝ፡፡ ስለ ሁኔታው ሳጫውተውና ነቢይ ነኝ ስለተባለውም ሰው ያውቅ እንደሆነ ብዬ ስጠይቀው የነገረኝ ነገር በበለጠ አስደመመኝ፡፡ በአገር ቤት እያለ እንደሚያውቀውና ጥሩ የሆነ የአገልግሎት ሕይወት እንደነበረውም አጫወተኝ፡፡ ነገር ግን አሁን የሰዎችን ፌስ ቡክ እየወሰደ ከዚያ መረጃዎችን ከሰበሰበ በኋላ ጌታ ተናገረኝ እያለ ወደ ሰዎች እንደሚደውል አስረዳኝ፡፡ ይህ ማለት የእኔ መኪና ቀለም ጥቁር ሰማያዊ መሆኑ የተነገረው ከጌታ ሳይሆን ከፌስ ቡክ ነው ማለት ነው፡፡የቁመቴም ጉዳይ ቢሆን ከውድ ባለቤቴ ጋር ሆኜ የተነሳሁትና ለቫይበር ፕሮፋይል ያደረግኩት ፎቶ በእርግጥም የአጭር ሰው ይመስላል ፡፡ ከእርሷ ጋር እኩል ለመሆን በደረጃ ላይ ሰበር ብዬ የተነሳሁት ስለሆነ ነቢዩ ከዚያ ሊያይ እንደሚችል ገባኝ፡፡ አንዳንዶች መዘምራን ቅኔና ወይም ዜማ ከዓለማዊ ዘፈን በመቅዳታቸው እነርሱም በዘመሩበት አማኞች በየሰፈሩ በመሰደባቸው የመጣብን ቁስል እያመረቀዘና እየጠዘጠዘን ባለበት ጊዜ የትንቢትን መልእክት ከፌስ ቡክ የሚቀዱ ደፋር ነቢያት የሚያታልሉን አጋጣሚ መፈጠሩ አስተክዞኛል፡፡ በዚህ ዓይነት ሁኔታ የተታለሉ ስንቶች ይሆኑ? ምን ይበጃል ትላላችሁ?
LikeShow more reactions
Comment

Thursday, February 23, 2017

     በአገልግሎታችን ቅዱሳንን እንዴት መጥቀም እንደሚገባን ( 2017-35)
                                                                                                   

                                                                                           ከመጋቢ ሳሙኤል ሾንጋ

እንደ አውሮጳውያን አቆጣጠር 1993 ዓ.ም. በደቡብ ሱዳን ከፍተኛ ድርቅ በመከሰቱ ምክንያት የበርካታ እንስሳትና የሰው ሕይወት ጠፍቶ ነበር፡፡ በጊዜው የተከሰተው ተፈጥሮአዊ አደጋ በጣም አስከፊ በመሆኑ የተባበሩት መንግሥታት ድርጅት/United Nations  በጉዳት ላይ ለነበረው ሕዝብ ሰብአዊ ርዳታ እንዲሰጡ የተለያዩ ዘርፍ ባለሙያ ሰዎችን ወደ ደቡብ ሱዳን መላኩ ይታወሳል፡፡ በጊዜው የህክምና ባለሙያዎች፣ የሰብአዊ ርዳታ ሰጪ አካላት ወዘተ  መድኃኒት፣ ምግብና ሌሎች አሰፈላጊ  ቁሳቁሶችን ይዘው ወደ ቦታው ተንቀሳቅሰዋል፡፡ በወቅቱ ከተንቀሳቀሱት ውስጥ ዓለም አቀፍ ጋዘጤኞችም የነበሩበት ሲሆን ታዋቂ ፎቶጆርናሊስት ደቡብ አፍሪካዊው ኬቪን ካርቴር ይገኝበታል፡፡ ኬቪን ከልዑካን ቡድኑ ጋር ወደ ደቡብ ሱዳን ከደረሰ በኋላ በካሜራው ያነሳቸው ፎቶግራፎች በጣም ተደናቂነትን ያኙና በሥፍራው ስለነበረው የድርቅ ሁኔታ በጣም በኃይለኛው ሁኔታ የሚገልጹ ነበሩ፡፡ ለምሳሌ ልጆች ውሃ ከማጣታቸው የተነሳ ላሞች ሽንት ሲሸኑ ከስር ቀርበው ሲጠጡ፣ ወይም ጭንቅላታቸውን አስጠግተው ሲታጠቡ ኬቪን በካሜራው አንስቷል፡፡ ከሁሉም ፎቶዎቹ ይልቅ ግን በወቅቱ ሁሉንም ያስደነቀችና የኬቪንንም ዝና እጅግ ያወጣችው ፎቶ ሌላ ነበረች፡፡ አንዲት በረሀብ በጣም ከመጎዳቷ የተነሳ ሰውነቷን መሸከም ያቃታት፣ በአካላቷ  ላይ ምንም ሥጋ የሌላት ፣ ቆዳዋና አጥንቷ የተጣበቀ የሚመስል ሕጻን ልጅ በአንድ በረሀማ በሚመስል ቦታ  ፣ በሰውነቷ ላይ ምንም ልብስ ሳይኖር ራቁቷን ሆና ጭንቅላቷን በሁለት እግሮቿ መካከል አድርጋ በግምባሯ ተደፍታ ፣  በአጠገቧ ምንም ሰው ሳይኖር ነገር ግን ከኋላ አንድ የፈረጠመ ጆፌ አሞራ ተንሰፍስፎ ሲጠብቃት ሳለ ኬቪን በካሜራው አነሳና ለዓለም ሕዝብ አሳየ፡፡ ያ ፎቶግራፍ በደቡብ ሱዳን የነበረው ድርቅ አስከፍነቱ ምን ያህል ጥልቅ እንደሆነ የሚያስረዳ በመሆኑ በጊዜው የዓመቱ ምርጥ ፎቶ ተብሎ ተመረጠ፡፡ በዩናይትድ ስቴት ኦፍ አሜሪካ ያለው በሥነ ጽሑፍ፣ በጋዜጠኝነት፣ በሙዚቃ ድርሰት የላቀ አስተዋጽኦ ላበረቱት ሽልማት የሚሰጠው Pultizer price የተሰኘው ድርጅት የሚሰጠውን ሽልማት ያሸነፈ አስደናቂ ፎቶ ሆኖ ተመረጠ፡፡ ከዚያ በኋላ የኬቪን ዝና እጅግ ወጣ፣ በዓለም ዙሪያ ሁሉ ገናናና እና ታዋቂ ሆነ፡፡ የኬቪን ፎቶ የፓልትዘርን ሽልማት ስላሸነፈ የሽልማት ስነሥርዓት በተባበሩት መንግሥታት ዋና ጽሕፈት ቤት ተዘጋጀለት፡፡ ከተለያዩ የሙያ ባለሙያዎች፣ የኪነ ጥበብ ሰዎች፣ ከጋዘጠኞችና የፊልም ባለሙያዎች የእንኳን ደስ ያለህ መልእክት ከየአቅጣጫው ጎረፈለት፡፡ የሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ወቅት በታዳሚዎች ፊት  በሙያውም ስኬታማ ሊሆን የቻለው እንዴት እንደሆነ ከጋዘጠኞች ለሚቀርብለት ጥያቄ መልስ እየሰጠና በደቡብ ሱዳን በረሀ ላይ ያቺን ሕጻን እንዴት በካሜራው እንዳገኛት ስለብልሃቱና ስለጥበቡ  እያብራራ ከሁሉም ሰው አድናቆትን  እያኘ ሳለ ከጉባኤ በስተ መጨረሻ በኩል አንድ ሰው አንድ ወሳኝ ጥያቄ አቀረበለት፡፡ ጥያቄውም እንዲህ የሚል ነበረ፡፡ “የልጅቷ መጨረሻ ምን ሆነ?”  በዚህን ጊዜ ኬቪን ደነገጠ፡፡ አንደበቱ ተሳሰረ፡፡ በዓይነ  ሂሊናው ወደ ደቡብ ሱዳን በረሀ ጭልጥ ብሎ ሄደ፡፡ ሰውነቱ ይንቀጠቀጥ ጀመር፡፡ ልጅቷ ምን ሆነች ለሚለው ጥያቄ በሽልማት ሥነ ሥርዓቱ ላይ የተገኘውን ሕዝብ አስተሳሰብ በአንዴ ቀየረው፡፡ ጉባኤተኛው ሕዝብ ኬቪን ለዚህ ጥያቄ ምን መልስ ይሰጥ ይሆን ብሎ በጉጉት እየጠበቁ ሳለ  እርሱ ምንም ሳይመለስ ያን ጥያቄ ያቀረበው ሰው ሌላ ጥያቄ በከፍተኛ  ጩኼት “ ልጅቷን አዳንካት ወይ “ በሚል አስከተለበት፡፡ ኬቪን ልቡ ይመታ ጀመር፡፡ ራሱን በዚያ ሥፍራ ማቆየት ስላልቻለ ከወንበሩ ተነስቶ ወደ ውጭ ወጣ፡፡ በዚያው ወደ አዳራሹ ሳይመለስ ወደ ትውልድ አገሩ ወደ ደቡብ አፍሪካ አቀና፡፡ ቢሆንም ከህልናው ክስ መሸሽ ስላልቻለና ስለተሰቃየ በተወለደ በ33 ዓመቱ አንድ ወረቀት ጽፎ አጠገቡ አስቀመጠና ራሱን ሰቅሎ ሞተ፡፡
ኬቪን ወደ ደቡብ ሱዳን የተላከበት ዋንኛ ምክንያት ለራሱ ዝና እንዲሠራ አልነበረም፣ የሌሎችን ሕይወት ለማዳን እንጂ፡፡ እንደዚያች ላሉ ሕጻናትና ለሌሎች በድርቁ ለተጎዱት ሰዎች የነፍስ አድን ርዳታ እንዲያደርስላቸው ነበር፡፡ ነገር ግን የዚያች ልጅ ሕይወት እየመጣባት ካለው አሞራ ማዳን ሲችል ተልዕኮውን ወደ ጎን በመተው የራሱን ዝና ለማውጣት የሚችለውን ሥራ ብቻ ሥርቶ ልጅቷን በዚያ በረሀ ለአሞራ ተዋት፡፡ ሌሎችን ለመጥቀም የተሰጠውን ተልዕኮ ዘንግቶ ራሱን መጥቀም ፣ በሰዎች ጉዳት እርሱ የመክበርን መንገድ ተከተለ፡፡ በመጨረሻም በጣም ወሳኝ ወቅት ላይ ልጅቷን አዳንካት ወይ የሚል የቀረበለት ጥያቄ ያንን ክብርና ዝናውን ሁሉ አበላሸበት፡፡
ይህ በእግዚአብሔር ቤት ቅዱሳንን ለመጥቀም ከጌታ የአገልግሎትን አደራ ለተቀበልን ሁሉ ማንቂያ ደወል ሊሆን የሚችል ምሳሌያዊ አሳብ ነው፡፡ እኛ የተጠራነውና አገልግሎትን የተቀበልነው ሌሎችን ለመጥቀም ነው፡፡ አገልግሎት የሚለው አሳብ ራሱ ሌላውን ማገዝ፣ መጥቀም፣ መርዳት ወይም ለሌሎች ጥቅም መኖር ማለት ነው፡፡ ይሁን አንጂ በአሁኑ ጊዜ አገልግሎትና አገልጋይ ማለት የተሳሳተ ሥፍራ ላይ እየዋለ ይገኛል፡፡ ከቅርበ ጊዜ ወዲህ በቤተ ክርስቲያን አገልጋይ መሆን ሌሎችን የመጥቀም ጉዳይ መሆኑ ቀርቶ  በሰዎች መጠቀም፣ የተገኘውን ዕድል ሁሉ ለራስ መውሰድ( taking an Advantage to own self ) መሆን እየመሰለ መጣ፡፡ ሰዎችን አዋርደን እኛ ክብር ማግኘት፣ ሰዎችን ዝቅ አድርገናቸው ወይም ጎድተናቸው እኛ ዝናን ማግኘት፣ ድፍረት በባይሆነኝም የሰዎችን ኪስ አራቁተን እኛ ማለትም አገልጋዮች የሆንንው እኛ ብቻ  መበልጸግን ልማድ እያደረግን እንገኛለን፡፡ እግዚአብሔር ለቤተ ክርስቲያንና ለአገልጋዮች የሰጠን ተልእኮ ወደ ጎን የተተወ ይመስለኛል፡፡ ልክ የፎቶግራፍ ጋዜጠኛው ኬቪን የተባበሩት መንግሥታት የሰጡት ተልእኮ የተጎዳውን ሕዝብ እንዲያድን ሆኖ ሳለ እርሱ ግን ያንን ሰውን የማዳን ሥራ ወደ ጎን ትቶ የተራቡ ሕጻናትን ለአሞራ ሰጥቶ ለራሱ ክብር ዝና፣ ገንዘብ ሽልማት፣ ታዋቂነትን የሚያተርፍበትን መንገድ እንደተከተለ ሁሉ ዛሬ እኛም አገልግሎታችንን ለሌሎች ጥቅም መስጠት ትተን ለራሳችን ክብርና ዝና የምንኖር እንዳይሆን መጠንቀቅ እንዳለብን የሚያሳስበንን መልእክት ሐዋሪያው ጳውሎስ ከኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ከተናገረው አሳብ እንመለከታለን፡፡
ሐዋሪያው ጳውሎስ በመልእክቱ መግቢያ ላይ እንዲህ ይላል፡፡
ከሚሊጢንም ወደ ኤፌሶን ልኮ የቤተክርስቲያንን ሽማግሌዎች አስጠራቸው፤ ወደ እርሱም በመጡ ጊዜ እንዲህ አላቸው፦ ወደ እስያ ከገባሁበት ከመጀመሪያ ቀን ጀምሮ፥ በትሕትና ሁሉና በእንባ ከአይሁድም ሴራ በደረሰብኝ ፈተና ለጌታ እየተገዛሁ ዘመኑን ሁሉ ከእናንተ ጋር እንዴት እንደ ኖርሁ እናንተው ታውቃላችሁ፤ ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ንስሐንና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች እየመሰከርሁ በጉባኤም በየቤታችሁም አወራሁላችሁና አስተማርኋችሁ እንጂ፥ ከሚጠቅማችሁ ነገር አንዳች ስንኳ አላስቀረሁባችሁም።
ጳውሎስ ሌሎችን የመጥቀሙን አገልግሎት በኤፌሶን ላሉት አማኞች በትክክል አስመስከሯል፡፡ እንዲያውም እርሱ በዚያ ሲያገለግል ሁለት ዓይነት ሰዎች እንደነበሩ ከክፍሉ አጠቃላይ አሳብ እንረዳለን፡፡ አንደኛዎቹ የሐሰት ትምህርት አስተማሪዎች ናቸው፡፡ ጳውሎስ ስለ እነርሱ ሲገልጽ ከተኩላ ጋር ይመስላቸዋል፡፡ ከአውሬዎች ጋር ይመስላቸዋል፡፡ ነጣቂዎች ናቸው ይላቸዋል፡፡ ለመንጋው የማይራሩ ጨካኞች ይላቸዋል፡፡ ደቀመዛሙርትን ወደ ኋላ  የሚስቡ፣ ጠማማ ነገርን የሚናገሩ እንደሆኑ ያሳስባል( ቁ 29-30)፡፡ አገልጋዮች ናቸው፣ የወንጌል አገልጋዮች፣ ሰባኪዎች ናቸው ግን በመንጋው ላይ የሚጨክኑ ፣ የአውሬነትና የተኩላነት ልብ ያላቸው፣ የሚነጥቁና የሚያጣምሙ መሆናቸው በጣም የሚያስገርም ነው፡፡ አንድ ሰው ወደ አገልግሎት ሲገባ የእግዚአብሔርን ሕዝብ ልጥቀም ብሎ ካልሆነ የራሱን የሚመግብ ጨካኝና ነጣቂ ነው የሚሆነው፡፡ ያ ደግሞ መጥፎ መርገም ነው፡፡ ልክ ኬቪን ልጅቷ አዳንካት ወይ የሚል ጥያቄ ሲቀርብለት ግራ እንደተጋባና ራሱን ከሥፍራው እንዳገለለ ሁሉ አገልጋዮች አንድ ቀን መጠየቃችን አይቀርም፡፡
ሁለተኛው ጳውሎስ ራሱ ሲሆን የኖረው ለአማኞች ጥቅም ሲል እንደሆነ ይናገራል፡፡ በእስያ  ለሦስት ዓመታት ኖሯል፡፡ በዚያን ጊዜ ጢራኖስ በሚባል የመጽሐፍ ቅዱስ ትምህርት ቤት እያስተማረ ለሁለት ዓመታት መኖሩን በሐዋሪያት ሥራ ምዕራፍ 20 ላይ እናገኛለን፡፡ ከዚያም በላይ ዘመናትን ኖሮ ሊሆን ይችላል ግን በኖረባቸው ጊዜያቶች ሁሉ ለቅዱሳን የሚጠቅመውን አድርጓል፡፡ ከሽማግሌዎች ጋር ሆኖ የሦስት ዓመት አገልግሎቱን ሲገግምና ሲከልስ የእግዚአብሔርን ሰዎች ከሚጠቅማቸው ነገር አንዱንም እንዳላስቀረ በልበ ሙሉነት ይናገራል፡፡
በዚህ ክፍል ሐዋሪያው ርግጠኛ ሆኖ የሚናገረው ከቤተ ክርሰቲያን ሕዝብ ከሚጠቅማቸው ነገር አንድ እንኳ እንዳላስቀረባቸው ነው፡፡ የሚያደርጋቸውን ሁሉ ነገሮች ያደረገው ለአማኖቹ እንድጠቅማቸው ብሎ ነው፡፡ የእውነተኛ አገልጋይነት ሕይወትም እኮ እ ሌላውን በመጥቀም ነው፡፡ ወንጌላችን ራሱ ሌሎችን መጥቀም ነው፡፡ ጳውሎስ በሌላም ሥፍራ ሰዎችን ለመጥቀም ራሱን እንደሰጠ ሲናር እንዲህ አለ፡፡
ከሰው ሁሉ አርነት የወጣሁ ስሆን የሚበልጡትን እንድጠቅም እንደ ባሪያ ራሴን ለሁሉ አስገዛለሁ። አይሁድንእጠቅም ዘንድ ከአይሁድ ጋር እንደ አይሁዳዊ ሆንሁ፤ ከሕግ በታች ያሉትን እጠቅም ዘንድ፥ እኔ ራሴ ከሕግ በታች ሳልሆን፥ ከሕግ በታች ላሉት ከሕግ በታች እንዳለሁ ሆንሁ፤ ሕግ የሌላቸውን እጠቅም ዘንድ፥ ያለ እግዚአብሔር ህግ ሳልኖር ነገር ግን በክርስቶስ ሕግ በታች ሳለሁ፥ ሕግ ለሌላቸው ሕግ እንደ ሌለኝ ሆንሁ፤ ደካሞችን እጠቅም ዘንድ ለደካሞች እንደ ደካማ ሆንሁ፤ በሁሉ መንገድ አንዳንዶችን አድን ዘንድ፥ ከሁሉ ጋር በሁሉ ነገር እንደ እነርሱ ሆንሁ(1 ቆሮ 9፡19-22)።
ጳውሎስ ለተለያዩ ሰዎች ወንጌልን ሰብኮ እነርሱ ደህነነትን የሚያገኙበት መንገድ ሲናገር እነርሱን መጥቀም ይለዋል፡፡ በሌላም ሥፍራ ለፊልጵስዩስ ቤተ ክርስቲያን አማኞች ስናገር በምድር መኖሩ ራሱ ለራሱ ጥቅም ሳይሆን ለአማኞች ጥቅም እንደሆነ ይናገራል፡፡ ለእርሱ ወደ ክርስቶስ መሄድ እጅግ የተሻለና የበለጠ ነገር እንደሆነ ቢያምንም በሥጋ ከእነርሱ ጋር መኖር ግን ከእርሱ ይልቅ ለእነርሱ/ ለአማኞቹ/ ጥቅም እንደሆነ ያስረዳል፡፡ እንዲህም ሲል፡
ለእኔ ሕይወት ክርስቶስ፥ ሞትም ጥቅም ነውና። ነገር ግን በስጋ መኖር ለእኔ የሥራ ፍሬ ቢሆን፥ ምን እንድመርጥ ኣላስታውቅም። በእነዚህም በሁለቱ እጨነቃለሁ፤ ልሄድ ከክርስቶስም ጋር ልኖር እናፍቃለሁ፥ ከሁሉ ይልቅ እጅግ የሚሻል ነውና፤ ነገር ግን በሥጋ መኖሬ ስለ እናንተ እጅግ የሚያስፈልግ ነው( ፊልጵስዩስ 1፡19-23)።
እኛስ ዛሬ ራሳችንን ስንፈትሽ  እግዚአብሔር በሰጠን ዘመን ባገለገልንባቸው ሥፍራዎች ሁሉ የእግዚአብሔርን ሕዝብ የሚጠቅም አገልግሎት እንደሰጠን እርግጠኞች ነንን? ለእግዚአብሔር ሕዝብ የምንጠቅም አገልጋዮች እንድንሆን እግዚአብሔር ይፈልጋል፡፡ በእውነት በዚህ ዘመን እግዚአብሔር ይርዳን፡፡ ሐዋሪያው ጳውሎስ ለኤፌሶን ቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ካስተማረው ትምህርት በአገልገሎታችን እንዴት ቅዱሳንን መጥቀም እንደምንችል አራት መሠረታዊ ነጥቦችን እንመለከታለን፡፡ በአገልግሎታችን ሌሎችን መጥቀም የምንችለው እንዴት ነው?
1.    ለአገልጋይነት የሚገባ ባሕሪይ /An aproprate character/ ሲኖረን ነው፡፡

ወደ እስያ ከገባሁበት ከመጀመሪያ ቀን ጀምሮ፥ በትሕትና ሁሉና በእንባ ከአይሁድም ሴራ በደረሰብኝ ፈተና ለጌታ እየተገዛሁ ዘመኑን ሁሉ ከእናንተ ጋር እንዴት እንደ ኖርሁ እናንተው ታውቃላችሁ፤ ጳውሎስ በዚህ ሥፍራ ወደ ሌሎች አሳቦች ሁሉ ከመግባቱ በፊት ስለ ራሱ የአገልጋይነት ባሕሪይ አጠንክሮ ይናገራል፡፡ በአማኞች መካከል በተመላለሰባቸው ጊዜያቶች ሁሉ 3 ዋና ዋና የአገልጋይ ባሕሪያትን ማሳየቱን በልበ ሙሉነት ይገልጻል፡፡ 1. ትሁት ነው፡፡ 2. የእምባ ሰው ነው፡፡ 3. ለጌታ የተገዛ ሰው ነው፡፡ ትህትና የሌለው ሰው በእግዚአብሔር አገልግሎት ቢሰማራም ቅዱሳንን ሊጠቅም አይችልም፡፡ እንዲያውም የእርሱ አገልጋይነት ለቤተ ክርስቲያን ሸክምና ፈተና ነው፡፡ ትህትና የትዕቢት ተቃራኒ ሲሆን በምድር ላይ እጅግ አስቸጋሪ ኃጢአት ቢኖር ትዕቢት ነው፡፡ ትዕቢተኛ ሰው መንፈሳዊ ፍሬ ሊያፈራ አይችልም፡፡ ቅዱሳንን ይጎዳል፣ አገልግሎትንም ያበላሻል፡፡  ትሁታን ባሉበት ግን ፍሬ አለ፣ ነጻነት አለ፣ ሰላምም አለ፣ ሁም በደስታ ጌታን ያልካል ያገለግላልም፡፡ ጳውሎስ በዚህ ሕይወቱ የተመላለሰ አገልጋይ ነበር፡፡ እርሱ ትሁት ብቻ ሳይሆን የእምባ ሰው ነው፡፡ ስለ አማኞች በእግዚአብሕር ፊት የሚያነባ ሰው ነው፡፡ አማኞችን ሲያስተምራቸውና ሲገስጻቸውም ሁሉ በእምባ ነበር (ስለዚህ ሦስት ዓመት ሌሊትና ቀን በእንባ እያንዳንዳችሁን ከመገሠጽ እንዳላቋረጥሁ እያሰባችሁ ትጉ ቁ 31)፡፡ የምናገለግለው አገልግሎት ከእውቀት ፣ ከትምህርት፣ ከልምድ ሁሉ በላይ እምባን የሚጠይቅ ነው፡፡ ከዚህም ጋር ጨምሮ በዘመኑ ሁሉ ለጌታ የተገዛ ሰው መሆን ይገባል፡፡ ጳውሎስ ከአይሁዶች ሴራና ዛቻ ቢደርስበትም እንኳ በሕይወቱ አንድም ቀን የትዕቢት ነገር አልታየበትም፡፡ይልቁንም ከእምባ ጋር ለጌታ እየተገዛ ዘመመኑን ሊኖር የቻለ ሰው ነው፡፡ የጌታ ባሪያ ጳውሎስ እነዚህ ሦስት ዋና ዋና መልካም ባሕሪያት የታየበት ድንቅ የእግዚአብሔር አገልጋይ ነው፡፡
በዛሬዋ ቤተ ክርስቲያን ከፍተኛ ግምት የሚሰጠው አንድ ሰው የአገልግሎት ስጦታ መኖሩን ብቻ ነው፡፡ ሰባኪ፣ ዘማሪ፣ የፈውስ አገልጋይ፣ ተአምራት የሚያደርግ መሆኑን ብቻ ነው፡፡ እኛም አገልጋዮች የሆንነው የምናተኩረው በዚያ ላይ ነው፡፡ ነገር ግን እግዚአብሔር የሚባርከን በእኛ አገልግሎትም ሌሎችን የሚባርካቸው ባለን መንፈሳዊ ሕይወት ለውጥና ባሕሪይ(Charactor) መሰረት ነው፡፡ ይህ በጣም መሠረታዊ ነገር ነው፡፡  ጳውሎስ በምዕመናን መካካል ሲመላለስ እነዚህን ቁልፍ ባሕሪያትና ያሳየው ለአንድ ጊዜ ቆይታ ብቻ ወይም የሆነ ነገር ሲፈልግ ፣ ወይም አንድ ነገር እንዲሆንለት ሰዎችን ሊያማልል ያደረገው የግብዝነት ነገር አልነበረም፡፡ ነገር ግን የሁል ጊዜ የሕይወቱ ተሞክሮ እንደሆነ ሲገልጽ ወደ እስያ ከገባበት ጊዜ ጀምሮ እነዚህ ባሕሪያት የታዩበት እንደነበረ ይናገራል፡፡ ስለዚህ በአጥቢያ ቤተ ክርስቲያንም ሆነ በሌሎች የአገልግሎት  ክፍሎች ተሰማርተን ስናገለገል በእውነት ሌሎችን እንጥቀማቸው ካልን ወደ መሠረቱ መመለስ ይኖርባናል፡፡ ያውም ከተሰጡን የጸጋ ሥጦታዎች በላይ በእግዚአብሔርና በሕዝቡፊት ያለን የሕይወት ለውጥ ምን እንደምመስል መገምገምና መረዳት ያስፈልገናል፡፡

2.   አገልግሎታችን ሥልታዊነት Strategy ያለው ሲሆን ነው፡፡

 የምንሰጠውን አገልግሎት የትና እንዴት እንደምንሰጥ በትክክል ማወቅ ቅዱሳንን ለመርዳት የሚያግዘን አንዱ መንገድ ነው፡፡ ሐዋሪያው የአገልግሎቱ ሽፋን( a ministerial scope) ለማን፣ ለምንና   እንደሆና ከየት እስከ የትም መሆን እንዳለበት የተረዳ ሰው መሆኑን በዚህ ክፍል ያሳየናል፡፡ (ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ንስሐንና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች እየመሰከርሁ በጉባኤም በየቤታችሁም አወራሁላችሁና አስተማርኋችሁ፣ቁ.20-21)፡፡ ጳውሎስ በዚህ አሳቡ ማንን እንደሚጠቅም ያውቅ ነበር፣ የት እንደሚጠቅማቸውም ያውቅ ነበር፡፡ በእርሱ አገልግሎት የሚጠቀሙት ሰዎች ሁሉ ማለትም አይሁድም አሕዛብም ናቸው፡፡ በዚያ ጊዜ የዓለም ሕዝብ አይሁድና አሕዛብ ተብሎ በሁለት ጎራዎች የተከፈሉ ቢሆንም የጳውሎስ አገልግሎት ግን  ለሁሉም ነበረ፡፡  እርሱ ራሱ ሁሉንም የሚጠቅም አገልጋይ ነበረ፡፡ ሁሉንም ማገልገሉና መጥቀሙ የሕይወቱ መመሪያ ስለነበረ ለፊልጵስዪስ ሰዎች ሲጽፍ ለወገኔ ይጠቅማል በማለት ወይም በከንቱ ውዳሴ ምክንያት አንድ እንኳ አታድርጉ፥ ነገር ግን እያንዳንዱ ባልንጀራው ከራሱ ይልቅ እንዲሻል በትሕትና ይቍጠር፤እያንዳንዱ ለራሱ የሚጠቅመውን አይመልከት፥ ለባልንጀራው ደግሞ እንጂ(ፊልጵ 2፡4) በማለት ጠንካራ መመሪያ ሰጥቶ አለፈ፡፡  የጳውሎስ ሥረ- መሠረቱ አይሁዳዊ ቢሆንም እርሱ ግን አህዛብ የሆኑ ግሪኮችንም ይጠቅማቸው ነበር፡፡ ደካሞችን ይጠቅማቸው ነበር፡፡ የተጠቁትን፣ የተጣሉትን፣ የተገለሉትን፣ አምላክ የላቸውም የተባሉትን፣ አገርም የሌላቸው የተባሉትን፣ ያልተገረዙ የተባሉትን ሁሉ ለመጥቀም ያገለግል ነበረ፡፡ በጳውሎስ አገልግሎት ውስጥ ልዩነት የሚባል ነገር ስላልነበረ እርሱ ለሁሉም የሚጠቅም አገልጋይ ሆነ፡፡
ጳውሎስ  የአገልግሎቱን ተደራሲያን ብቻ ሳይሆን የት ማገልገል እንዳለበትም የተረዳ ሰው ነበረ፡፡  አገልግሎቱ ጉባኤም በየቤታቸውም  ሁሉ ነበር፡፡ የሐሰት አስተማሪዎች ትልቁ ትኩረታቸው ቤት ለቤት እየዞሩ የቅዱሳንን ቤት መብላት፣ በእምነታቸው ያልበረቱትና አንዳንድ ቅምጥል ሰዎችን ማሳት ነው፡፡ በኢየሱስም ጊዜ የፈሪሳውያን ትልቅ ስህተት ከነበረው አንዱ ቤት ለቤት እየዞሩ የመበለቶችን ቤት መብላት ነው፡፡ በአንጻሩም ደግሞ እውነተኞች አገልጋዮች እውነተኛና ጤናማ የሆነ አገልግሎት ይዘው ወደ የቤቱ ሄደዋል፡፡ ኢየሱስም ወደ የቤቱ ሁሉ ሂዱ ስትሄዱም ሰላም ለዚህ ቤት ይሁን በሉ፣ ያቀረቡላችሁንም ብሉ ያለው አገልጋዮች ወንጌልን ለመስበክም ሆነ አማኞችን በእምነታቸው ለማጽናት የቤት ቤት አገልግሎት በጣም ተፈላጊ ስለነበረ ነው፡፡ አሁንም ይህ ሊተኮርበት ይገባል፡፡ ዛሬ በኢትዮጵያ በአገልጋይነት ስም  ብዙ ሰዎች ቤት ለቤት እየተዘዋወሩ የቅዱሳንን እምነት እየሸረሸሩ እንደሆነ በግልጽ የሚታይነው፡፡ አንዳንዶች ደግሞ ቤት ለቤት አገልግሎትን እያስቀሩ ይገኛሉ፡፡ ለምሳሌ፣ በቤተ ክርስቲያን የሚደረገው የፈውስ አገልሎት መልካም ቢሆንም አስተምሮአዊ መርሆ ግን ሙሉ በሙሉ እየተረሳ ነው፡፡ በያዕብ 1፡16 ላይ ማንም የታመመ ቢኖር የቤተ ክርስቲያንን ሽማግሌዎች ወደ ራሱ ይጥራ እነርሱም በጌታ ስም ዘይት ቀብተው ይጸልዩ ይላል፡፡ ዛሬ ቤተ ክርስቲያን አስተምህሮን ለመጣሷ ይህ ምሳሌ ነው፡፡ ሰዎች በአደባባይ ግሩም ክርስቲያኖች ቢመስሉም እቤታቸው የሚኖሩበት ሕይወት መታየት ይኖርበታል፡፡ በቤታቸው መከራን የሚቀበሉ፣ ሕይወት የተበላሸባቸው፣ የቅዱሳንን ድጋፍና ምክር የሚፈልጉ ሲኖሩ በጉባኤ አገልግሎት ብቻ መፍትሔ ልናስገኝላቸውና ልንጠቅማቸው አንችልም፡፡ የእግዚአብሔር አገልጋዮች ወደ እነዚያ ሰዎች በማቅናት ባሉበት ሁኔታ ሲገለግሉአቸው ይገባል፡፡ በተለይም የቤተ ክርስቲያን ሽማግሌዎች ከጌታ የተሰጣቸውን መንፈሳዊ ሥልጣን ከሚገልጹባቸው መንገዶች አንዱ ወደታመሙ ሰዎች ቤት በመሄድ ቃሉን ማስተማር ፣ አስፈላጊውን ምክር በመስጠት ፣በጌታ ስም ዘይት ቀብተው በመፀለይ ድዊውን የመፈወስአገልግሎት ነው፡፡ በቤተክርስቲያን ጉባኤ ላይ የሚደረገው የፈውስ አገልግሎት ለወንጌል ሥርጭት ጠቃሚ ነው፡፡ ነገር ግን የእግዚአብሔር ቃል በግልጽ የሚያስተምረን ግን ማንም የታመመ ቢኖር የቤተ ክርስያንን ሽማግሌዎች ወደ ቤቱ እንዲጠራና አገልግሎቱን እንዲካፈል ነው፡፡ የቤት ለቤት አገልግሎት ቃሉን ለማስተማር፣ መንፈሳዊ ምክርንም ለመስጠት ፣ የቅዱሳንን የእርስ በርስ ህብረት ለማጠናከርና የስተት ትምህርቶች ለመከላከል የሚረዳበመሆኑ በአደባባይ ያለውን አገልግሎት ከማካሄድ ጎን ይህኛውንም ማጠናከር ተገቢ ነው፡፡ ከመድረክ አገልግሎት ይልቅ ቤት ለቤት ተዘዋውሮ ማገልገል በጣም አድካሚ ነው፣ታዋቂም አያስብልም፡፡ ስለዚህ ብዙዎች አይሞክሩትም፣ አይፈልጉትምም፡፡ በተለይም መድረክ ተኮር መጋቢዎች መዕመናን ወደ እነርሱ እንዲመጡ እንጂ ወደ መዕመናን ወርደው በቤታቸው ማገልገል አያስቡትም፡፡ ቅዱሳንን በመንፈሳዊ ሕይወታቸው የሚጠቅም የእረኝነት  ልብ ያላቸው መጋቢያን ግን የኢየሱስንና የጳውሎስን ፈለግ ተከትለው የሚያለግሉአቸውን ምዕመናን በቤትም በጉባኤም ያለግሉአቸዋል፡፡
ከጳውሎስ አገልግሎትየምንማረውሌላው ቁም ነገር የሚያገለግላቸውን ሰዎችና ቦታን ለይቶ ማወቅ ብቻ ሳይሆን እንዴት እንደሚያገለግልም ያውቅ ነበር፡፡ እርሱ በበጉባኤም ሆነ  በቤትም ያደረገው ምንድነው; ሦስቱ የአገልግሎቱ ስልቶች ዋና ዋናዎቹ ናቸው፡፡ እነርሱም ማስተማር፣ በስበክ( እየመሰከርኩ አወራሁላችሁላችሁ ይላል እርሱ)ቁ 20፣ መገሰጽ( ቁ.31) ናቸው፡፡ ሐዋሪያት ፣ ነቢያት፣ አስተማሪዎች፣ የወንጌል ሰባኪዎችና እረኞች ሽማግሌዎች አሁን በእጃቸው የለውን ሕዝብ ቤቤቱ እየገቡ ቢያስተምሩ፣ ቢሰብኩ፣ በድካማሙም አባታዊና መጋቢያዊ ግሳጼ እየሰጡ ማገልገል ከቻሉ በእውነት ጠቅመዋል ማለት ነው፡፡ በዛሬው ጊዜ ወደ ሰዎች ቤት የሚሄዱ አገልጋዮች አሉ፡፡ መነሳት ያለበት ጥያቄ ግን የሚሄዱት እነማን ናቸው፣ ማንስ ጋ ይሄዳሉ፣ ሄደውስ ምን ያድርጋሉ የሚለው ነው፡፡ ይህ በትክክል መለስ ማግኘት ይኖርበታል፡፡ ወደ ሰዎች ቤት መሄድ ያለባት ቤተክርስቲያን ናት፣ ወይም ደግሞ ቤተክርስቲያን የወከለቻቸው አገልጋዮች በዓላማና በመርሀ ግብር ፣ ያለምንም ልዩነት ወደ እያንዳዱ ምዕመን በመግባት ሕይወታቸውን ማደስ ማስተማር፣ መምከር፣መገሰጽ ይኖርቸዋል፡፡ ካልሆነ ግን ሀሰተኞች ተኩላዎች መንጋውን ይበሉባቸዋል፡፡    
         

3.   አገልግሎታችን ቁም ነገርና ይዘት /substance and content/ ያለው ሲሆን ነው፡፡

ሰዎችን በአገልግሎታችን የምንጠቅመው በመንፈሳዊ ሕይወታቸው እንዲጠናከሩ የሚያደርገውን ነገር ሁሉ በመስጠት ነው ፡፡  ጳውሎስ እንዲህ ይላል፡፡ ወደ እግዚአብሔር ዘንድ ንስሐንና በጌታችን በኢየሱስ ክርስቶስ ማመንን ለአይሁድና ለግሪክ ሰዎች እየመሰከርሁ በጉባኤም በየቤታችሁም አወራሁላችሁና አስተማርኋችሁ እንጂ፥ ከሚጠቅማችሁ ነገር አንዳች ስንኳ አላስቀረሁባችሁም(20-21)። አሁንም፥ እነሆ፥ እኔ የእግዚአብሔርን መንግሥት እየሰበክሁ በመካከላችሁ የዞርሁ ሁላችሁ ከእንግዲህ ወዲህ ፊቴን እንዳትዩ አውቃለሁ( ቁ.25)። የእግዚአብሔርን ምክር ሁሉ ነግሬአችኋለሁና፥ ምንም አላስቀረሁባችሁም(ቁ 27)። ጳውሎስ እንደሚነግረን እርሱ ወደየቤቱም በየጉባኤ ምን ያደርግ ነበር  የሚለው ዋና ጉዳይ ነው፡፡ ወደ ሰዎች ቤት መሄድ ወይም በጉባኤ ፊት መቆም ብቻ ሳይሆን ምን አደረጉ የሚለው ነው መታየት ያለበት፡፡ ጳውሎስ አስተማረ፣አወራላቸው( ሰበከላቸው) ፣ በቁጥር 31 ላይ እንደምንመለከተው ያለማቋረጥ ሌሊትና ቀን ያውም በእምባ ሆኖ ይገስጻቸው ነበር፡፡ ሲሰብክና ሲያስተምርም መንፈሳዊ ቁም ነገር ያለበትን ስብከትና ትምህርት ያስተላልፍ እንደ ነበርከፍ ብሎ አይተናል፡፡ የመልእክቱ ይዘትስ ምን እንደነበር መረዳት በጣም አስፈላጊ ነው፡፡ ሰዎች ወደ ሰዎች ቤት መሄዳቸው ወይም ለአገልግሎትመድረክ ላይ መውጣታችን ብቻ ሳይሆን የምንለው ምንድነው የሚለው ደግሞ ሌላው ወሳኝ አሳብ ነው፡፡ ባለፈው ሁለት ዓመት አካባቢ ወደ ጌታ የሰበበሱቡት  ተወዳጁ የቅዱሳት መጻሕፍት አቀንቃኝ፣ አስተማሪና ሰባኪ የነበሩ ዶር ጆን ስቶት በአንድ ስብከታቸው ላይ እንዲህ ብለው ነበር፡፡ “ኢየሱስ ካልተዘመረ ዘማሪው መዝሙሩን አልዘመረውም፣ ኢየሱስ ካልተሰበከ ሰባኪው ስብከቱን አልሰባከውም፣የኢየሱስ ሥልጣን ካልታከለበት ጸሎቱም አልተጸለየም”፡፡ ይህ የቀድሞ ሐዋሪያት ያደረጉት  አባቶቻችንም የተከተሉት ሲሆን እኛም ጠንክረን ሊናደርገው የሚገባ ተግባር ነው፡፡ ሓዋሪያው ጳውሎስ መልእክቱም ለሰዎች ያስተላፈው ስለ ንስሐና በኢየሱስ ክርስቶስ ስለማመን(ቁ 20-21)፣ እና  ስለ እግዚአብሔር መንግሥት(ቁ.25) ይስብክና ያስተምር ነበር፡፡ እንደዚህ ዓነቱን አገልግሎት ስንሰጥ ሰዎች ይጠቀማሉ፣ይጠነክራሉ፡፡ ጳውሎስ ለራሱ ጥቅምና ዝና የሆነውን ስብከት አይሰብከም፣ እንደዚያ ያለውንም ትምህርት አያስተምርም፡፡ ራሱን አያወድስም ይልቁንስ ኢየሱስን ነው ያሳየው፡፡ ያ አገልግሎቱ እስከ ዛሬ ድረስ ወደ እኛ ዘለቀ፡፡ ዛሬ በየመድረኩ የሚሰበኩትና የሚተላለፉት ስብከቶችና ትምህርቶች ምን ይዘት አላቸው የሚለው አሳሳቢ እየሆነ በመጣበት ዘመን ላይ ነን፡፡ ሰውን ለማስደሰት ተብሎ በሚደረጉ ውድድሮች ከቁም ነገሩ ይልቅ ገለባው እየበዛ ነው፡፡ ከሰማያዊው ትምህርት ይልቅ ምድራዊ ብልጽግና ፣ ስኬት፣ የመሳሰሉት ይተኮርበታል፡፡ ካልሆነም ደግሞ የግለሰቦች ማንነት የኢየሱስን አዳኝነትና ክብር እስክሸፍን ድረስ አየተወራና እየተነገረ ነው፡፡ ይህንን ትምህርት እያዘጋጀሁ ሳለ ወደ አገር ቤት ሲደውልና ስለ አንዳንድ መንፈሳዊ እንቅስቃሴዎች ሲጠይቅ የአንድ ዕድሜ ጠገብ  ስለሆኑ አባት ይነግሩኝ ነበር፡፡ እኒህ ሰው አቶ ባንጫ በመባል የሚታወቁ ሲሆን ዶር ላምቤ ወደ ወላይታ ገብተው ወንጌል ሲሰብኩ የዶክተሩን በቅሎ በመጎተት ከረዱአቸው ወጣቶች አንዱ ሲሆኑ በወላይታ ውስጥ ወንጌልን በማሰራጭትና ቤተ ክርስቲያንንም በመምራት ትልቅ ዋጋ የከፈሉ ሰው ናቸው፡፡ እኒህ ሰው ጓደኞቻቸው ሁሉ ወደ ጌታ ተሰብስበው እርሳቸው ብቻ በሕይወት ያሉ ናቸው፡፡ ሰዎች ስለእሳቸው አገልግሎትና ታሪክ ለመጻፍ ፈልገው ሲጠይቋቸው የመለሱላቸው መልስ የሚገርም ነው፡፡ እኔ በሕይወት እያሁ የእኔን ታሪክ አትጻፉ፣ መጻፍ ከፈለጋችሁም የኢየሱስን ሥራና ታሪክ ጻፉ እንጂ የእኔን እንድትጽፉ አልፈልግም በማለት ነው፡፡ ይህ አስገርሞኛል፡፡ ሰው ራሱን ለማሳየት፣ ዝናውን ለማግኘት፣ ክብርንም ለማግኘት ብዙ ነገሮችን በሚያደርግበት ወቅት የእኔ ታሪክ አይጻፍም ማለት፣ ያውም የተሠራ የሚታይ ታሪክ እያለ አለመፍቀድ እንዴት ያለ አስደናቂ ጉዳይ ነው፡፡  በአገልግሎታችን ሰዎችን መጥቀም  የምንችለው መንፈሳዊ ቁም ነገርና ይዘት ያለበትን መልእክት ፣ መጽሐፍ ቅዱሳዊ የሆነውን እውነት፣ ሥነ-መለኮታዊና አስተምህሮአዊ የሆነውን በታማኝነት ያቀረብንላቸው እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ያስተማርናቸው፣ የሰበክናቸው፣ እና በትጋት የገሠጽናቸው እንደሆነ ብቻ ነው፡፡ ያለዚያ እያሳሳትናቸውና እየበደልናቸው መሆኑን መዘንጋት የለብንም፡፡ እግዚአብሔር ግን ቅዱሳንን እንድንጠቅም ስለሚፈልግ ከሰጠን መንገድ አንዱ ቁም ነገርን መናር፣ ቁም ነገርን ማስተማር፣ ቁምነገርን ማድረግም ነው፡፡   

4.   በአገልግሎታችን የቁርጠኝነት ሕይወት/ Determination/  ሲኖረን ነው፡፡

አሁንም፥ እነሆ፥ እኔ በመንፈስ ታስሬ ወደ ኢየሩሳሌም እሄዳለሁ፥ በዚያም የሚያገኘኝ ምን እንደ ሆነ አላውቅም፤ ነገር ግን መንፈስ ቅዱስ እስራትና መከራ ይቆይሃል ብሎ በየከተማው ሁሉ ይመሰክርልኛል። ነገር ግን ሩጫዬንና ከጌታ ከኢየሱስ የተቀበልሁትን አገልግሎት እርሱም የእግዚአብሔርን ጸጋ ወንጌልን መመስከር እፈጽም ዘንድ ነፍሴን በእኔ ዘንድ እንደማትከብር እንደ ከንቱ ነገር እቆጥራለሁ (ቁ.22-24) ።


አሁን ጳውሎስ ወደ ኢየሩሳሌም እየሄደ ነው፡፡ በዚያ ምን እንደሚገጥመው አያውቅም ግን መከራ እንደሚደርስበት ከመንፈስ ቅዱስ ተረድቷል፡፡ ቢሆንም ግን መከራ ተቀብሎም ቢሆን በኢየሩሳሌም ያሉ ቅዱሳንን በወንጌል ለመጥቀም ቆረጠ፡፡ እንዲሁም ሰዎች መከራ መኖሩን ተረድተው ወደ ኢየሩሳሌም እንዳይሄድ አጥብቀው ቢለምኑትም በኢየሩሳሌም ለመሞትም እንኳ ዝግጁ መሆኑን በቁርጠኝነት ተናገረ፡፡  ሰዎች ከሚናገሩት ይልቅ ጳውሎስን ይገዛው የነበረው እርሱ የተቀበለው የእግዚአብሔር መንፈስ ነው፡፡ ወደ ወንጌል አገልግሎት የሚሄደው በእግዚአብሔር መንፈስ ቁጥጥር ሥር ሆኖ ነው፡፡ እርሱን የሚመራው የእግዚአብሔር መንፈስ ስለሆነ ምንም እንኳ  ወደ ኢየሩሳሌም ሲደርስ የሚጠብቀው መከራና ስደት ቢሆንም በእግዚአብሔር መንፈስ ተሥሮ ወደዚያ ሥፍራ እንደሚጓዝ በግልጽ ተናራቸው፡፡  ጳውሎስ በኢየሩሳሌም የሚጠብቀው መከራ ወንጌልን በመስበኩ ምክንያት ከአይሁዶች የሚደርስት ስደት ሊሆን ይችላል፡፡ ቢሆንም ግን እርሱ ወደ ኢየሩሳሌም የሚሄደው በመንፈስ ታሥሮ መሆኑን ግልጽ አደረገላቸው፡፡ በወንጌል አገልገሎት ውስጥ  ይህን የሚመስል ዋጋ መክፈል የሚስፈልገው ለምንድነው? መስዋዕትነት  ከፍሎ ማገለገል የሚያስፈልግበት ምክንያትማ የተሰጠው አገልግሎት  ስለነበረው ነው፡፡ እንዲሮጥ የተሰጠው ሩጫ ስላለ ነው፡፡ከኢየሱስ የተቀበለው አገልግሎት መፈጸም ስላለበት ነው፡፡ ይህን ሩጫ ማጠናቀቅና አገልግሎትን መፈጸም ሲባል መከራና ስደት መኖሩ በግልጽ እየተነገረም ቢሆን ወደ አገልሎቱ እንዲንገሰግሥ ያስገድደናል፡፡ ነፍሴ በእኔ ዘንድ እንደማትከብር እንደ ከንቱ ነገር እቆጣራታለሁ ያለው ለዚህ ነው፡፡ ይህ ሐዋሪያው ጳውሎስ ለወንጌል አገልግሎትና በወንጌል ሌሎችን ለመጥቀም ምን ያልህ እንደተሰጠ የሚመለክት ነው፡፡ እርሱ ገና በኤፌሶን ከተማ ወንጌልን መስበክ በጀመረበት ወቅት መከራና ስዴት አንዲሁም በሚሰብከው ወንጌል እውነት ምክንያት በከተማው ውስጥ ሁከት ከተነሳት ጊዜ ጀምሮ ወንጌልን በመከራ መስበክን ተለማምዷል፡፡በገና በደማስቆመንገድ ሲጠራ በጌታ ስም መከራን የሚቀበል አገልጋይ እን ደሚሆን በጌታ የተነገረለት ሰው ስለነበርና ያንን ሁሉ አልፌ እዚያጋ ስለደረሰ በኢየሩሳሌም ሰለሚጠብቀው  መከራ የሚፈራበት ምክንያት አልነበረውም፡፡   ለእግዚአብሔር አገልሎት ታማኝ የሆኑ አገልጋዮች በመከራም ውስጥ ሆነው ጌታን ያገለግሉታል፡፡ እኛ ሁላችንም እኮ ከእኛ በፊት የሄዱ ሰዎች የከፈሉበት ዋጋ ውጤቶች ነን፡፡ የቀደሙት አባቶቻችን እኛ ከዳንን ይበቃናል ብለው አልተቀመጡም፡፡ ወንጌልን በብዙ መስዋዕትነት ለእኛ ሰበኩልን፡፡ እግዚአብሔር በመስዋዕትነት የምናለግለውን አገልግሎት እጅግ በጣም አድርጎ ያከብረዋል፡፡ ቁርጠኝነት ካላቸው አገልጋዮች ጋር እግዚአብሔር ይቆማል፡፡ ስለዚህ  ከጌታየተቀበልነውን አገልግሎትና ሩጫ በመፈጸም የእግዚአብሔርን መንጋ ለመጥቀም እንድንችል እግዚአብሔር ይርዳን፡፡