የቡድን መጽሐፍ ቅዱስ ጥናት የመምራት ዜዴ
በፓስተር ሳሙኤል ሾንጋ
በፓስተር ሳሙኤል ሾንጋ
ክፍል
አንድ
2 ጢሞ
3፡16-17፤ዕብራውያን
4፡12፤ሐዋ.17፡11
መግቢያ፡
የእግዚአብሔርን ቃል በግልም በጋራም ማጥናት
ለመንፈሳዊ ህይወት እጅግ በጣም አስፈላጊ
መሆኑን በቃሉ በራሱ መመልከት እንችላለን።
የእግዚአብሔርን ቃል በሚያጠኑና በማያጠኑ
ሰዎችና አገልጋዮች መካከል ትልቅ ልዩነት
መኖሩ ግድ ነው። ቃሉን ስናጠና ከሁሉ ይልቅ
ቅድሚያ ሊሰጠው የሚገባው በመንፈሳዊ ሕይወታችን
ለማድግ ካለን ዓላማ አንጻር መሆን እንዳለበት
ነው።
አንድ
ሰው በየቀኑ ተገቢውን ምግብ ካላገኘ ለተለያዩ
በሽታዎች ከመጋለጡም አልፎ ሕይወቱንም ሊያጣ
ይችላል። እንደዚሁም ሁሉ መንፈሳዊ ምግብና
ወተት የሆነውን የጌታን ቃል በየዕለቱ የማይመገብ
አማኝ በዚህ ዓለም ያሉ የተለያዩ ፈተናዎች
ቢመጡበት በቀላሉ ተጠላልፎባቸው ልወድቅ
ይችላል።
ሰዎች
የእግዚአብሔርን ቃል የሚያጠኑብቸው የተለያዩ
መንገዶች ያሉ ሲሆን አንደኛው የግል የመጽሐፍ
ቅዱስ ጥናት ዜዴ ሲሆን ሁለተኛው የቡድን
ወይም የጋራ የመጽሐፍ ቅዱስ አጠናን
መንገድ ነው።
የግል
የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ማለት አንድ ግለሰብ
ጊዜ ሰጥቶ ብቻውን በግሉ ቃሉን የሚያጠናበት
መንገድ ሲሆን የቡድን ጥናት ግን በዓይነቱ
ለየት የሚል ነው።
ሁሉም
የክርሰቲና ሕይወት ተሞክሮ የሚመጣው ከግል
ሕይወት ነው፡፡ አምልኮ፤ጸሎት፤ንስሐ፤የቅዱሳት
መጻሕፍት ጥናት ሁሉ የሚመነጨው ከግል ሕይወት
ነው፡፡ የግል መጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ማለት
አንድን ሰው ለብቻው አንድን የመጽሐፍ ቅዱስ
ክፍል ወስዶ ወይም መርጦ የሚያጠናበት ሂደት
ነው፡፡ ይህ ደግሞ ለአማኙ የመንፈሳዊ ሕይወት
ዕድገት በጣም አስፈላጊ ነው፡፡
የቡድን
የመጽሐፍ ቅዱሰ ጥናት መንገድ፡ ይህ ደግሞ
መጽሐፍ ቅዱስን በጋራ የማጥናት ዘዴ ነው፡፡
በቡድን
ማጥናት ስንል በጋራ ማጥናት ማለታችን ነው።
መጽሐፍ ቅዱስን በግል ካጠናን አይበቃም ወይ
ለምንድነው በጋራ ማጥናት የሚያስፈልገው
የሚል ጥያቄ ሊነሳ ይችል ይሆናል፡፡ ለዚህ
ደግሞ መልስ መስጠት አስፈላጊ ነው፡፡
- የቡድን መጽሐፍ ቅዱስ ጥናት የሚያስፈልገው ለእርስ በርስ መማማር ነው፡፡
- የእግዚአብሔር ቃል በቡድን ማጥናትን ስለሚያበረታታ ነው፡፡ ሐዋ. 2፡41-12፤17፡11
- መጽሐፍ ቅዱስን ስናጠና የተለያዩ ደረጃዎች እንደሚኖሩ መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡ለምሳሌ፡
- ማንበብ፡ አሳቡን መመልከት
- ማጥናት፡ መመልከት መተርጎምና መዛመድ
- ማሰላሰል፡ ቃሉ እንዳይረሳ በአእምሮ ማሰላሰልና ማብሰልሰል
- መጫወት፡ ከሌሎች ሰዎች ጋር ስላነብብነው ቃል ማውራትና ማካፈል
- የቡድን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት እንደግል ጥናት በተፈለገው ጊዜና ሁኔታ ሊከናወን አይችልም፡፡ ምክንያቱም በቡድን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ቁጥራቸው በርከት ያሉ ሰዎች በአንድ ላይ በመሰባሰብ የሚያደርጉት ስለሆነ ነው፡፡በቡድን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት የሚታዩ ባሕሪያት
- ቡድኑ ከ5- 7 ወይም ቢበዛ 9 አባላትን ያቀፈ ነው፡፡ አባላቱ ከ5-9 ሲሆኑ ይህ አነስተኛ ቡድን የሚባል ሲሆን ከ9 በላይ ከሆነ ግን መካከለኛ ቡድን ይሆናል፡፡ የአባላቱ ቁጥር ከ15 በላይ ከሆነ ደግሞ ከፍተኛ ቡድን ተብሎ ይጠራል፡፡ ስለዚህ የቡድን ጥናቱ አባላት ቁጥር ከ9 መብለጥ የለበትም ምክንያቱም የአባላቱ ቁጥር በበዛ መጠን አባላቱ አሳባቸውን የማንሸራሸር እድል እየቀነሰ ይሄዳል፡፡
- ሁሉም አባላት የንባብ ክፍሉን በየራሳቸው ይረዱታል፡፡ የተለያዩ አሳቦችንም ያፈልቁበታል፡፡
- እያንዳንዱ የቡድኑ አባል ለሌላው ያስተምራል( ያካፍላል) ከሌላውም ይማራል፡፡
- የቡድኑ አባላት በተለያየዩ የመረዳት ደረጃዎች የሚገኙ ናቸው፡፡ለምሳሌ፡- የቅርብ ጊዜ አማኞች ሆነው ብዙም የቃሉን መረዳት ያላገኙ ወይም ወደ ከፍተኛ የመረዳት ደረጃ ላይ ያልደረሱ፡፡- ቃሉን ተግተው የሚያጠኑና በፈጣን የእድገት ጎዳና ላይ ያሉ፡፡- በሕይወታቸው ያደጉና ጥልቅ የቃሉ እውቀት ያላቸው፡፡
- የቡድን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ወደ ጥናቱ የሚመጡ የተለያዩ ባሕሪያት ያላቸውን አባላት ያቀፈ ነው፡፡ለምሳሌ፡- ለመናገር የሚፈጥኑ (መሪውንም ለመቅደም የሚሞክሩ)- ረጅም ንግግር የሚወዱ- አዋቂ እንደሆኑ የሚሰማቸው- በጥናት ወቅት አውደ ወጥ የሚሆኑ- ዝምተኞች(እየያወቁም ቢሆን ለመናገር የማይቸኩሉ- ሲሶችና በቀላሉ የሚጎዱ- አልፎ አልፎ ብቻ የሚናገሩ- ያለዓላማ የሚመጡ(በይሉኝታ)- ዓይናፋሮችና በሰው ፊት ለመናገር የሚፈሩ፤ የመናገር ልምዱም የሌላቸው ሲሆኑ እነዚህን ሁሉ አንድ ላይ አዋህዶ በቡድን መምራት የመሪውን ከፍተኛ ጥረትና ትዕግሥት የሚጠይቅ ነው፡፡
- የቡድን መጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ከግል ጥናት እንዴት እንደሚለይ
- በግል ሲጠና በራስ ተነሳሽነት ከየትኛውም ቦታ በመነሳት ማጥናት የሚቻል ሲሆን በቡድን ሲጠና ግን የጥናት ክፍሉ ማዕከላዊ በሆነ አካል ይመረጣል፡፡ ለምሳሌ የክርሰቲያናዊ ትምህርት አገልግሎት ባለበት ቤተክርሰቲያን ያ የአገልግሎት ክፍል የሚመርጠው ሲሆን ካልሆነ ደግሞ በመጋቢው በኩል ይመረጥና ይዘጋጃል፡፡
- በግል የተፈለገው ያህል ምዕራፍ ወይም አንቀጽ ማጥናት የሚቻል ሲሆን በአንድ ጊዜ የቡድን ጥናት ከአንድ አንቀጽ ወይም ቢበዛ ከአንድ ምዕራፍ በላይ ማጥናት አይችልም፡፡ ምክንያቱም በቂ ጊዜ ስለማይኖርና የክፍሉ ጭብጥ አሳብ ሳይያዝ ተንጠልጥሎ ሰለሚቀር ነው፡፡
- በግል ለሚጠናው ጥናት ሰዓቱን የሚወስነው ግለሰቡ ራሱ ሲሆን በቡድን ለሚጠናው ግን በቡድኑ ራሱ ይወስናል፡፡
- የቡድን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት በቤተስብ ደረጃ፣ በቤተክርስቲያን ደርጃ፣ በአንድ መሥሪያ ቤት የሚሠሩ አማኞች ወዘተ ሰብሰብ ብለው የጌታን ቃል የሚያጠኑበት መንገድ ነው። ብዙ ወገኖች በዚሁ መንገድ በሚደረገው የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት በሕይወታቸው አድገዋል፣ ቃሉን በማስተማርም ሆነ በመስበክ ውጤታማ አገልግሎት መስጠት ወደ ሚችሉበት የዕድገት ደረጃ ሊደርሱ ችለዋል።
የቡድን
የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ሁለት አቀራረቦች አሉት
- ዳይዳክቲቭ (Didactic)አቀራረብ ዜዴ፡ ይህ አቀራረብ ከውስን አሳብ ተነስቶ አጠቃላይ መርሆን የሚዳስስ ሲሆን ወጥ የሆነ የጥናት ክፍል የለውም፡፡ አንዳንድ ጊዜ ይህ ዓይነቱ አቀራረብ በሰለጠኑት አገሮች ይታያል፡፡ ይሁን እንጂ ወጥ ለሆነና ተያያዥነት ላለው ጥናት አይረዳም፡፡
- ኢንዳክቲቭ (Inductive)አቀራረብ ዜዴ ፡ ይህ አቀራብ ዜዴ ከአጠቃላይ መርህ ተነሰቶ እውነታን በመዳሰስ ውስን ወደ ሆነው አሳብ የሚያደርስ የአቀራብ ዓይነት ነው፡፡ የኢንዳክቲቭ አጠናን ዜዴ ከመጽሐፍ ቅዱስ ንባብ ተነስቶ ወደ ድምዳሜና የሕይወት ተዛምዶ የሚያደርስ ነው፡፡ በዚህ ጥናት ጊዜ ጥናቱ የሚጀምረው ከምንባቡ እንጂ ከተወሰኑ ውስን አሳቦች አይደለም፡፡ ውስንና የግል ጉዳዮች የሚዳሰሱት የንባብ ክፍሉ በተገቢው ሁኔታ ከተተነተነ በኃላ ያንን ትንተና መሠረት በማድረግ ነው፡፡
- የቡድን መጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መሪ ጥያቄዎችን በመጠየቅ የቡድኑን የውይይት አቅጣጫ ይጠቁማል፡፡ ይህ ደግሞ መጽሐፍ ቅዱስ ስለ ራሱ እንዲናገር ለማድረግ ያግዛል፡፡
- በሁሉም ጊዜ ከሚጠኑ የንባብ ክፍሎች በመነሳት የሚጠየቁ የጥያቄ ዓይነቶች አሉ፡፡እነርሱም ፡
- የምልከታ ጥያቄዎች፡ ክፍሉ ምን እንደሚል ለመናገር የሚያስቸሉ ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ክፍሉ ምን ይላል?፤ነጥቦችን ዘርዝር፤ እና የመሳሰሉት ይገኙበታል፡፡
- የትርጉም ጥያቄዎች፡ የክፍሉ አሳብ ምን ማለት እንደሆነ ለመረዳት የሚያስችሉ ጥያቄዎች ናቸው፡፡ ይህ ማለት ምን ማለት ነው? በራስህ አባባል ገለጽ፤ ይህንን እንዴት ትረዳዋለህ የመሳሰሉት ጥያቄዎች ናቸው፡፡
- የትግበራ ወይም የተዛምዶ ጥያቄዎች፡ ተሳታፊዎቹ በንባብ ክፍሉ የተገኘውን አሳብ ከግል ሕይወታቸው ጋር እንዲያዛምዱት የሚረዳ ጥያቄ ነው፡፡ ይህ በሕይወት እንዴት ሊተገበር ይችላል? ከዛሬው ጥናት ያገኘኸውን ለቡድንህ አካፍል፡፡ ይህ አቀራረብ ም.ት.ተ. (ምልከታ፤ ትርጉምና ተዛምዶ) ወይም መ.መ.ማ.(መመልከት፤ መተርጎም ና ማዛመድ ) ተብሎ ይታወቃል፡፡ መሪው የጥናት ቡድኑን በሚመራበት ወቅት እነዚህን ሦስት ዓይነት ጥያቄዎችን ለይቶ ማወቅ ይኖርበታል፡፡ በቡድን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ዝግጅቱ የቀረቡት ጥያቄዎች ግልጽ ላይሆኑ ይችላሉ፡፡ መሪው ግን በራሱ አባባል ለቡድኑ አባላት ግልጽ ሊያደርግ ይችላል፡፡
- የዚህ ዓይነት ጥናት ዋና ዓላማ መጽሐፍ ቅዱስ ራሱ እንዲናገር ማድረግ ነው፡፡
የቡድን
መጽሐፍ ቅዱስ ጥናት በተለይም የኢንዳክቲቭ
አቀራረብ
በምን እንደሚያተኩር፡፡
- ምንባባዊ (Textual Study ) ፡ በምንባብ ክፍል ወይም በአንድ መጽሐፍ ላይ ያተኮረ ጥናት ነው፡፡ይህ ዓይነት አቀራረብ አንድን መጽሐፍ በሚገባ ለማወቅ የሚረዳ ነው፡፡ ለምሳሌ፤ የሮሜ መጽሐፍ፣ የኤፌሶን መጽሐፍ፣ የዘፍጥረት መጽሐፍ ወዘተ ናቸው፡፡
- ርዕሳዊ ( Topical Study ) በአንድ ርዕስ ላይ የሚያተኩር ሲሆን ይህኛው ደግሞ አስተምህሮችን ለመዳሰስ ይረዳል፡፡ ለምሳሌ፡ ፍቅር፤ ቅድስና፤ በቤተ ክርስቲያን፤ ጸሎት፤ መስጠት ወዘተ የመሳሰሉት የጥናት ዝግጅቱ ትኩረት ሊሆኑ ይችላሉ፡፡
- ገጸ ባሕሪያዊ ( Character Study)፡ በአንድ ሰው ሕይወት ላይ መሠረት ያደረገ ጥናት ሲሆን እግዚአብሔር በብሉይ ኪዳንም ሆነ በአዲስ ኪዳን የተጠቀመባቸውን ሰዎች ሕይወት የሚተነትንና ከምሳሌነታቸው የሚያሰተምር ነው፡፡ ለምሳሌ፡ የዳዊት ሕይወት፤ የአብራሃም ሕይወት፣ የሙሴ ሕይወት፣ የጳዉሎስ ሕይወት፤ የኢየሱስ ሕይወት ወዘተ የመሳሰሉት ናቸው፡፡
ክፍል ሁለት
የመሪው
ሚና
- በቡድን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት ወቅት የቡድኑ መሪ ዋና ኤጄንት ስለሆነ ሊኖረው ስለሚገባው ሚና ማወቅ ይኖርበታል፡፡
- የቡድን መጽሐፍ ቅዱስ ጥናቱ በመሪው ምክንያት ሊያምርም ሊበላሽም ይችላል፡፡ ሁሉም የሚወሰነው በመሪው ማንነትና አቀራረብ ነው፡፡ ስለዚህ የመሪው ሚና እጅግ በጣም አስፈላጊ መሆኑን መገንዘብ ያስፈልጋል፡፡
- የቡድን የመጽሐፍ ቅዱስ ጥናት መሪን ሚና በሦስት ከፍለን ማየት እንችላለን፡፡
- የመሪው ሚና ከጥናት በፊት፡
- ጥናት ከመካሄዱ በፊት መሪው በግሉ መዘጋጀት ይኖርበታል፡፡ ይህ ደግሞ የመሪውን ተሳትፎ ከአድማጮቹ የተለየ ያደርገዋል፡፡ የቡድኑ አባላት ወደ ጥናቱ ከመምጣታቸው በፊት በሚያጠኑበት የምንባብ ከክፍሉ ተዘጋጅተውበት መምጣት ቢችሉ መልካም ነው፡፡ እነርሱ ቢዘጋጁም ባይዘጋጁም መሪው ግን የመዘጋጀት ግዴታ አለበት፡፡ መሪው ከጥናት በፊት እንዴት ነው የሚዘጋጀው;
- ስለ አገልግሎቱ እግዚአብሔርን በማመስገን ተግቶ መጸለይ አለበት፡፡
- ስለሚያጠኑ ሰዎች ስለ እያንዳንዳቸው በጌታ ፊት መማለድ አለበት፡፡
- በተቻለ መጠን የቡድኑን አባላት ስለ ዕለቱና ስለ ጥናቱ ማሳሰብ አለበት፡፡
- የጥናት ክፍሉን በግሉ አስቀድሞ ማጥናት ይኖርበታል፡፡ የጥናት ክፍሉን በግሉ ሲያጠና በጥናት ዝግጅቱ ለተቀመጠው ጥያቄ መልስ ከመስጠት ጠለቅ ባለ መልኩ መዘጋጀት አለበት፡፡
- የንባብ ክፍሉ የሚያስተላልፈው መልእክት ምን እንደሆነ መረዳትመቻል አለበት፡፡ ለዚህም የሚረዱ መርጃዎችና ማጣቀሻዎችን መጠቀም ይችላል፡፡ ለምሳሌ፡ መዝገበ ቃላት(ባይብል ዲክሺኔሪ ) ፤የቃላት ማውጪያ ( ኮንኮርዳንስ)፤የመጽሐፍ ቅዱስ ካርታ ( አትላሰ) እና የማብራሪያ መጻሕፍት ( ኮሜንታሪ) ሲሆን የማብራሪያ መጻሕፍት ሲጠቀም መሪው በጣም ከፍተኛ ጥንቃቄ ሊያደርግ ይገባዋል፡፡ ምክንያቱም በተሳሳተ መንገድ የተተረጎሙ በርካታ ኮሜንታሪዎች ስላሉ ሙሉ በሙሉ በእነርሱ መተማመን አያስፈልግም፡፡ ጥሩ የሆኑ ኮሜንታሪዎች ግን ለመሪው ዝግጅት በጣም ጠቃሚዎች ናቸው፡፡
- የመሪው ሚና በጥናት ወቅት
- ከተሳታፊዎችም ሆነ ከመደበኛው ሰዓት ቀድሞ መገኘት አለበት፡፡ አንዳንድ መሪዎች ቀድመው በመገኘት መልካም ምሳሌዎች ናቸው፡፡ ቀድሞ መገኘት በርካታ ጥቅሞች አሉት፡፡ ለምሳሌ፡
- ቦታውን ለማስተካከል፤ የአባላት ወንበር አቀማመጥ ማስተካከል የሚቻለው ቀድሞ በመገኘት ነው፡፡ የጥናት ቦታን በጥናቱ ጊዜ ለማዘጋጀት ሞከር ሰዓቱን ያባክንና መጨረሻ ለይ ሰውን ሁሉ ለጥድፊያ ያጋልጣል፡፡
- ቦታው ለጥናት ቡድኑ አባላት ተስማሚና ጸጥታ ያለው መሆኑን ማረጋገጥ፡፡
- የአባላት አቀማመጥ ዙሪያ ክብ እንዲሆን ያስፈልጋል፡፡ መሪውም ሁሉንም አባላት ሊያይ በሚችልበት ቦታ መቀመጥ አለበት፡፡
- በጥናቱ ቦታ በቂ የመጽሐፍ ቅዱስ ቅጂዎች መኖራቸውን ማረጋገጥ፡፡
- ጥናቱን ልክ በሰዓቱ መጀመር ያስፈልጋል፡፡ ማንኛውንም ፕሮግራም በሰዓት አለመጀመር በሰዓት እንዳያልቅ ያደርጋል፡፡ ፕሮግራምን በሰዓት መጀመር ተሳታፊዎቹ በጥናት ፕሮግራሙ ላይ መተማመን እንደዲኖራቸው ከማድረጉም በላይ በሚቀጥለው ፐሮግራም በንቃት እንዲመጡ ያደርጋቸዋል፡፡
- ጥናቱ በሰዓት ከተጀመረ ደግሞ በሰዓት ለመጨረስ መትጋት ያሰፈልጋል፡፡ አባላቱ ለመምጣት ከሚቸኩሉ ይልቅ ለመሄድ እንደሚጣደፉ ምንጊዜም የታወቀ ነው፡፡
- ጥናቱ ሲጀመር ተገቢውን መግቢያ መስጠት፡፡
- ፍቅርን የሚገልጽ አጭር ሰላምታ መስጠት
- ጥናቱን በጸሎት መክፈት
- አጭር ክለሳ መስጠት(ጥናቱ የተያያዘ ስለሆነ) የባለፈውን ጥናት አሳብ ማሰታወስ
- ከ2 ደቂቃ ላልበለጠ ጊዜ ስለዕለቱ ጥናት አጭር መግለጫ መስጠት ምክንያቱም አድማጮቹ የዕለቱን የጥናት ርዕሰ ጉዳይ በእምሮአቸው እንዲይዙና እንዲዘጋጁ ይረዳል፡፡
- የዕለቱን ጥናት ስትጀምር ክፍሉን በግልጽ ሁኔታ አንብብ ወይም አባላቱ ተከፋፍለው እንዲያነቡት ጋብዛቸው፡፡
- ቡድኑን በምትመራበት ወቅት ብዙ እንዳትናገር ተጠንቀቅ፡፡ የማጠቃለያ አሳብ መስጠት ካልሆነ በቀር ጥያቄውን ለአባላቱ አቅርብላቸውና አንተም አብረህ ተሳታፊ ለመሆን ሞክር፡፡
- የቡድኑ አባላት በጥናቱ እንደሚገባ መሳተፋቸውን አረጋግጥ፡፡ ጥቂት ሰዎች ብቻ የሚሳተፉበትና የቀሩት ደግሞ ሰሚዎች ብቻ እንዳይሆኑ ተከታተል፡፡
- ራስህን እንደ አስተማሪ አትቁጠር፡፡
- ጥያቄዎች ሲነሱ መልስ ከመስጠትህ በፈት ተሳታፊዎች ለቀረበው ጥያቄ መልስ እንዲሰጡበት አበረታታቸው፡፡ የተሳታፈዎች መልስ አርኪ ካልሆነ አንተ መልስ ስጥበት፡፡ ጥያቄው ከባድ ከሆነ ደግሞ ሌሎችን ለማማከር ተስፋ ስጥ እንጂ ያልሆነ መልስ እንዳትሰጥ ተጠንቀቅ፡፡ ሁሉንም ጥያቄ የመመለስ ግዴታ ሊኖርብህ አይችልም፡፡
- በጥናት ወቅት የቁጣና የተግሣጽ ባሕሪይ እንዳይታይብህ ተጠንቀቅ ይልቁንም ሁሉን በፍቅር ተቀበል፡፡
- አባላት አሳብ ሲሰጡ ከንባብ ክፍሉ አሳብና ከአውዱ እንዳይወጡ ተከታተል ምክንያቱም የአሳብ መልቀቅ ወይም ከርዕስ ውጭ መሆን የጥናቱን መድረሻ ያበላሸዋል፡፡
- የጥናት ክፍሉን ጥያቄ በአባላቱ ፊት እንዳታጠና ተጠንቀ፡፡ ይልቁንም አስቀድመህ በአእምሮህ ተዘጋጅተህበት መምጣት ያስፈልጋል
- በጥናት ጊዜ ክርክር እንዳይኖር ለመቆጣጠር ሞክር፡፡ የሚከራከሩ ሰዎች በክርክራቸው ለመቀጠል የሚፈልጉ ከሆነ ጉዳዩን ትተው ወደ ሌላ ነጥብ እንዲሸገሩ በጥበብና በዜዴን መጠቀም፡፡
- እያንዳንዱ ተሳታፊ የሚያቀርበውን አሳብ አክብር፡፡ አሳብ አቅራቢውንም አበረታታ፤ የሚያቀርበው አሳብ ልክ ካልሆነ በፍቅር አስረድተህ መልሰው፡፡
- በርካታ ጥቅሶችን ከተለያዩ ቦታዎች መጥቀስ ለአሳብ መልቀቅ ( ለአውደ ወጥነት ) መንስኤ ስለሚሆን ከፍተኛ ጥንቃቄ አድርግ፡፡
- አባላቱ በተቻለ መጠን መጽሐፍ ቅዱስ ይዘው እንዲመጡ አበረታታ፡፡
- ጠጥረሩነና መለከካመም የሀሆነ መደመምደመሚየያ አደድረርገግ
- ከጥናት ክፍሉ የተገኙ አሳቦችንና ዋና አሳቡን ጠቅለል አድርገህ ለአባላቱ አስጨብጥ
- በጥናቱ ተገኝተው አሳባቸውን ያካፈሉትን ሌሎችንም በአጭር ቃል አመስግናቸው፡፡
- በሚቀጥለው የጥናት ክፍል ተዘጋጅተውበት እንዲመጡ አሳስባቸው የንባብ ክፍሉንም ንገራቸው፡፡
- ከቤተ ክርሰቲያን የሚተላለፍ መልእክት ካለ ባጭሩ ተናገር፡፡
- የፀሎት ርዕስ የሚሰጥ ሰው ካለ ተቀበል፡፡ የይሁን እንጂ እንዳይንዛዛና የሚቸኩሉ አባላት ልብ እንዳያንጠለጥል አድርግ፡፡ ፕሮግራሙን በጸሎት ዝጋው፡፡
- የመሪው ሚና ከጥናት በኃላ
የመሪው ሥራ ከጥናቱ
በኃላም የሚቀጥል ነው፡፡ ስለዚህ የቡድን
መጽሐፍ ቅዱስ ጥናቱን የመምራት አገልግሎቱን
ካጠናቀቀ በኃላ ሊያደርጋቸው የሚገባቸውን
ነገሮች በአጭሩ እንመልከት፡፡
- አባላቱ ጥናቱን በተገቢ ሁኔታ ማጥናት አለማጥናታቸውን ፤በሰዓት መገኘት አለመገኘታቸውን፤መሪው ራሱ በሰዓት ጀምሮ በሰዓት መጨረስ አለመጨረሱን እና ሌሎች ነጥቦችን መሠረት በማድረግ አጠቃላይ የጥናቱን ሁኔታ መገምገም ይኖርበታል፡፡
- መሪው በጥናት ወቅት የተቸገረባቸው እና መፍትሔ ለመስጠት ያልቻለባቸው ጉዳዮች ካሉ ለቤተክርስቲያን ሪፖርት ማድረግ የጋራ መፍትሔ ሊፈልግ ይችላል፡፡
- በተቻለ መጠን ረዳት ሊሆን የሚችል ሰው ማዘጋጀት ፡፡ መሪ ተተኪ ሊያፈራ ከቻለ አገልግሎቱ ከሁሉም አንጻር እድገት እያሳየ ሊሄድ ይችላል፡፡
- ከጥናት ቡድኑ አባላት ጋር በጥሩ ግንኙነትና መቀባበል ቀጥል፡፡ እግዚአብሔር አምላክ ለሁሉም በሁሉም የአገልግሎት ወቅት ጸጋውንና ምሕረቱን ያብዛ፡፡ አሜን፡፡
No comments:
Post a Comment